>

የድሬ ዳዋ በረከቶች...!!! (አፈንዲ ሙተቂ)

የድሬ ዳዋ በረከቶች…!!!

አፈንዲ ሙተቂ

   አዎን! ድሬ ዳዋ የበረከት ከተማ ናት፡፡ ልዩ ልዩ በረከቶች ይፈልቁባታል፡፡ “የበረሃ ገነት” እየተባለች የምትጠራበት አንዱ ምክንያት የበረከቶች መፍለቂያ መሆኗ ነው፡፡ እስቲ ከድሬ በረከቶች በጥቂቱ እንቅመስ፡፡
——-
    የድሬ ዳዋ ዳቦ ሁሌም ይገርመኛል፡፡ ርዝመቱ እስከ ግማሽ ሜትር ድረስ ይሆናል፡፡ ልስላሴው ደግሞ ሌላ ነው፡፡ ሲበሉት እንደ ላስቲክ እየተተረተረ ይላቀቃል፡፡ እንደ አሁኑ ዳቦ ከመጠን በላይ በኸሚራ (እርሾ) የተነፋ ባለመሆኑ ከሆድ ሰተት ብሎ ይገባል፡፡ ደግሞም በደንብ የበሰለ ስለሆነ “ሊጡ ሆዴን ይነፋኛል” በማለት እርሱን ከመብላት የሚያፈገፍግ የለም፡፡ የሚገርመው ነገር ደግሞ ዳቦው ሳይበላሽ እስከ አምስት ቀናት ድረስ መቆየት የሚችል መሆኑ ነው፡፡ በድሮው ጊዜ እናቶቻችን ከድሬ ዳዋ ሲመጡ መጀመሪያ እርሱን ነው የምንጠይቃቸው፡፡ ታዲያ በቅርቡ እንደ ሰማሁት እንደዚያ ዓይነት ዳቦ ከጅቡቲ ባቡር እየተጫነ ነው የሚመጣው፡፡ ለዚህም ነው ድሬ ዳዋ በቀል ከሆነው ዝነኛው ሀሩን ዳቦ የሚለየው፡፡
    ድሬ ዳዋን የጎበኘ ሰው በድሬ ዳዋው “ቴምር” መገረሙ የማይቀር ነገር ነው፡፡ በህጻንነታችን “ቴምር” ሲባል የድሬ ዳዋውን ቴምር ነው የምናውቀው፡፡ እስከ አሁን ድረስም ከድሬ ዳዋ በስተቀር በቴምር አብቃይነት የሚታወቅ የሀገራችን ከተማ ያለ አይመስለኝም፡፡ ይህ የድሬ ዳዋ ቴምር ከዐረቢያው ቴምር በጣም ይለያል፡፡ ቴምሩ የሚለቀመው በእሸትነቱ ነው፡፡ ሲበሉትም እንደ ሌሎች ፍሬዎች በአፍ ውስጥ “ኮሽ..ኮሽ..” ይላል፡፡ ከዚህም አልፎ በአፍ ውስጥ የመጣበቅ ባህሪ ስላለው እርሱን የበላ ሰው ውሃ መጠጣት ያሰኘዋል፡፡ በድሮ ዘመን ቴምሩ በጣሳ እየተሰፈረ ነው የሚሸጠው፡፡ በአሁኑ ዘመን ግን በኪሎ ግራም እየተመዘነም ይሸጣል፡፡
      ሌላው የድሬ ዳዋ በረከት “ጃጁር” ነው፡፡ ጃጁር አራት ማዕዘን ቅርጽ ያለው ትንሽዬ ብስኩት ነው፡፡ መጠኑ አሁን አቡወለድ እና ሂፕሆፕ ከሚባሉት የብስኩት ዓይነቶች ጋር ተቀራራቢ ሆኖ በጣም ወፍራም ነው፡፡ ከውፍረቱ በላይ የሚደንቀው ግን ጥንካሬው ነው፡፡ ህጻናት በጥርሳቸው ካልሆነ በእጃቸው ሊሰብሩት አይቻላቸውም፡፡ ይህ ጃጁር በዘይት፣ ዱቄት፣ ስኳርና እንቁላል ነው የሚሰራው፡፡ ጃጁር ሲሰራ ብዙ ልፋትና ብዙ ወጪ የሚጠይቅ በመሆኑ በችርቻሮ ሲሸጥም ዋጋው ይወደዳል፡፡ ሁለቱ ጃጁር ስሙኒ ነው የሚሸጠው (ሌላው ብስኩት በአምስት ሳንቲም ነው የሚሸጠው)፡፡
——
