>

በዶ/ር አብይ እውነት የማይመስለው እውን ሆነ- በርካታ ስደተኛ እስረኞች ተለቀቁ (አንተነህ ይግዛው)

በርካታ ስደተኛ እስረኞች ተለቀቁ

ኡምዱርማን ስጅን ሁዳ – ብዙ ህልም የታጎረበት የበረሃ ወህኒ

.(20 አመት ተፈርዶባቸው በሱዳን ስለሚማቅቁት ኢትዮጵያውያን)

. (አንተነህ ይግዛው)
“በሰቲት ሁመራ በገዳሪፍ ካርቱም
ጅቡቲ ኬንያ ያን ጊዜ ሳዘግም
በእግሬ ሳዘግም ብቻዬን ሳዘግም
በረሃ ሳቋርጥ በስደት ዘመቻ
የተከተለችኝ ባንዲራዬ ብቻ…”
              (ንዋይ ደበበ)
.
አሻግሬ አየዋለሁ…
እያየሁት እፈራለሁ፣ እሰጋለሁ፣ እጨነቃለሁ… ብዙ ነገር እሆናለሁ…
ያንን ባሻገር የሚታየኝን፣ የአገሬ ልጆች የታጎሩበትን፣ የአስጨናቂውን የኡምዱርማን ስጅን ሁዳን በር አልፌ ስለመግባቴ፣ ከእነ ኑር ሁሴን ጋር ስለመገናኘቴ፣ የአገሬን ልጆች ሰቆቃ ከአንደበታቸው ስለመስማቴ፣ ህልሜን ስለማሳካቴ እርግጥኛ አይደለሁም…
የእስር ቤቱን የመጀመሪያ ኬላ ከብበው የማያቸው፣ እነዚያ በቅርብ ርቀት የቆሙት አራት ኮስታራ ፖሊሶች፣ ወደ እስር ቤቱ የምገባበትን በር ሊከፍቱልኝ ፈቃደኛ ስለመሆናቸው እርግጠኛ አይደለሁም…
በቆምኩበት ሆኜ አሻግሬ እያየኋቸው፣ በፍርሃትና በስጋት ተሰቃየሁ…
አብረውኝ ተጉዘው እዚህ የደረሱት፣ ናስርና ሙስጠፋ ወደ ፖሊሶቹ እያዩ በአረብኛ ሲያወሩ ቆይተው፣ ወደመኪናችን ተመልሼ እንድገባ ነገሩኝ…
ደነገጥሁ!…
እነ ናስር ግን… ተረጋጋ እያሉኝ ነው…
እነሱ እንደኔ አይደሉም…
ስጅን ሁዳንም፣ የስጅን ሁዳን ፖሊሶችም፣ የፖሊሶችን ልብ ማራሪያውንም፣ ይሄን ኬላ አልፎ ገብቶ ከእስረኞች ጋር መገናኛውን ሁነኛ መላም… ሁሉንም ጠንቅቀው ያውቁታል…
ከፖሊሶቹ አንደኛው ከባልደረቦቹ ተነጥሎ ወደመኪናችን መጣ…
ኮስታራ ነው…
በመኪናዋ መስኮት ዝቅ ብሎ፣ ከናስር ጋር በአረብኛ ማውራት ጀመረ…
እየቃተትኩ የንግግራቸውን መጨረሻ ለማወቅ በጉጉት መጠበቅ ቀጠልኩ…
ብዙ አወሩ…
ናስር ወደኔ እየጠቆመ ለፖሊሱ የሚናገረው ነገር ባይገባኝም፣ ያስገባኝ ዘንድ እየለመነው እንደሆነ ከገጽታው ተረድቻለሁ…
ፖሊሱ አጎንብሶ ተመለከተኝ…
ፊቴን አሳዛኝ ለማድረግ ሞከርኩ…
እንደተኮሳተረ ሲያየኝ ቆይቶ፣ ወደ ናስር ዞር ብሎ የሆነ ነገር ነገረው…
በስተመጨረሻ…
ናስር ከኪሱ ሰማኒያ የሱዳን ፓውንድ አውጥቶ፣ አጣጥፎ ለፖሊሱ አስጨበጠው…
ኬላው ተከፈተ!…
በእፎይታ ተነፈስኩ!…
ተንፍሼ ሳልጨርስ ግን፣ ዋነኛው የእስር ቤቱ በር ከፊቴ ተገትሮ ጠበቀኝ…
ናስር እኔንና ሙስጠፋን መኪናችን ውስጥ ትቶ፣ ወደ በሩ በማምራት፣ እስረኞችን ለመጎብኘት ወረፋ ከሚጠብቀው ረጅም ሰልፍ ጋር ተቀላቀለ…
.
ከደቂቃዎች በኋላ…
ናስር ተራው ደርሶት ከጠባቂዎች ጋር ሲያወራ ቆይቶ፣ ወደቆምንበት ዘወር ብሎ በምልክት ጠራን፡፡
እሱ እና ሙስጠፋና የእሱን ወንድም ሊጠይቁ እንደመጡ፣ እኔ ደግሞ ኑር ሁሴንን ልጠይቅ እንደመጣሁ ለፖሊሶቹ ነግሯቸው፣ ስማችንንን አስመዘገበ፡፡
ፓስፖርቴንና ሞባይል ስልኬን ለዘቦቹ አስረክቤ፣ የሁዳን በር አልፌ ገባሁ!…
ወፍራሙ ፈታሽ በደረት ኪሴ የያዝኳቸውን አንዲት ብጣሽ ወረቀትና እስክርቢቶ ከጉዳይ አልጣፋቸውም!…
ደስ አለኝ!…
.
