>
5:21 pm - Thursday July 20, 7150

የጦቢያ ዘመን አቆጣጠር ከፈረንጅ ዘመን አቆጣጠር አንጻር (መስፍን አረጋ)

የጦቢያ ዘመን አቆጣጠር ከፈረንጅ ዘመን አቆጣጠር አንጻር

መስፍን አረጋ


ዓመት ሁለት ዓመት ሲሄድ እያያችሁ

ጊዜ ገሰገሰ ለምን ትላላችሁ፡፡

በዘመን ግሥገሳ ዕድሜያችን ተማርኮ

ያለፍነው እኛ ነን ጊዜ አይደለምኮ፡፡

አለቃ ከበደ ሚካኤል  (ዛሬና ነገ)


ይህ ጦማር የሚያተኩረው አገራችን ጦቢያን ጦቢያ ካሰኟት ዐበይት ትውፊቶች ውስጥ አንዱ በሆነው በዘመን አቆጣጠራችን ላይ ነው፡፡  አስቀድመን ግን ዘመን መቁጠርያ የሚለው ሐረግ የተንዛዛ ስለሆነ ዮማዝ በሚለው አጭር ቃል እንተካዋልን፡፡   ዮማዝ (calendar) ማለት ሳይቸግረን ጤፍ ተበድረን፣ እንግሊዘኛውን እንዳለ ወስደን ካሌንደር የምንለው ሲሆን፣ ቃሉ የተገኘው ደግሞ ዮም (ዛሬ) እና አሃዝ (ቁጥር) ከሚሉት ቃሎች ነው፡፡  ስለዚህም የአገራችን የዘመን አቆጣጠር የኢትዮጵያ ዮማዝ (Ethiopian Calendar) ወይም ባጭሩ ኢዮ (EC) ሲሆን፣ የፈረንጆች የዘመን አቆጣጠር ደግሞ ጎርጎሮሳዊ ዮማዝ (Gregorian Calendar) ወይም ባጭሩ ጎዮ (GC) ይሆናል፡፡  አማረኛችን ደግሞ ግሱን እንደ ባለቤቱ በመለዋወጥ እንዳበጁት ስለሚበጅ፣ ዮማዝ የሚለውን ቃል ግስ በማድረግ ዮመዘዩምዝዮማዥዩመዛዮማዛዊ እያልን ልናስኬደው እንችላለን፡፡  ዮመዘ ማለት ዮማዝ አዘጋጀ፣ ዮማዛዊ አደረገ ማለት ሲሆን፣ የእንግለዚኛ አቻ የለውም፡፡  

አገራችን ጦቢያ ከሰለጠነው ዓለም ጋር አብራ ትራመድ ዘንድ የራሷን ዮማዝ ንቃ ጥላ የፈረንጆችን መከተል አለባት የሚሉ ምሁር ነን ባዮቸ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተበራከቱ መጥተዋል፡፡  የነዚህ ‹‹ምሁሮች›› ምክኒያቶች የተለያዩ ቢሆኑም፣ ዋናወቹ ግን የሚከተሉት ሁለቱ ናቸው፡፡  

የመጀመርያው ምክኒያት የስልጣኔን ምንነት በትክክል ባለመረዳት ፈረንጅን በሁሉም ረገዶች ስልጡን፣ የፈረንጅን እሴቶች ደግሞ ሁሉንም ምጡቅ አድርጎ የማየት የተሳሳተ አመለካከት ነው፡፡  ለዚህ አመለካከት ዋናው ተጠያቂ ደግሞ በነጮች (በተለይም ደግሞ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን አምርረው በሚጠሉት በመሠሪወቹ በእንግሊዞች) ከፍተኛ ተሳትፎ የተሠረተው ዘመናዊ ሳይሆን ዘመናዊ ነው የሚባለው የትምህርት ስርዓታችን ነው፡፡   

ሁለተኛውና ይበልጥ አደገኛ የሆነው ምክኒያት ደግሞ የሐበሻ (ይበልጡንም ደግሞ የአማራ) ናቸው ተብለው የሚታሰቡን የኢትዮጵያን አሻራወች ተራ በተራ በማጥፋት ኢትዮጵያዊነትን ለማጥፋት የተሸረበው በምዕራባውያን የሚደገፈውና የሚደጎመው የኦነጋውያን ሤራ ነው፡፡  በዋቄፈታ እንጅ በክርስትና የማያምኑት ጉዲና ቱምሳን የመሳሰሉት ቀንደኖቹ ኦነጋውያን የጵንጠጣ ሊቃቡኖች (patriarchs) የሆኑት ተዋሕዶን ለመግደል ሲሉ ብቻ እንደሆነ ሁሉ፣ የኦሮሞ ናቸው የሚሏቸውን እነ ገዳን ስልጡን እያሉ ፊደልንና ሌሎችን የሐበሻ ናቸው የሚሏቸውን እሴቶች ኋላቀር የሚሏቸው ደግሞ በዘመናዊነት ሰበብ የኢትዮጵያዊነትን አሻራወች ለማጥፋት ሲሉ ብቻ ነው፡፡        