      “ሙሸበክ” እና “ባቅላዋ” የማይነጣጠሉ የድሬ በረከቶች ናቸው፡፡ ይሁንና በድሮው ዘመን “ባቅላዋ”ን ቀምሰነው አናውቅም፡፡ እናቶቻችን በየጊዜው ከሚያመጡልን “ሙሸበክ” እና “ሀላዋ” ጋር ባቅላዋን እየቀላቀሉ አያመጡልንም፡፡ ምክንያቱን በትክክል ባላውቅም ባቅላዋው በረጅሙ ጉዞ ወቅት በሚፈጠረው ሙቀት እየቀለጠ ስለሚበላሽ ይመስለኛል፡፡ በበኩሌ ባቅላዋ የቀመስኩት በአዲስ አበባ እንጂ በድሬ ዳዋ አልነበረም፡፡ ቢሆንም በሀገራችን ካሉት ከተሞች መካከል አሁንም “ባቅላዋ” በከፍተኛ መጠን የሚመረተው በድሬ ዳዋ ነው፡፡ ዋጋውም ቢሆን በድሬ ዳዋ ይረክሳል፡፡
    “ሙሸበክ”ም በድሬ ዳዋ በስፋት ይመረታል፡፡ በዋጋውም ከባቅላዋ ይረክሳል፡፡ ይሁንና እርሱም እንደ “ባቅላዋ” እርጥብ ነው፡፡ ደግሞም በብረት ምጣድ እየተጋገረ ነው የሚሰራው፡፡ ሙሸበክ ብዙ ወጪ አያስወጣም፡፡ እርሱን ለመስራት የፉርኖ ዱቁት፣ ስኳርና ዘይት ብቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡
   ይልቅስ ብዙ ሰው የማያውቀውን በረከት ልናገር። “ሙቀስቀስ” በድሬ ዳዋ ብቻ ሳይሆን በመላው የሀረርጌ ከተሞች ዝነኛ ሆኖ ዛሬም ይወሳል። የገጠሩ ክልል ጭምር ሙቀስቀስን ያውቀዋል። ይሁንና እርሱም ቢሆን በድሬ ዳዋ በኩል እየገባ ነበር ወደኛ የሚመጣው። በተለይም ኮንትሮባንድ በጦፈበት በዚያ የጥንት ዘመን ከድሬ ዳዋ ይመጡ ከነበሩ ሸቀጦች ቁጥር አንዱ እርሱ ነበር ለማለት ይቻላል፡፡ ታዲያ የርሱ ቀዳሚ ደንበኞች እኛ ህጻናት ነበርን እንጂ አዋቂዎች አይደሉም፡፡
 “ሙቀስቀስ” የስኳር እንክብል ነው፡፡ መጠኑ ከሜንታ ከረሜላ ትንሽ ከፍ ይላል፡፡ ቀለሙ ደግሞ በጣም ነጭ ነው፡፡ ቅርጹም አራት ማዕዘን (ኪዩቢክ) ነው። “ሙቀስቀስ” የተሰራው በጣም ከተጣራ ስኳር “(concentrated sugar) በመሆኑ በጣም ጣፋጭ ነው፡፡
አሁን ትዝ እንደሚለኝ ሙቀስቀስ በታሸገበት ፓኬት ላይ “ከአሜሪካ ህዝብ” ( from the People of United States) የሚል ጽሑፍና የኮከቦቹ አርማ ነበረበት፡፡ በመሆኑም ሙቀስቀስ እንደ “ቡክራ ወተት” ለእርዳታ የመጣ ነው ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ኮንትሮባንዲስቶቹ ለማይመለከተው ሁሉ ቸበቸቡት፡፡ እኛም ቀመስነው፡፡ አጣጣምነው!
   “ሙቀስቀስ” ተደጋግሞ ቢላስ በቀላሉ አያልቅም፡፡ አምስት “ሙቀስቀስ” በስሙኒ የገዛ ሰው ቀኑን ሙሉ ሲልሰው ይውላል፡፡ ሙቀስቀስ ከደርግ መንግሥት ውድቀት በኋላም ለተወሰኑ ዓመታት በገበያ ላይ እንደነበረ አስታውሳለሁ፡፡
——–
(አፈንዲ ሙተቂ፣ “ኡመተ ፈናን ኡመተ ቀሽቲ ድሬ ዳዋ” ከተሰኘው መጽሐፌ የተወሰደ፣ 2006 )
Filed in: Amharic