ይህ ስጅን አል ሁዳ ነው!…
10 ሺህ 500 እስረኞችን የመያዝ አቅም ያለውና፣ በአገረ ሱዳን በግዙፍነቱ አቻ የማይገኝለት የበረሃው ወህኒ – ስጅን አል ሁዳ ቅጽር ግቢ ውስጥ ነው ያለሁት!…
ናስርና ሙስጠፋን ተከትዬ፣ ግቢው መሃል ላይ ወደሚገኝ፣ አረንጓዴ ቀለም የተቀባ አዳራሽ አመራሁ፡፡ እስረኞች ከጠያቂዎቻቸው ጋር የሚገናኙበት ሰፋ ያለ አዳራሽ ነው፡፡ በሩን አልፈን ወደውስጥ ስንዘልቅ፣ ጨለም ያለና በእስረኛ ጠያቂ ሰዎች የተሞላ ሰፊ ክፍል ጠበቀን፡፡ ፊትለፊት ላይ፣ በብረት ፍርግርግ የታጠረ ሌላ ክፍል አለ፡፡
የጓጉ አይኖቼን በፍርግርጉ አሾልኬ ወረወርኳቸው፡፡ የብረት ወንፊት ላይ ተለጥፈው፣ ከጠያቂዎቻቸው ጋር የሚያወጉ፣ ነጫጭ ስስ ቱታ የለበሱ እስረኞች ይታዩኛል፡፡
ናስርን ተከትዬ፣ ጥግ ላይ ወደተቀመጠ ረጅም ፖሊስ አመራሁ…
ጠያቂዎችን እየተቀበለ፣ ሊጠይቁት የመጡትን ሰው የሚመዘግብና፣ እስረኞችን የሚያስጠራ ተረኛ ፖሊስ ነው፡፡
ጠረጴዛው ላይ አቀርቅሮ ሲጽፍ ቆየና፣ ኮስተር እንዳለ ቀና ብሎ አየን…
“አብዱላዚዝ ሸሪፍ…” አለው ናስር ወደ ፖሊሱ ጠጋ ብሎ፡፡
አብዱላዚዝ የ10 አመት እስር ተፈርዶበት በእስር ቤቱ ውስጥ የሚገኘው የናስር ታናሽ ወንድም ነው፡፡
ፖሊሱ ስሙን ወረቀት ላይ ጻፈና ወደኔ ዞረ…
ተናነቀኝ…
“ኑርሁሴን…” አልኩት እንደምንም እያቃተተትኩ፡፡
ፖሊሱ እስክርቢቶውን ወረቀቱ ላይ እንደተከለ በአረብኛ የሆነ ነገር ተናገረ…
“ኑርሁሴን…” አልኩት ደግሜ፡፡
በንዴት ጠረጴዛውን ደቃውና፣ ቀና ብሎ እያያኝ በንዴት ተናገረኝ…
በድንጋጤ ውሃ ሆንኩ…
ምን እያለኝ ነው?…
ናስር ጣልቃ ገብቶ ሊያረጋጋኝ ሞከረ…
“‘የኑርሁሴን የአባቱ ስም ማነው?’ ነው ያለህ…” አለኝ ወደኔ ዞሮ፡፡
አልመለስኩለትም!…
የሆነ ነገር ተናነቀኝ…
የአባቱን ስም እንደማላውቀው እየተንቀጠቀጥኩ ነገርኩት…
በአረብኛ ተርጉሞ ለፖሊሱ ነገረው…
ፖሊሱ የባሰ ተናደደና ከናስር ጋር መጨቃጨቁን ቀጠለ…
ጭቅጭቁ ተባባሰ…
በኋላ እንደገባኝ ከሆነ፣ እንዴት የሚጠይቀውን እስረኛ ሰው ስም እንኳን ጠንቅቆ አያውቅም በሚል ነበር ፖሊሱ በእኔ የተናደደው…
እየለፈለፈ ወረቀቱን ይዞ ከተቀመጠበት ተነሳ… ናስር ተከተለው…
“ምንድን ነው?…” ስል በሹክሹክታ ጠየቅኩት ናስርን፣ በጭንቀት ተውጬ፡፡
በጫትና በሃሺሽ የታሰሩትን እስረኞች መጎብኘት የሚቻለው ማክሰኞና እሁድ ብቻ ስለሆነ፣ አብዱላዚዝንም ሆነ ኑር ሁሴንን መጠየቅ አትችሉም እንዳለው ነገረኝ…
ተስፋዬ ድራሹ ሲጠፋ ተሰማኝ…
ናስር ግን፣ እንድረጋጋ ነግሮኝ፣ ኪሱን እየደባበሰ ፈጠን ብሎ ፖሊሱን ተለከተለው…
በቆምኩበት ሆኜ በአይኔ ተከተልኳቸው…
የሆኑ ፓውንዶች አጣጥፎ የያዘው የናስር ቀኝ እጅ፣ የፖሊሱን መዳፍ አስፈለቀቀው…
ፖሊሱ ከእጁ ጋር ፊቱ ተፈታ…
በጠባቧ በር አልፎ ወደ ውስጥ ገባ…
“ሊጠራልን ነው!…” አለኝ ናስር ፈገግ ብሎ እያየኝ፡፡
.
