>
5:15 pm - Friday May 1, 0691

የካይሮ የትሮይ ፈረሶች ….!?!    (እስክንድር ከበደ)

የካይሮ የትሮይ ፈረሶች ….!?!

   (እስክንድር ከበደ)

”የሬዲዮ ኮሙኒኬሽናቸውን ሳይቀር በደምብ ነው የምንሰማው፤የምንጠልፈው…”ጌታቸው ረዳ
 ” በመቀሌ  የሚዲያና የኢነሳ አውታሮች  ተደበደቡ ” የመገናኛ ብዙሀን
አቶ ጌታቸው ረዳ ሰሞኑን በሰጠው መግለጫ ” በሬዲዮ መገናኛ የሚያወሩትን እንሰማለን !” ብዙ ስለሚወራ በወጣ ቁጥር ወታደራዊ ሚስጥር ሁሉ ሳይታወቀው ያመልጠዋል፡፡ ይህ ቃለምልልስ አንዳች ሚስጥር ለኢትዮጵያ መከላከያ ኃይል  የተቆመው ነገር ይኖራል፡፡ በክልሉ የስልክና የኢንተርኔት መገናኛ አውታሮች ቢቋረጡም ፤ ከውጭ በህገወጥ መንገድ ቀደም ሲል የገባ ወይም በእርዳታ እህል ውስጥ ተሸጎጠው ወደ መቀሌ የገቡ ከፍተኛ የመገናኛ መሳሪያዎች  እንዳሏቸው የሚጠቁም ሊሆን ይችላል፡፡ እናም የሀገሪቱ የደህንነት ተቋም የደረሰበት ሁኔታ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በማቅረብ  ፈጣን  የአየር ኃይሉ  እርምጃ    እንዲወሰድ  መሆኑን መገመት ይቻላል፡፡   ይህንን ጥቃት ተከትሎ ቡድኑ ወደ ለቅሶ ያደላ መግለጫ ያወጣው ያለምክንያት አይደለም፡፡ አንድ ሚስጥራዊ አቅም መውደሙ እርግጥ ነው፡፡
ኢትዮጵያ አየር ኃይል ዛሬ ያካሄደው  የመቀሌ ከተማ   የአየር ድብደባ   ፋይዳው ምንድነው ? የኢትዮጵያ መንግስት  እየተዋጋ ያለው ከፊት የሚታየውን ሀይል ብቻ አይደለም ፡፡ በአንድ ወቅት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ባልደረባ የነበሩ ከፍተኛ ባለስልጣናት ወይም ባለሞያዎች እዛ እንደሚገኙ አስቡት፡፡ ፋና ሚዲያና  ኢንሳ ታወሮች ተመቱ ሲባል አንድ ግዙፍ ፕሮጀክት መወደሙን መጠርጠር ይቻላል፡፡
 የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ላይ ”መብረቃዊ ጥቃት ” ተካሄደው የወታደራዊ  እዙን  ኮሙኒኬሽን ሬዲዮኖች  በማቋረጥና የክልሉን የቴሌኮሙኒኬሽን ስርአት በማቋረጥ ነበር፡፡ የቡድኑ ተዋጊዎች ከውጪ በሱዳንና በሌላ ስውር መንገዶች የገቡ የኮሙኒኬሽን መሳሪዎች እንደሆኑ ይገመታል፡፡  የጦርነቱ ሰሞን በድንገት የተገኘውን  ሲሲቲቪ  ምስል  የኢትዮቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ  አሳይተው እንደነበር ይታወሳል፡፡ ከጨረቃ የወረደ የሚመስለው  ”ዩፎ ” መሰል ሰውዬ  ከጸጉር እስከ እግር ጠፍሩ ተሸፋፋኖ  የቴሌኮሙኒኬሽን  ስርአቱን ሲበጣጥስና ሲያቋርጥ አይተናል፡፡ ይህ ባለሞያ ኢትዮጵያዊ ያልሆነ  ወይም  የውጭ ቅጥረኛ  ባለሞያ ሳይሆን አቀርም፡፡
የግብጹ  ቱርክ ለኢትዮጵያ ድሮን እንዳትሸጥ ለማግባባት ግፊት ለማድረግ እየሞከረች እንደሆነ ሲዘገብ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ግብጽ  ለኢትዮጵያ ድሮኖች እንዳይሸጡ  የምትፈልገው በሁለት ምክንያት ይሆናል፡፡አንደኛው  ኢትዮጵያ የዘመነ ቴክኖሎጂ መጠቀሟ በግዛቷ  በአዋሳኝ ድንበሯና ግዛቷን ውስጥ የሚፈጠሩ የውጭ ኃይሎችአደገኛ አዝማሚያዎችን  በብቃት ቅኝት እንዳታደርግ  እንዳትከላከል ማድረግ  ትፈልጋለች፡፡
