ግልጽ ደብዳቤ ለአቶ ጌታቸው አሰፋ
ለአቶ ጌታቸው አሰፋ
ለብሄራዊ መረጃና ደህንነት ሃላፊ
ሰኔ 27/2008
ለዚህ መነሻ የሆነን እና ከስራ ባልደርቦቻችን እንዲሁም ካለንበት ተቋም ኢሳት ውጭ በግል ለመጻፍ ያነሳሳን ረቡዕ ሰኔ 22 ቀን 2008 ዓ.ም /June 29/2016/ የተላከልን መልዕክት ነው።የርሶ ማለትም የደህንነት መስሪያ ቤት ሰራተኞች እንዲሁም የገዢው ፓርቲ ባለስልጣናት በየወላጆቻችን ቤት በመገኘትና በመጥራትበተጠቀሰው ቀን የሰጡት ማሳሰቢያ እና መደለያ እንደደረሰን እየገለጽን፣ እ ንደማንቀበል ለማረጋገጥ ይህን ለመጻፍ ተገደናል።
ወንጀል የፈጸመ ግለሰብ ወይንም ቡድን ቢሆን እንኳን ወንጀል በስጋ ዝምድና እንደማይተላለፍ ለአቅም አዳም ለደረሱ ያውም መንግስታዊ ሃላፊነት ላይ ላሉ ባለስልጣናት እንደማይጠፋቸው ቢታምንም በክፋት፣በጥላቻ እና በዘረፋ ግዚያቸውን ለሚያባክኑት የሕወሓት መሪዎች ይህ አለመከሰቱ አይገርመንም። እኛን ዝም ለማሰኘት አዛውንት እና ሕጻናትን በመያዣነት /hostages/ ለመያዝ ስትወስኑ ምን ያህል አቅም እያነሳችሁና ተስፋ እየቆረጣችሁ እንድሆንም አሳይቶናል።
እናንተ በደል አንገፈገፈን ብላችሁ ለመብታችሁ እሰከመጨረሻው ታግላቹኋል።እናንተ በተራችሁ በበደል ላይ በደል ስትጭኑብን ፡ ኢትዮጵያን በዘረኝነት ስትቀጠቅጡና ስትዘርፉ፣ ዜጎችን በገዛ ሃገራቸው ባይተዋር ስታደርጉ ይህንን በዝምታ እንድንመለከት ማስፈራሪያ እና መደለያ መላካችሁ የሚያናድድ ቢሆንም፣ ይህ ድፍረት ይበልጥ ጉልበት እንደሰጠን ለርስዎም ሆነ በሕወሃት ለሚመራው መንግስት ማስታወስ እንሻለን። ማናቸውም ማሰፈራሪያና መደለያ እንዲሁም ቤተሰቦቻችንን በዕገታ መያዝ ከነጻነት ጉዞ አንዲት ስንዝር እንደማትመልሱን በተግባራዊ ርምጃዎቻችን የምትመለከቱት ይሆናል።
''ማናቸውም ማሰፈራሪያና መደለያ እንዲሁም ቤተሰቦቻችንን በዕገታ መያዝ ከነጻነት ጉዞ አንዲት ስንዝር እንደማትመልሱን የምትመለከቱት ይሆናል''
Filed in: Amharic