እጠብቃለሁ…
ከሰው አገር ሰው መሃል፣ ቁጭ ብዬ የራሴን ሰው እጠብቃለሁ…
አግዳሚ ወንበር ላይ ተቀምጬ፣ ከብረት ፍርግርግ ማዶ፣ አንድ ሰው እማትራለሁ…
በቫይበር ሳወጋው ያመሸሁትን፣ ወጌን ያላስጨረሰኝን፣ ሳይሰናበተኝ ከቫይበር ወጥቶ የቀረውን፣ በፎቶ ግራፍ እንጂ በአካል የማላውቀውን፣ የወንዜን ልጅ የኑር ሁሴንን የተጎሳቆለ ፊት፣ ከብረት ወንፊት በስተጀርባ አሻግሬ አስሳለሁ…
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ…
የብረት ወንፊት ላይ ከወዲያ ወዲህ የሚንገዋለሉ… ግራ ገብቷቸው ግራና ቀኝ የሚንከባለሉ… የሚፈሩ፣ የሚጠራጠሩ የሚሰጉ፣ ተስፋ የሚያደርጉ… የተደነባበሩ ጥንድ አይኖች፣ አይኔ ውስጥ ገቡ…
ፈጥኜ ተነስቼ የብረት አጥሩ ላይ ተለጠፍኩ…
“ኑር ሁሴን ነህ?…” ስል በጉጉት ጠየቅኩት፡፡
ፈጥኖ አልመለሰልኝም…
ምክንያቱም፣ እየሆነ ያለው ሁሉ ሆኖ እሚያውቅ አይደለም፡፡
እዚህ የመከራ ግቢ ውስጥ ከገባባት ከዚያች የተረገመች ቀን ወዲህ፣ ከእስረኞችና ከእስረኛ ጠባቂ ፖሊሶች በስተቀር፣ አንድ እንኳን ሰው ስሙን ጠርቶት አያውቅም፡፡ ላለፉት ከሶስት በላይ አመታት፣ ወግ ደርሶት ወዲህ ወደ መጎብኛው ክፍል ተጠርቶ አያውቅም ነበር፡፡
ደህንነቱን የሚጠይቅ ዘመድ ወዳጅ ጓደኛ፣ ወደእሱ መጥቶ አያውቅም ነበር – በአንድ ወቅት ከጎበኙት፣ አሁን በህይወት የሌሉት አባቱ በቀር፡፡ የተቀረው አለም ሁሉ፣ ረስቶ ትቶኛል፣ ወደ መጎብኛው ክፍል የሚያስጠራኝ ሰው አይኖርም ብሎ ደምድሞ ነበር (በኋላ ላይ እንዳጫወተኝ)፡፡
ኑር ሁሴን ዝም ብሎ አየኝ…
ድንገት ከተፍ ብሎ ስሙን ለሚጠራው ሰው፣ ድንገት ፈጠን ብሎ መልስ የሚሰጥበት ሁኔታ ላይ አልነበረም፡፡
ትናንት በቫይበር ሳወራው የነበርሁት ሰው እንደሆንኩ ነገርኩት…
“እዚህ ድረስ ትመጣለህ ብዬ አላሰብኩም ነበር!… ሰላም ነህ?…” አለኝ ኑር ሁሴን፣ በፍርግርጉ ውስጥ እያየኝ፡፡
ከምን እንደምጀምር ግራ ገብቶኛል…
“ኑሮ እንዴት ነው?…” አልኩት፡፡
ፈገግ አለ…
ፈገግታው ውስጥ ብዙ ነገር አለ…
ያንን ብዙ ነገር፣ በብረት ወንፊት እያጠለለ፣ ወደ ጆሮዎቼ አንቆረቆረው…
.
ኑርሁሴን በሪሁ ሰኢድ…
አዲስ አበባ ተወልዶ ያደገው፣ አብነት ተብሎ የሚጠራው ሰፈር ውስጥ በልብስ ስፌት ስራ ሲተዳደር የነበረው፣ የተሻለ ገቢ የማግኘት ህልም ሰንቆ ወደ ስደት የወጣው ኑርሁሴን…
ከሶስት አመታት በፊት በጎንደር አድርጎ፣ በሁመራ በኩል ወደ ሱዳን ሊሻገር ሲነሳ፣ ተስፋን ሰንቆ ነበር፡፡ ብዙ ፈተና ቢገጥመውም፣ ባሻገር የተሻለ ነገር እንደሚያገኝ ተስፋ አድርጎ ነበር፡፡ ህልሙም ጉዞውም ሩቅ ነበር፡፡ ወደህልሙ የጀመረው ጉዞ እውን ይሆን ዘንድ፣ ብዙ ነገር ከፍሎ ነበር፡፡
ብዙ ነገር የከፈለለት ጉዞው ግን፣ እንዳሰበው የተሸለ ነገር ላይ አላደረሰውም፡፡ ከሁመራ አቅራቢያ በምትገኘው ሉግዲ የተባለች የድንበር ከተማ ላይ ተቋጨ፡፡ ለቀጣዩ ጉዞ ሲዘገጃጅ ባለበት፣ ስደተኛን አነፍንፈው መያዝና ወደ ወህኒ መወርወር የማይታክታቸው የሱዳን ፖሊሶች፣   ድንገት ከተፍ ብለው ያዙት፡፡ ወደ ህልሙ ትተው፣ ወደ ገዳሪፍ አጋዙት፡፡