ኢትዮጵያን አለመጠን ከመጥላታቸው የተነሳ ዋና መፈክራቸው ‹‹ኢትዮጵያ ከኦሮምያ ትውጣ ›› (Ethiopia out of Oromia) የሆነው ኦነጋውያን፣ የኢትዮጵያን ዮማዝ ከኢትዮጵያ ለማጥፋት ቆርጠው ቢነሱ ደግሞ አይፈረድባቸውም፣ በኢትዮጵያ ዮማዝ የማትጠቀም ኢትዮጵያ፣ ኢትዮጵያ ልትባል አትችልምና፡፡  ያስራ ሦስት ወሮች አገር የመባልን ብርቃይነት (uniqueness) ማንም አያገኘውም፡፡  ምዕራባውያን የራሳቸው ጠጠር እያዋደዱ ያፍሪቃውያንን ወርቅ የሚያራክሱት ያፍሪቃውያንን በራስ መተመማን እንደ ጦር ስለሚፈሩት እንደሆነ ልንገነዘብ ይገባል፡፡  ካብዛኛው ዓለም ተለይቶ በግራ በመንዳቱ (driving on the left) ወይም ደግሞ ለሰገል (science) እንዲሁም ለኪንሲን (technology) አመቺ ያልሆነ የቁነና ስርዓት (measurement system) በመጠቀሙ ራሱን ብርቃይ (unique) አደርጎ ለመኩራራት የሚሞክር እንግሊዛዊ መደዴ፣ በአፍሪቃዊ እሴቶች ለመሳለቅ ሲሞክር ከት ብለን ልንስቅበት ይገባል፡፡  

የኢትዮጵያ ዮማዝ የተቀመረው በዘፈቀደ ሳይሆን ካገራችን አየር ንብረት፣ ባሕልና ሐይማኖት ጋር በጥብቅ ተቆራኝቶ መሆኑን ከወሮቹ ስያሜወች መረዳት ይቻላል፡፡  እነዚህ የወሮች ስሞች ደግሞ በታላቁ ሊቅ በአለቃ ደስታ ተክለወልድ ‹‹ዐዲስ ያማረኛ መዝገበ ቃላት›› ውስጥ ተዘርዝረዋል፡፡  

  1. መስከረም (መዝከረ፣ ዓም) ማለት ያመቱ መዘከርያ (ማስታወሻ) ማለት ነው፡፡
  2. ጥቅምት ማለት ከመሬት ብዙ ጥቅም የሚገኝበት፣ እህሉ፣ ተክሉ ፍሬ የሚሰጥበት ማለት ነው፡፡
  3. ኅዳር ማለት ገበሬ ሰብሉን እየጠበቀ ከቤቱ ውጭ (ማሳ ላይ) የሚያድርበት ማለት ነው፡፡
  4. ታኀሣሥ ማለት ሰብዓ ሰገል ወልደሔርን (ማለትም እየሱስን) ለመፈለግ (ለማሠሥ) ወደ ቤተልሄም የሄዱበት ጊዜ ማለት ነው፡፡  የገና በዓል የሚውለውም በዚሁ ወር ነው፡፡
  5. ጥር ማለት የጠረረ፣ ሙቀቱ ብርቱ የሆነ ማለት ነው፣ ጠራራ ፀሐይ እንዲሉ፡፡
  6. የካቲት (ከተተ) ማለት የመከር (ማለትም ያዝመራ) መክተቻ ማለት ነው፡፡
  7. መጋቢት ማለት ወልደሔር (ኢየሱስ) በጸሎተ ሐሙስ (ከፋሲካ በፊት ባለው ሐሙስ) ሥጋውንና ደሙም የመገበበት (ማቴወስ 26፣ 26፣ ማርቆስ 14፣ 24) ማለት ነው፡፡  ለምሳሌ ያህል መጋቢ ዓለም ማለት በዝናብ አብቅሎ፣ በፀሐይ አብስሎ የሚመግብ ማለት ሲሆን፣ የመድሐኔ ዓለም ሌላኛው ስሙ ነው፡፡  
  8. ማዚያ (ሚያዚያ) ማለት የሙሽራና የሚዜ ወር ማለት ነው፡፡ 
  9. ግንቦት (ገነባ) ማለት ለክረምት የሚገነባበት (የሚዘጋጁበት) ጊዜ ማለት ነው፡፡  በግንቦት ወር አትጋቡ የሚባለው ደግሞ የግንቦት አየር ለጤና ተስማሚ ስላልሆና የግንቦት መናዝል (zodia) መንታ (Gemini) ስለሆነ ነው፡፡  ‹‹እንኳን ያንች ፍቅር ተጨምሮበት፣ እንደውም ሞቃት ነው ሰኔና ግንቦት›› እንዲሉ፡፡ 
  10. ሰኔ (ሠነየ) ማለት ሠናይ (ውብ፣ መልካም) ማለት ሲሆን፣ የእርሻ ማሳ ተተልሞ (ተገምሶ)፣ ታይሞ (ተቀብቅቦ)፣ እንዲለሰልስ መደረጉንና ዘር መዘራትን ያመለክታል፡፡  ‹‹ቀልደኛ ገበሬ በሰኔ ይሞታል›› እንዲሉ፡፡  ባገራችን በጦቢያ ተሸከርካሪን በግራ መንዳት ቀርቶ በቀኝ መንዳት የተጀመረው በኢትዮጵያ ዮማዝ (ኢዮ) ሰኞ፣ ሰኔ 1 ቀን፣ 1957 ዓ.ም ነበር፡፡ 
  11. ሐምሌ ማለት የልምላሜ (የሐመልማል፣ የቅጠል) ወር ማለት ነው፡፡ 
  12. ነሐሴ (ናሴ)፡፡  የዚህን ወር ትርጉም በትክክል ላውቀው አልቻልኩም፡፡  የቃሉ መሠረት ግን ነሐሰ (ነሐስን፣ መዳብን፣ ግንብን፣ መደብን) ሠራ የሚለው የግእዝ ግስ ስለሆነ፣ ነሐሴ ማለት ያመቱ መጨረሻ፣ ያመቱ ገደብ ማለት ሊሆን ይችላል፡፡  
  13. ጳጉሜ ማለት ደግሞ ተረፈ ዓመት፣ ጭማሪ፣ ተውሳክ ማለት ነው፡፡  ራሱ ፊደል ጰ ከፊደል ጸ የተገኘ ትርፍ ወይም ዲቃላ ፊደል ነው፡፡ 