 ሁለተኛው  ግብጽ የትግራይ ሀይሎችን ለመደገፍ  እና አሁንም እያደረገች ያለውን  ”ጥቁር ዘመቻ”( Black Operations)  በየጊዜው እየፈጸመች  በሌሎች ኃይሎች እንዲሳበብ መፈለጓ  ይሆናል፡፡
የግብጽ  የቀድሞ ፕሬዚዳንት  ጋማል አብዱናስር  ከአሜሪካ በተሰጣቸው የስጦታ ገንዘብ  ያስገነቡት  ባለ 187 ፎቁ  የጀዚራ ታወር ወይም የካይሮ ታወር የካይሮ  ምልክት ብቻ አይደለም፡፡ በአረብና በአፍሪካ ሀገራት  ውስጥ ”ጥቁር ዘመቻዎች” የምታቅድበትና የየሀገራቱ ፖለቲካ ለማናወጥ  ሴራ የምትጠምቅበት  ቢሮ ነው፡፡  ይህንን ለማስፈጸሚያ ደግሞ የስለላና ደህንነት ተቋሟ  ከ1950ዎቹ ጀምሮ  አል ናስር የተሰኘ  ህጋዊ መሰል አስመጪና ላኪ ኩባንያ አቋቁሞ ፤ አል ናስር  የመኪና አምራች ኩባንያ አለው፡፡ ይህንን የሚያውቁ አንዳንድ የደህንነት ተንታኞች  ”ጭራቁ ኩባንያ” ብለው በለሆሳሳ የሚጠሩት ስም አይጠሬ ኩባንያ ነው፡፡
የግብጽ  በዓለም አቀፍ  መድረክ  የግብጻውያን ባለሀብቶችን  በትግራይ ግጭት  መቀስቀሱን  ተከትሎ ፤ የደረሰባቸውን  ኪሳራ  ኢትዮጵያ እንድትከፍል ለመክሰስ   ውጥን  እንዳላት  የአረብ ሚዲያዎች ሲዘግቡ ነበር፡፡  የግብጽ ባለሀብቶች  ካሳ እንዲከፈላቸው የጠየቁት  በመቀሌ የኢንዱስትሪ ፓርክ  የማምረት ሂደቱ በማቋረጡ ለኪሳራ ተዳርገናል  በሚል  ነው፡፡ በመጀመሪያ 2 ሚሊየን ዶላር  የሚሆን ገንዘብ ኪሳራ ደርሶብናል ሲል ነበር፡፡ ቀስ በቀስ ወደ 10 ሚሊየን ዶላር አድርሰውታል፡፡ የግብጽ ባለሀብቶች በመቀሌ ኢንዱስትሪ ፓርክ ከመቼ ወዲህ እንደገቡና በምን ምርት ላይ እንደተሰማሩ ዘገባዎቹ አይጠቅሱም፡፡ በሚድል ኢስትና በኢጂፕት ቱደይ እንዲሁም በሌሎች የአርብ መገናኛ ብዙሀን ይህንን አስመልክተው የቀረቡ  ዘገባዎች   አበክረው የሚኮንኑት  የኢትዮጵያን መንግስት ሲሆን ፤ የዘገባዎቹ አብዛኛው  ይዘት የሚያተኩረው የታላቁ ህዳሴ ግድብ ውዝግብና ውጥረት ነው፡፡  ግብጽ በአረብና በአፍሪካ ሀገራት  የኢንቨስትመንት ተሳትፎዋ ንጹህ የንግድ ግንኙነት እንዳልሆነ የግብጽ የስለላና ደህንነት ተቋም  ታሪክ ይነግረናል፡፡  በኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ፓርኮች በመገንባት የምትታወቀው ቻይና ናት፡፡
ቻይና የገነባችውን የመቀሌ ኢንዱስትሪ ፓርክ ስለመግባታቸውም ሆነ ምን ያመርቱ እንደነበር አይታወቅም፡፡ ጦርነቱ ከመጀመሩ በፊት 70 ግብጻውያን  በመቀሌ በኩል ወደ  ወደ ኪዌት እንሄዳለን ብለው መንግስት እነዚህን የግብጽ ዜጎች ከጉዞ እንዳናጠባቸው ብልጭ ብላ የጠፋች  መረጃ ነበረች፡፡ ኤርትራም የግብጽ ጠላቂ ጀልባዎችና  ”አሳ አጥማጆች ”  ይዛ በኋላ መልቀቋ  ይታወሳል፡፡ በዛው ሰሞን ግብጽና ሱዳን በኢትዮጵያ ድንበር አካባቢ በጦር ጄቶችና በሂሊኮፕተሮች የታገዙ የጋራ ልምምዶች ሲያረጉ መቆየታቸው አይረሳም፡፡