በብዙዎች ላይ የጭካኔ ፍርድን በማሳተላለፍ የሚታወቀው የገዳሪፍ ፍርድ ቤትም፣ በጫት መቃም ወንጀል ተከስሶ የቀረበለትን ይሄን መንገደኛ፣ ያለ ርህራሄ የአስር አመታት እስር ቅጣት አስተላለፈበት፡፡ ከወንጀሉ ነጻ ነኝ ብሎ ያስተባብልበት ቋንቋም ሆነ ዕድል አልነበረውም፡፡ ጠበቃ ቀጥሮ ይከራከርበትና ይግባኝ ይልበት አቅም አልታደለውም፡፡ ጎትተው ከዳኛው ፊት ያቀረቡት ፖሊሶች፣ ጎትተው ወደ ወህኒ ወሰዱት – የመከራን ገፈት ይቀምስ ዘንድ በገዳሪፍ እስር ቤት ጣሉት፡፡
ኑርሁሴን ስቃይን አያት፡፡ መከራን ቀመሳት፡፡
ከጊዜያት በኋላ…
የተሻለ ስቃይ ወዳለበት፣ ድረሱልኝ ቢል ሰሚ ያገኝበት ወደመሰለው ወደ ስጅን አልሁዳ እስር ቤት መዛወር የሚችልበትን ዕድል ለማግኘት ደፋ ቀና ማለት ጀመረ፡፡ ይህን ዕድል የሚፈጥርለት ደግሞ ገንዘብና ገንዘብ ብቻ እንደሆነ ገብቶታል፡፡ እንደምንም ደክሞ፣ ለወህኒው ፖሊሶች ጠቀም ያለ ገንዘብ ከፍሎ፣ ተሳካለትና ወዲህ ወደ ስጅን ሁዳ ተዛወረ፡፡
ገንዘብ ከፍሎ የገባበት ስጅን አል ሁዳ ግን፣ ይሄው ለአመታት ከፍሎ እማይጨርሰው ፍዳ ሲያስቆጥረው አለ…
“ኑሮ እንዴት ነው?…” ለሚለው ጥያቄዬ በሰጠኝ የፈገግታ መልስ ውስጥ የተቋጠረ፣ ብዙ ነገር አለ፡፡
እዚህ ፈገግታው ውስጥ፣ የማይጥመው የስጅን አል ሁዳ “ገራ” አለ፡፡
ገራ እህል እህል የማይል የዱባ ወጥ ነው፡፡
ስጅን አል ሁዳ ለኑርሁሴንና ጓዶቹ፣ ይሄን ምን ቢራቡ ወደአፍ የማያደርሱት ዘግናኝ የዱባ ወጥና ስድስት ዳቦ ነው፣ ለእለት ጉርሳቸው የሚወረውርላቸው፡፡
ስጅን አል ሁዳ ከማቅረቡ እንጂ ከመብላታቸው ጉዳይ የለውም፡፡ በርሃብ ቢሰቃዩም፣ በውሃ ጥም ቢቃጠሉም፣ በህመም ቢቃትቱም፣ እዬዬ ቢሉም፣ ተንጠራውዘው ቢሞቱም ዴንታ የለውም፡፡ የሞተው ይሞታል፤ በተአምር የተረፈውም ይተርፋል – ልክ እንደ አብዱላዚዝ፡፡
ደጋግመው በህመም ሲቃትቱ፣ ከጉዳይ ይጥፋቸው፣ ደግፎ ያሳክማቸው ረዳት አጥተው ሲሰቃዩ ከርመው፣ በተአምር ከሞት ከተረፉት በርካታ የግቢው ታሳሪዎች አንዱ ነው  – የጅማው ልጅ አብዱልአዚዝ ሸሪፍ (የመንገድ መሪዬ የናስር ታናሽ ወንድም)፡፡
ይሄ ከብረት ፍርግርጉ ጀርባ ቆሞ የሚያወራኝ ቅስሙ ተሰብሮ ያጎበጠ ሰው፣ የ24 አመት ወጣት ነው ብዬ ለማመን ቸግሮኛል፡፡ የእስር ቤቱ ስቃይና መከራ ያለዕድሜው ያስረጀው አብዱልአዚዝ፣ ከ4 አመት በፊት ነበር፣ ከኦሮምያ ክልል ጅማ ዞን ኦሞ ናዳ ወረዳ ተነስቶ፣ ብዙ ብር ከፍሎ በህገወጥ ደላሎች አማካይነት በገዳሪፍ በኩል ሱዳን የገባው – በሊቢያ በኩል ወደ ጣሊያን ለመሻገር አስቦ፡፡
ወደሊቢያ ለመሻገር ዝግጅት ሲያደርግ ሳለ ግን፣ በጫት መቃም ወንጀል ተከስሶ 20 አመት እስር ተቀጥቶ ወህኒ ወረደ፡፡
ይሄው ላለፉት አራት አመታት በአል ሁዳ እስር ቤት መከራውን ያያል፡፡
“የሚገጥመንን መከራ ምን ብዬ እንደምገልጽልህ አላውቅም!… ሙቀቱ እጅግ አስቸጋሪ ነው!… የሚሰጠን ምግብም ለመመገብ አስቸጋሪ ነው፡፡ በተለያዩ በሽታዎች እንያዛለን፡፡ በተለይ እኛ ኢትዮጵያውያን እስረኞችን፣ ከሰው የሚቆጥረን የለም!… ያሰቃዩናል!… ከሌሎች እስረኞችም ሆነ ከፖሊሶች ጋር መግባባት አልቻልንም፣ ስንታመም እንኳን አሳክሙን ብለን ለመናገር የቋንቋ ችግር አለብን!… ስንቱን ልነግርህ!?…” አለኝ አብዱላዚዝ አይኖቹ እንባ አቅርረው፡፡
.