የኢትዮጵያን ዮማዝ ከጥቅም ውጭ ለማድረግ የሚጣጣሩት ምሁር ነን ባዮች (በተለይም ደግሞ ኦነጋውያን) ከሚያቀርቧቸው የማታለያ ምክኒያቶች አንዱ ዮማዙ ዘመንን በትክክል ስለማይቆጥር የወቅቶች መዛባትን ያስከተላል የሚለው ነው፡፡  ይህ ችግር ግን የኢትዮጵያ ዮማዝ ብቻ ሳይሆን፣ የሁሉም የዓለማችን ዮማዞቸ ችግር ነው፡፡  እቅጭነትን (ማለትም እቅጩን መሆንን፣ precision) በተመለከተ ደግሞ የበለጠ እቅጭ (precise) የሆነው የፈረንጆቹ ጎርጎሮሳዊ ዮማዝ  (Gregorian calendar) ሳይሆን የፋርሶች ዮማዝ (Persian calendar) ነው፡፡  እንደ ሁሉም የዓለማችን ዮማዞች፣ የጦቢያ ዮማዝ ያለበትን የእቅጭነት (precision) ችግር ደግሞ በሚከተለው መንገድ በቀላሉ በማስተካከል ቢያንስ ቢያንስ ከጎርጎሮሳዊ ዮማዝ የበለጠ ትክክለኛ ማድረግ ይቻላል፡፡  

አንድ ዕለት (day) ማለት 24 ሰዓት ማለት ሲሆን፣ ምድር በዛቢያዋ ላይ አንድ ጊዜ ለመሾር (spin) የሚፈጅባት ጊዜ ነው::  አንድ ዓመት (year) ማለት ደግሞ ምድር በምሕዋሯ ላይ ፀሐይን አንድ ጊዜ ለመሖር (orbit) የሚፈጅባት ጊዜ ማለት ነው፡፡  የአንድ ዓመት እሴት እቅጩን (precisely) 365.24219 ዕለት ነው፡፡  በጦቢያ ዮማዝ መሠረት ደግሞ አንድ ዓመት 365.25 ዕለት ነው፡፡  ስለዚህም፣ የጦቢያ ዮማዝ በያንዳንዱ ዓመት

  365.25 ዕለት – 365.24219 ዕለት = 0.00781 ዕለት = 11.2464 ደቂቃ    

ይስታል ማለት ነው፡፡  በሌላ አባባል፣ የጦቢያ ዮማዝ በያንዳንዱ ዓመት ላይ በስሕተት 0.00781 ዕለት ወይም 11.2464 ደቂቃ ይጨምራል ማለት ነው፡፡ አሁንም በሌላ አባባል፣ የጦቢያ ዮማዝ በያንዳንዱ ዓመት ላይ በስሕተት 11 ደቂቃ ገደማ ወደኋላ ይቀራል ማለት ነው፡፡   ይህ ማለት ደግሞ የጦቢያ ዮማዝ በ 128 ዓመታት ውስጥ አንድ ዕለት (ማለትም 24 ሰዓት) ገደማ ወደኋላ ይቀራል ማለት ነው፡፡  

