>
5:13 pm - Friday April 20, 7883

እኛ የጣልነውን ፣ የናቅነውን ግእዝ ምእራባውያኑ እስከ ሁለተኛ ድግሪ ይመረቁበታል! (ሔቨን ዮሐንስ) 

– ጀርመኖች ግዕዝ የእነሱ ቋንቋ እስኪመስላቸው ድረስ ያውቁታል
– በካናዳ ቶሮንቶ ዮኒቨርስቲም ግዕዝ ቋንቋ ማስተማር ጀምሯል
ኢትዮጵያውያን የግላቸው ፊደላት አላቸው እንባላለን ። የምንኮራበት አንዱ ይሄ ነው ። አባቶቻችን የቀረፁልን ፊደል እጅጉን ያስደንቃል ። የእኛ የግላችን የምንለው በእራሳችን የምንተማመንበት ቋንቋና ፊደልን አስረከቡን ። በሰው ፊደል ተውሰን እንዳንፅፍ ። ሚስጥራችንን በእኛው ፊደል እንድንጠቀም እረድተውናል ። የእኛን ጠብቀው ካኖሩና ካጎለበቱ በሓላ ነው የሰው ሀገርን ቋንቋ ያስጠኑን ። እኛ ግን ሩቅ ተሻግረን የሰው ቋንቋን ፊደልን ስንጠቀም እንኮራለን እንጂ በእኛ አንኮራም ይሄ ግዜ የወለደው በሽታችን ነው ።
አባቶቻችን እጅጉን ጠቢብ ነበሩ ። ብዙ መፅሀፍትን ፅፈዋል ። 
ቆዳን አልፍተው ብራናን ሰርተው ከአፈር ከአለት ቀለምን አዘጋጅተው ብራናው ላይ የቀረፃቸውን  ፊደላት ሲያሰፍሩ ለእኛ ነበር ። የአለም ሚስጥራትን ሁሉ ያውቁ ነበር ። ብሩህ አእምሮም ነበራቸው ። ቤተ ክህነትን መንፈሳዊነትን ከአለም አቀናጅተው ሁለቱንም አስማምተው የኖሩ የተረጋጉ አባቶቻችንን ማክበርም መዘከርም ትተን ያስረከቡንንም እንደ ተራ ንቀን የሩቅ እንናፍቃለን ።
የኢትዮጵያ ፊደላትና የኢትዮጵያ ቋንቋ በሀገራችን ባይከበር በእጅ የያዙት ወርቅ እንደ መዳብ ቢቆጠርም በሌላ ሀገራት በሰለጠኑ ሀገራት እንደ እንቁ ይጠብቁትና ይጠቀሙበታልም ከታች ጀምረው እስከ ሁለተኛ ድግሪያቸው  ድረስ ይመረቁበታል ። ለዚህ ዋናዋ ምሳሌ ጀርመን ናት ። ጀርመኖች ግዕዝ የእነሱ ቋንቋ እስኪመስላቸው ድረስ ያውቁታል ። አማረኛን ያነባሉ ። እኛ ሀገር ግን አማረኛን የሚያነቡ የሚችሉት ከግማሽ በታች ያሉ ኢትዮጵያውያን ናቸው ። አሁን አሁን በደቡብ ክልል በኦሮሚያ ክልል ወዘተ የሚማሩት ፊደልን የሚቆጥሩት በሀገራቸው ቋንቋ ሳይሆን በላቲኑ ቋንቋ ነው ። ይሄ ጥሩ ያልሆነ ልፋት ነው ።
በካናዳ ቶሮንቶ ዮኒቨርስቲ ግዕዝ ቋንቋ ማስተማር ተጀመረ ።
ለዚህም ድጋፍ ኢትዮ ካናዳዊው ሙዚቀኛ አቤል ተስፋየ የብር ድጋፍ አድርጓል ። እርሱ እንኳን በውጭ አለም አብዝቶ የሚኖረው በነጮች የሚወደሰው ካናዳዊ የሆነው ወጣት ኢትዮጵያዊነቱን በሚችለው ቋንቋና ገንዘብ ይገልፃል ። ኢትዮጵያዊነት በደም ውስጥ ያለ ስሜት ነው እንዳሉ አቶ ለማ መገርሳ እርሱም ይህንን ያሳያል። ለዚህ ተመስጋኝ ያሳደገው ቤተሰብ ነው ። ኢትዮጵያን አሳውቆ ማሳደግ ጥሩ ነው ። ሩቅ ናፋቂ አድርጎ ማሳደግ ደግሞ ባዶነትን ብቻ ማውረስ እንደሆነ መገንዘብ ነው ።
የሀገራችን እንቁ ደራሲያኖች የመድረክ ባለሙያዎች የጥበብ ሰዎች መነሻ ቤተ-ክርስቲያን ናት ። ግዕዝን ታስጠናለች ። እዛ ዜማ አለ ልዩ ዜማ አጥንትን የሚያለመልም ተስፋ የሚሰጥ ፅርሃ አርያም ወስዶ ይቅርታን ለምኖ የሚመልስ ዜማ ይሄ ሁሉ በዚህ ፊደል ይዘወራል ። የኢትዮጵያ ትያትር ቤቶች ሳይጀመሩ ቅድመ አመታት የነበረች ቤተ ክህነት ጥበብም ተጠባ አቋቋምን ዜማን ግጥምን የተለያዩ ስነ ፁሁፍን በየ ነገስታቱ መድረክ በሰርግ በሀዘን እያስተጋባች ዛሬን ሰርታልን
ነበር ። ዛሬ ላይ ሆነን ትናንትን እንወቅሳለን እንጂ አመስጋኞች ለመሆን አልታደልንም ። ይባስ ብለን የእኛን ጥለናል ። እኛ የጣልነው የናቅነው ባለማወቅ ነው። ይህንን በደንብ አውቃለሁ ። ብዙ የሀገራችን ሚስጥራት በግዕዝ ታስረዋል ። ብዙ እውቀቶች በግዕዙ ተሸብበዋል ። እኛም ለማወቅ እደሉን አንጠቀምም ብቁም አይደለንም ስልቹዎች ነን ። የባህር ማዶ ሰዎች በእኛ መፅሀፍ የከፍታ ማማን ይዘዋል ። እኛ ባይሆንልን እንኳ እስኪ ልጆቻችንን እናብቃ ። እነሱ እንድያውቁ በርን እንክፈት።።።
Filed in: Amharic