አብዱላዚዝ እውነቱን ነው!…
የወንዜ ልጆች እዚህ አል ሁዳ የሚያስተናግዱት መከራ… ተነግሮም፣ ተሰምቶም አያልቅም…
ሁሉም የጋራ ስቃይ ላይ የሚቋጭ፣ የየግል አሳዛኝ ታሪክ አለው….
መሃሪም አልሁዳ ግቢ ውስጥ ኩርምት ብሎ የሚተርከው የራሱ ታሪክ አለው…
ልክ እንደ አገሩ ልጅ እንደ ኑር ሁሴን ሁሉ፣ ለፖሊሶች ገንዘብ ከፍሎ ከገዳሪፍ ወደ አል ሁዳ የተዘዋወረ ኢትዮጵያዊ እስረኛ ነው – መሃሪ ሆጎስ፡፡
ነዋሪነቱ በመተማ ዮሃንስ ከተማ የነበረውና በእርሻና በንግድ ስራ ይተዳደር የነበረው መሃሪ ሃጎስ፣ የእርሻ መሳርያዎችና የመለዋወጫ ዕቃዎችን ወደ ገዳሪፍ እየወሰደ ይነግድ ነበር፡፡
ከኣራት ዓመታት በፊት ግን…
አንድ ምሽት፣ ገዳሪፍ ላይ ድንገት በሱዳን ፖሊሶች እጅ ላይ ወደቀ፡፡
በ2004 ዓ.ም፣ በመጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ…
መሃሪ የተመለደ የንግድ ስራውን ለመከወን በማሰብ፣ ከሚኖርባት መተማ ዮሃንስ ከተማ በ155 ኪ.ሜ ርቃ ወደምትገኘው የሱዳኗ ገዳሪፍ ከተማ አቀና፡፡ ለሁለት ሳምንታት ያህልም፣ መንጢጋ ሲናዕያ ተብሎ በሚጠራው የገዳሪፍ የንግድ መንደር ውስጥ ስራውን ሲያከናውን ቆዬ፡፡
በስተመጨረሻም ስራውን አጠናቅቆ፣ ወደ አገሩ ለመመለስ ተሰናዳ፡፡ እንደ ነገ ጧት ወደአገሩ ሊጓዝ አስቦ፣ ማታውን እዚያው ገዳሪፍ የሚኖር ወንድሙ ቤት ውስጥ እያለ ያልጠበቀው ነገር ገጠመው፡፡
በንግድ ስራ የሚያውቀው አንድ ሱዳናዊ ወዳጁ በምሽት ስልክ ደወለለት፡፡ ለአስቸኳይ ጉዳይ እንደሚፈልገውና በአቅራቢያው ከሚገኝ ቦታ ላይ እየጠበቀው እንደሆነ ነገረው፡፡፡ ክፉ ነገር ይጠብቀኛል ብሎ ያልገመተው መሃሪም፣ በምሽት ከወንድሙ ቤት ወጥቶ ወደደወለለት ሰው ሄደ፡፡ ሱዳናዊው ከፖሊሶች ጋር ሆኖ ነበር የጠበቀው፡፡
በፖሊሶች ቁጥጥር ስር መዋሉ ተነገረው፡፡
“ምን አጥፍቼ?…” ሲል ጠየቀ መሃሪ ተደናግጦ፡፡
ጋንጃ ተብሎ የሚጠራውን አደንዛዥ ዕጽ ታዘዋውራለህ ተባለ፡፡
ስለሚባለው ነገር ምንም እንደማያውቅና በወንጀሉ ውስጥ እንደሌለበት የነገረኝ መሃሪ፣ በወቅቱ በወንጀሉ አለመሳተፉን በመግለጽ ሊያስተባብል ቢሞክርም፣ ሰሚ እንዳላገኘ አጫውቶኛል፡፡
እያዋከቡና እያዳፉ በጨለማ ወደ አንድ የምርመራ ክፍል ወሰዱት፡፡
ወንጀሉን ፈጽሚያለሁ ብሎ እንዲያምን ሲደበድቡት አድረው ዋሉ፡፡
መጋቢት 25 ቀን ንጋት ላይ፣  “ጊስም አል-አውስጥ” ወደሚባለው የገዳሪፍ ፖሊስ ጣብያ ወስደው እንደጣሉት የሚናገረው መሃሪ፣ እናቱ በስጦታ መልክ ያበረከቱለትን የወርቅ ሃብልና የብር የእጅ አምባር በፖሊሶቹ ተነጥቆ፣ ከእስር ቤቱ በር ጋር በቁሙ ታስሮ እንዳደረ በምሬት ተርኮልኛል፡፡ ለቀናት ያለ ምግብና ውሃ በሱዳን ፖሊሶች ድብደባና ስቃይ ሲፈጸምበት መቆየቱንም ነግሮኛል፡፡
የመሃሪ ስቃይ ቀጥሏል፡፡ እጆቹ እስኪሰበሩ በዕየለቱ ተደብድቧል፡፡ በርሃብና በውሃ ጥም ተብገላትቷል፡፡ ስፍር ቁጥር የሌለው መከራን አስተናግዷል፡፡
በስተመጨረሻም…
በፖሊስ ቁጥጥር ስር በዋለ በ77ኛው ቀን፣ ሰኔ 10 ቀን 2004 ዓ.ም…
ጉዳዩን ሲመረምር የቆየው ፍርድ ቤት፣ የሰራ አካላቱ በድብደባ የተሰባበረውንና ቁስሉ ያልጠገገውን መሃሪን፣ የ20 አመታት እስር አከናንቦ ወህኒ እንዲወረወር ፈረደበት፡፡
ምንም ምርጫ የለውም መሃሪ – እያነከሰ፣ እያለቀሰ መራሩን የገዳሪፍ እስር ቤት ህይወት ተቀላቀለ…
.