የግብጽ   እ.ኤ.አ በ1952  የግብጽ አብዮት ተከትሎ ነበር፡፡ ኤጀንሲው  ከወታደራዊ የስለላና ቅኝት አገልግሎት  ቢሮ  ጋር   በአንድነት  በዓለም ላይ  ንቁ  ከሚባሉት  የስለላና መረጃ ተቋማት በ5ኛ ደረጃ የሚታይ ነው፡፡ የግብጽ  ጄነራል የስለላና ደህንነት ዳይሬክቶሬት  በቀድሞ ፕሬዚዳንት ጋማል አብዱ ናስር ነበር፡፡ ዳይሬክቶሬቱ እ.ኤ.አ በ1954 ዓ.ም  ለመቋቋሙ ገፊ ምክንያት የሚጠቀሰው ከውጭ ኃይሎች  እንደ ብሪታኒያና እስራኤል  የሚፈጠሩ አሉታዊ ተጽኖዎች እያደጉ በመምጣታቸው ነበር፡፡
 ይህንን የውጭ የስለላና ደህንነት ተቋማት የስለላ ተግባራት ላይ አጸፋ ስለላ የመድረግ ተልኮን ደርቦ እንዲሰራ ተደርጓ፡፡በናስር ክትትልና ቁጥጥር ስር በመሆን ፤የራሱ ህንጻ እንዲኖረው ብሎም   የሬዲዮ ፣ የኮምፒተር፣ የፎርጀሪ እና ”ብላክ ኦፕሬሽንስ” Black Operations.  በሚል  የተለያዩ መምሪያዎች  አደራጅቷል፡፡  የግብጽ  የቀድሞ ፕሬዚዳንት ጋማል አብደል ናስር  የግብጽ የስለላና ደህንነት ተቋም  ለሚያከናውናቸው  ኦፕሬሽኖች  ወጪ የሚሸፍን   ምስጥራዊ የአስመጪና ላኪ ደርጅት ፈጠሩለት፡፡ ይህውም   አል ናስር ተሰኘ ህጋዊ መሰል አስመጪና ላኪ የንግድ  ኩባንያ  ማቋቋማቸውን መረጃዎች ያሳያሉ፡፡
ይህ የደህንነቱ  የንግድ ኩባንያ በአልጄሪያ፣በደቡብ የመንና በበርካታ የአረብና የአፍሪካ ሀገራት ነጻነት እንዲያገኙ  በስውር መስራቱ ይነገራል፡፡የግብጽ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የውጭ ጉዳዮች የሚመለከተው ቢሆንም ፤ ጄነራል ኢንተለጀንስ ዳይሬክቶሬት (GID) በበርካታ የአረብና የአፍሪካ ንቅናቄዎችን በመደግፍ  እጁን  አስገብቷል፡፡
ግብጽ  በስለላና ደህንነት  መዋቅሯ  ውስጥ  የብላክ ኦፕሬሽን  (black operation) ”የጭለማ ዘመቻ” መምሪያ  አላት፡፡    ”ብላክ ኦፕሬሽን” በመንግስታዊ ኤጀንሲ በምስጥር  ወታደራዊ አሃድ ወይም ፓራሚሊተሪ ድርጅት (መደበኛ ያልሆነ ውትድርና ቀመስ አደረጃጀት)  ወይም የግል ኩባንያዎች ወይም ቡድኖች የሚፈጽሙት ስውር ዘመቻ ነው፡፡ እንዲህ ያሉ ዘመቻዎች ”የጭለማ ኃይሎች ” የወጠኑትን ዘመቻ  በሚስጥር  የሚፈጽሙበትና  ”ያልታወቁ ኃይሎች ” በሚል ለማምለጫ የሚጠቀሙበት መሆኑ ልዩ  ያደርገዋል፡፡ የግብጽ የስለላና ድህንነት ተቋም ይህንን ዘመቻ  እንደ መምሪያ አደራጅቶ በተለያዩ ሀገራት ሲፈጽም ቆይቷል፡፡
ከሀገር ውስጡ ኃይል ጋር የተቀናጀና በመመሳጠር  ከፍተኛ ስልጠና የወሰደ ወታደራዊ አሃድ በፈጣን ማጓጓዣ የሀገሪቱን የየብስና የአየር ክልል ጥሶ በመግባት የወጠኑትን እቅድ አሳክተው የሚወጡበት እድሉ ዝግ አይደለም፡፡ የህውሀት ከፍተኛ አመራሮች የአቶ ስዬና አብረሃና  የአቶ ስዩም መስፍን ቃለምልልስ ውስጥ  ጦርነት ከተጀመረ በአካባቢው እጃቸውን የሚያስገቡ በርካታ የማይታወቁ ኃይሎች እንደሚኖሩ የገለጹት ያለምክንያት አይደለም፡፡ ይህ ብዙ ምርመራ የሚጠይቅ ነው፡፡
ለማንኛውም ከላይ ያነሳሁትን የግብጽ ስለላና ደህንነት ተቋም  ሚስጥራዊው የአል ናስር አስመጪና ላኪ  የንግድ ኩባንያ  እንደ እርሾ ሆኖ  የአል ናስር ሞተር ካርን  ጨምሮ በርካታ የማይታወቁ  ግዙፍ የንግድ ተቋማትን በሽፋን እንደምትጠቀም   ማስታወሱ ነጥብጣቡን በሚገባ ለማገናኘት መነሻ ይሆናል፡፡
Filed in: Amharic