ስለዚህም፣ ከክርስቶስ ልደት በኋላ በ2014 ዓመታት ውስጥ የጦቢያ ዮማዝ 16 ዕለታት ገደማ በስሕተት ወደኋላ ቀርቷል ማለት ነው፡፡  ስለዚህም፣ 2014 ዓ.ም ላይ ሰኔ 18 መሆን የሚገባው ሰኔ 2 ይሆናል ማለት ነው፡፡  ይህ ስሕተት ደግሞ ወቅቶችን በማዛባት በተለይም በእርሻ ሥራ ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ ስለሚያሳድር በሚከተለው መንገድ በቀላሉ ሊታረም ይቻላል፡፡

  1. 2014 ዓ.ም ላይ ሰኔ 2 የሚባለውን ዕለት ሰኔ 18 ነው ብሎ በነጋሪት ማወጅ፡፡  በሌላ አባባል፣ ሰኔ 1 ካልን በኋላ ሰኔ 2 ማለት ትተን ሰኔ 18 ማለት፡፡  ይህን በማድረግ፣ ከክርስቶስ ልደት ጀምሮ የተከሰቱትን የዘመን አቆጣጠር ግድፈቶች ከሞላ ጎደል ሙሉ በሙሉ እናስተካክላለን፡፡ 
  2. ከ 2014 በኋላ ደግሞ በየ 128 ዓመት፣ ከቋጉሜ ወር ላይ አንድ ዕለት በመቀነስ አምስት ከሆነች አራት፣ አራት ከሆነች ደግሞ ሦስት እንድትሆን በነጋሪት ማወጅ፡፡  በሌላ አባባል የእጅ ሰዓት አቆጣጠሩን እንዳይስት በየሳንምንቱ እንደሚሞላ ሁሉ፣ ዮማዛችንም አቆጣጠሩን እንዳይስት በየ 128 ዓመት መሞላት አለበት፡፡    

እነዚህን ሁለት ቀላል ርምጃወች በመውሰድ ብቻ ኩራታችን የሆነውን የዘመን አቆጣጠራችንን አዘምነን ከፈረንጆች የዘመን አቆጣጠር የበለጠ ትክክልኛ እናደርገዋለን፡፡  ለትንሽ ለትልቁ መፍትሔ ለመሻት ወደ ምዕራባውያን ማማተር አፍሪቃን ለድቀትና ለንቀት ዳረጋት እንጅ ምንም አልጠቀማትም፡፡   ራሳችንን በራሳችን ካዋረድን ደግሞ ቢንቁን መከፋት የለብንም፣ ወደሽ ከተደፋሽ ቢገፉሽ አይክፋሽ ነውና፡፡  

የራሱን ንጹህ ጥብቆ፣ ራሱ ጥሎ አውልቆ

የሰው ቆሻሻ አጥልቆ፣ ተበክሎ ተጨመላልቆ፣

ሰው ተጸይፎት ርቆ፣ ሲሳለቅበት በሽቆ፣

ዙሮ እንባ ፈንጥቆ፣ እያለቀሰ ተነፋርቆ

ተናቅኩኝ ይላል ተንሰቀስቆ፣ ራሱን በራሱ አስንቆ፡፡

ምዕራባውያን አፍሪቃውያንን የሚንቁት ደግሞ ካፍሪቃውያን በሰረቁት መሆኑን ጊወርጊስ ያቆብ (George James) ‹‹የተሰረቀ ቅርስ፡ የግሪክ ፍልስፍና የተሰረቀ የኑባውያን ፍልስፍና ነው›› (Stolen Legacy: Greek Philolsophy is Stolen Egyptian Philosophy) በሚል ርዕስ በጻፈው ደንቅ መጽሐፉ ሊስተባበሉ በማይችሉ ማስረጃወች እያስደገፈ በሰፊው አብራርቶታል፡፡ 

ትናንት ጉግማንጉግ የነበረው አሕዛቡ ፈረንጅ

ዛሬ ስልጡን ነኝ ብሎ በሁሉም ዓይነት ፈርጅ

ቢንቅ ቢጸየፋችሁ አሳንሶ ከውሻ ልጅ፣ 

አዲስ በመፍጠር አይደለም አክብሮ በማንሳት እንጅ

ተንቆ የተጣለውን በናንተው ከናንተው ደጅ፡፡ 

Email: መስፍን አረጋ : mesfin.arega@gmail.com

Filed in: Amharic