መሃሪ የገዳሪፍ ወህኒን ሰቆቃ ሲያስታውስ በምሬት ነው…
“በገዳሪፍ እስር ቤት ያየሁትን መከራ በቃላት አልገልጸውም!… በድብደባ የሰራ አካላቴ ደቅቆና ቆስዬ ስገባ፣ ያለርህራሄ ነበር የእግር ብረት ያጠለቁልኝ፡፡ ገዳሪፍ ወህኒ ግቢው ትንሽ ስለሆነና ከባድ ፍርደኛ ያመልጥብናል ብለው ስለሚሰጉ፣ ተፈርዶብህ እንደገባህ ነው በእግር ብረት የሚያስሩህ፡፡ የእግር ብረቱ 5 ኪሎ ግራም የሚመዝን ነው፡፡ በሁለቱ እግሮችህ መሃል የእንድ ጫማ ክፍተት ብቻ እንዲቀር አድርገው፣ አጥብቀው ያስሩሃል፡፡
“እግርህ መድማትና መቁሰል ይቅርና፣ ቢበሰብስም ኣይፈታልህም፡፡ እኔም  እግሬ ብረቱን መቋቋም አቅቶት ቆስሎ ደም እየፈሰሰኝ እያዩ እንኳን፣ አዝነው ሊፈቱልኝ አልፈቀዱም፡፡ እያለቀስኩ ብለምናቸው፣ ‘እግርህ ቢቆረጥም ኣንፈታልህም!…’ ብለው እርሜን ነገሩኝ፡፡ የታሰርኩበት እግር ብረት፣ ለ11 ወራት አልወለቀልኝም ነበር…” ይላል መሃሪ የገዳሪፍ እስር ቤት ሰቆቃውን በምሬት እያስታወሰ፡፡
መሃሪ ለአመታት መገዳሪፍ እስር ቤት አሳር መከራውን ሲያይ ቆዬ…
በስተመጨረሻም፣ የተሻለ መከራ ወዳለበት ሌላ እስር ቤት መዛወር የሚችልበትን አጋጣሚ ለመፍጠር ደፋ ቀና ማለት ጀመረ፡፡ ከ3 አመታት በፊትም፣ ተሳካለትና 900 የሱዳን ፓውንድ ከፍሎ፣ አሁን ወደሚገኝበት ስጅን አል ሁዳ መዛወር ቻለ፡፡
“ወደስጅን አል ሁዳ ለመምጣት ያሰብኩት፣ በተለያዩ ምክንያቶች ነው፡፡ አንደኛ ነገር ይሄኛው ግቢ ሰፊ ስለሆነና ጥበቃውም አስተማማኝ ስለሆነ፣ ታመልጣለህ ተብሎ ስለማይሰጋ፣ የሞት ፍርደኛ ካልሆንክ በስተቀር፣ እንደ ከገዳሪፍ በእግር ብረት አትታሰርም፡፡ ስለዚህ ቢያንስ ከእግር ብረቱ ስቃይ መገላገል እንደምችል ገብቶኛል፡፡
“ሌላው ደግሞ፣ ይሄኛው እስር ቤት በሱዳን የኢትዮጵያ ኢምባሲ ለሚገኝበት አካባቢ ቅርብ ስለሆነ፣ ያለወንጀሌ መታሰሬን ለኢምባሲ ገልጬ፣ የአገሬ መንግስት ነጻ የምወጣበትን መንገድ ይፈልግልኛል ብዬ ተስፋ በማድረግ ነበር፣ ገንዘብ ከፍዬ ከገዳሪፍ ወደዚህ የተዛወርኩት…” ይላል መሃሪ፡፡
መሃሪ ብቻም አይደለም፤ ኑር ሁሴንና በስጅን አልሁዳ ታጉረው የመከራን ጽዋ የሚጎነጩት ሌሎች ኢትዮጵያውያን ስደተኞችም፣ ከዚህ የመከራ ግቢ ይገላግለናል ብለው ተስፋ ያደረጉበት ኢምባሲውን ነበር…
.
“ተስፋ አድርገን ነበር…” አለኝ ኑር ሁሴን ከፍርግርግ ብረቱ ጀርባ አቀርቅሮ እየተከዘ፡፡
“እዚህ ግቢ የገባሁ ሰሞን፣ የኢትዮጵያ ኢምባሲ ሰዎች መጥተው ጎብኝተውን ነበር፡፡ የታሰርንበትን ጉዳይ በተመለከተ ጠይቀውን ነበር፡፡ በሃሽሽ የታሰሩትን በተመለከተ ምንም ማድረግ ባይችሉም፣ ‘በጫት የታሰራችሁትን ግን ለማስፈታት ጥረት እናደርጋለን’ ብለው ተስፋ ሰጥተውን ነበር፡፡ እኛም ተስፋ አድርገን እየጠበቅናቸው ነበር፡፡ በአመት አንዴ ጎራ ብለው ከመጎብኘትና የማያልቅ ተስፋ ከመስጠት በቀር ግን፣ አንዳችም ነገር አላደረጉልንም!… ያም ሆኖ ግን፣ አሁንም ከኢምባሲያችን ውጭ ተስፋ የምናደርገው ነገር የለም!…” አለኝ ኑር ሁሴን አይኖቹ እምባ አቅርረው፡፡
.
እዚያው ነኝ…
የወንዜ ልጆች ታጉረው የሚሰቃዩበት አስከፊ ቅጽር ግቢ – ስጅን አል ሁዳ ውስጥ…
በሱዳን ግዙፉ ወህኒ የሆነው የስጅን አል ሁዳ ቅጽር ግቢ፣ በሰባት ንኡስ ግቢዎች የተከፋፈለ ሲሆን፣ በእያንዳንዱ ግቢ ውስጥም 20 ሰፋፊ የእስረኞች መኖሪያ ክፍሎች ይገኛሉ፡፡ በድምሩ 140 ክፍሎች ማለት ነው፡፡ በአንዱ ክፍል ውስጥ 25 ባለ ሶስት ተደራራቢ አልጋዎች ያሉ ሲሆን፣ በክፍሉ ውስጥ 75 እስረኞች ይኖራሉ፡፡
20 አመት ተፈርዶበት በስጅን አል ሁዳ እስር ቤት የሚገኘው መሃሪ ሃጎስ እንደነገረኝ፣ በአልሁዳ  ብቻ ከ10 እስከ 20 አመት የሚደርስ ከባድ ፍርድ ተፈርዶባቸው የሚሰቃዩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች 51 ያህል ናቸው፡፡ ከእነዚህ በተጨማሪ በፖርት ሱዳን 14፣ በከሰላ 1፣ በገዳሪፍና መደኒ ደግሞ ሌሎች ቁጥራቸው በውል የማይታወቁ ከባድ ፍርደኞች አሉ፡፡
ስሙን እንዳልጠቅስ በመግለጽ በዚሁ ግቢ ታስሮ እንደነበር ያጫወተኝ ሌላ ኢትዮጵያዊ ስደተኛ በበኩሉ፣ በግቢው ውስጥ ከታሰሩት ኢትዮጵያውያን፣ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ወንጀል ሰርተው የተገኙ እንዳሉ ሁሉ፣ ያለስራቸው በማያውቁት ነገር ከተገኙበት ታፍሰው ወደ እስር ቤት የተወረወሩም ብዙ ናቸው፡፡
ከወንጀል ነጻ መሆናቸውን ለማስረዳትና ፍርድ ቤት ቆመው ለመከራከር ይቅርና፣ ስለተከሰሱበት ወንጀል በቂ ግንዛቤ ለማግኘት የቋንቋ ችግር ኖሮባቸው እንደዋዛ አስርና ሃያ አመት የተፈረደባቸው ኢትዮጵያውያን እንዳሉ የገለጸልኝ ግለሰቡ፣ ከፖሊሶች ብቻ ሳይሆን ከሱዳናውያን እስረኞች ድብደባ፣ ዝርፊያና ሌሎች አሰቃቂ ግፎች እንደሚፈጸሙባቸው ነግሮኛል፡፡
“የስጅን አል ሁዳ ህይወት እጅግ መራርና ሞትን የሚያስመኝ ነው፡፡ ከንጋቱ 11 ሰዓት ላይ ለቆጠራ ይቀሰቅሱሃል፡፡ ከዘገየህ በጭካኔ ይደበድቡሃል፡፡ ይሰድቡሃል፡፡ ለቀን የሚሰጥህ 7 ዳቦ ብቻ ነው፡፡ ያንን አቻችለህ መጠቀም አለብህ፡፡ ጠዋት አንድ ጭልፋ ፉል ይሰጥሐል፤ ከቀኑ ዘጠኝ ሰአት አንድ ጭልፋ የዱባ ወጥ ይጨመርልሃል፡፡ ምግቡ ለመመገብ የሚያስቸግር ነው፡፡ ከዛውጭ ገንዘብ ካለህ በራስህ ነው የምትመገበው፡፡ የምትጠጣው ውሃ እጅግ ጨዋማ ከመሆኑ የተነሳ፣ ለኩላሊት ህመም ያጋልጥሃል፡፡ እኔም በዚህ ውሃ ሳቢያ ለከፋ የኩላሊት ህመም ተዳርጊያለሁ፡፡
“የፖሊሶቹ ጭካኔ በተለይ በኢትዮጵያውያን እስረኞች ላይ ያይላል፡፡ ፖሊሶቹ ትንሽ ጥፋት ካገኙብህ፣ ለመግረፊያ ባዘጋጁት አልጋ ላይ በሆድህ ያስተኙሃል፡፡ እግርህም እጅህም ይታሰራል፡፡ ሱሪህን ወደታች ያወርዱና መቀመጫህ ላይ በውሃ የተነከረ ብጫቂ ጨርቅ ያደርጉና በላዩ ላይ ደቃቅ ጨው ይነሰንሱበታል፡፡ ከዚያም በጉማሬ አለንጋ 25 ጊዜ ይገርፉሃል፡፡ ስጋህ ሲነሳና ከጨው ጋር ሲገናኝ፣ ምን ያህል ህመም እዳለው ለመግለጽ ያቅተኛል፡፡ እጅግ አሰቃቂ ነው!…
“በስጅን አል ሁዳ በጫትና በሃሺሽ ረጅም አመር ተፈርዶባቸው የታሰሩና፣ ተስፋ የቆረጡ ብዙ ሐበሾች አሉ፡፡ እነሱን ማየት በራሱ ያሳብዳል፡፡ ቁጥራቸው ትንሽ የማይባል ደሞ፣ በግድያ ወንጀል ተከሰውና ተፈርዶባቸው የታሰሩ አሉ፡፡ እነዚህኞቹ የእስር ጊዜያቸውን ቢጨርሱ እንኳን፣ በአገሪቱ ህግ መሰረት ከወህኒው ለመውጣት ለሟች ቤተሰቦች አርባ ሺህ የሱዳን ፓውንድ በካሳ መልክ መክፈል ይጠበቅባቸዋል፡፡ የመክፈል አቅም ከሌላቸው እድሜ ልካቸውን ከወህኒው አይወጡም፡፡ መሰል ችግር የገጠማቸው በርካታ ኢትዮጵያውያን አሉ፡፡” ብሎኛል ግለሰቡ፡፡
.
አሁንም በስጅን አል ሁዳ የስቃይ ህይወትን በመግፋት ላይ የሚገኘው መሃሪ ሃጎስ፣ በኢትዮጵያውያን እስረኞች ላይ የሚደርሰውን ግፋና በደል ቢቆጥሩት አያልቅም ይላል፡፡
“ለምሳሌ…” ይላል መሃሪ…
“ለምሳሌ… በህገ ወጥ መንገድ ወደ ሱዳን ገብታችኋል በሚል ተከሰው በ2005 መጨረሻ ወደ እስር ቤቱ የገቡና፣ የእስር ጊዜያቸውን አጠናቅቀውና የገንዘብ ቅጣት ከፍለው ወደ ኢትዮጵያ ሊመለሱ የተዘጋጁት ስደተኞች ነበሩ፡፡ እንደ ነገ ጠዋት ወደ አገራቸው ሊመለሱ፣ ምሽቱን ሁለቱ ኢትዮጵያውያን፣ በሱዳናውያን የግብረ ሰዶም ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል፡፡”
ሌላም የሚያስታውሰው ግፍ አለው – መሃሪ፡፡
“በ2006 ዓ.ም ግንቦት ወር ላይ ደግሞ፣ በአንድ ቀን ብቻ በህገወጥ መንገድ ወደ ሱዳን ገብተዋል የተባሉ ከ400 በላይ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ስደተኞች ወደ ስጅን አል ሁዳ ገብተው በጠባብ ክፍል ውስጥ ታጉረዋል፡፡ እነዚህ እስረኞች ለ3 ቀናት ያህል ውሃ አልተሰጣቸውም ነበር፡፡
“በሶስተኛው ቀን ንጋት ላይ፣ እስረኛ ቆጣሪው የፖሊስ መኮንን ወደ ክፍሉ ሲገባ፣ ከ30 በላይ የሚሆኑት በውሃ ጥምና በሙቀት ሳቢያ ራሳቸውን ስተው ወለል ላይ ወድቀው ነበር ያገኛቸው፡፡ አስራ ስምንቱ ቀላል የህክምና እርዳታ ተደርጎላቸው ተሸሏቸው ወደ ግቢው ሲመለሱ፣ ሶስቱ ኢትዮጵያውያን ሞቱ፡፡ የቀሩት ወደ 12 የሚሆኑ እስረኞች፣ ለተሻለ የህክምና እርዳታ፣ መሃል ካርቱም ወደሚገኘው ‘መስተሸፋ አል – ሹርጣ’ የተባለ ሆስፒታል ቢወሰዱም፣ ዳግም ወደ እስር ቤቱ አልተመለሱም!… የት እንደገቡ የታወቀ ነገር የለም!…” ይላል መሃሪ ሁኔታውን በሃዘን እያስታወሰ፡፡
እርግጥም ኢትዮጵያውያኑ በስጅን አል ሁዳ የሚገጥማቸው መከራ የትየለሌ ነው፡፡
ወደ እስር ቤቱ ሲገቡ ሃብልና ቀለበታቸውን፣ ገንዘብና ልብሶቻቸውን ይዘረፋሉ፡፡ በአንድ ምላጭ ለሁለት ይላጫሉ፡፡ የግብረ ሰዶም ጥቃት ይፈጸምባቸዋል፡፡ ከባህልና ከሃይማኖታቸው ጋር የማይጣጣም ድርጊት እንዲፈጽሙ ይገደዳሉ፡፡ ስነ-ልቦናዊ ጫና ይደረግባቸዋል፡፡ ብዙ ብዙ በደል ይደርስባቸዋል፡፡
ይሄን ሁሉ በደል ችለው ማስተናገድ እንጂ፣ በደላቸውን ለእስር ቤቱ ሃላፊዎች ተናግረው መላ የማግኘት መብትም፣ ዕድልም የላቸውም፡፡
አሁንም እዚያው ነኝ…
የማያልቀውን የወንዜ ልጆች ምሬት እያደመጥኩ…
.
(ይቀጥላል)
Filed in: Amharic