>
5:42 pm - Tuesday March 20, 5477

ኦሮሙማ እና የሶማሊ ተፈናቃዮች ነገር.. ለምን ሐውዜንን ያስታውሰናል???  (አሰፋ ሀይሉ)

ኦሮሙማ እና የሶማሊ ተፈናቃዮች ነገር.. ለምን ሐውዜንን ያስታውሰናል???
 አሰፋ ሀይሉ
    «An unexamined life is not worth living.” 
  «ያልተመረመረ ሕይወት ፤ መኖር የሚገባው ሕይወት አይደለም፡፡»
– Socrates (ሶቅራጠስ)
የዛሬ 30 ዓመት – በሰኔ 15 ቀን 1980 ዓ.ም. – በሐውዜን የገበያ ሥፍራ ላይ – የወታደራዊው መንግሥት የጦር አውሮፕላኖች ባካሄዱት ምህረት የለሽ የቦምብ ድብደባ – 3,000 ያህል የከተማዋ ገበያተኞች ነፍስ ባንድ ጀምበር ሲቀጠፍ – እና በሺኅዎች የሚቆጠሩ ዜጎች የአካል ጉዳት በደረሰባቸው ማግስት – ህወኀቶች ያን የሐውዜንን አሰቃቂ የወገን ጭፍጨፋ – በወታደራዊው መንግሥቱ ላይ ለጀመሩት የትጥቅ ትግል – እንደ ዓይነተኛ የትግራይ ተወላጆችን ማሰባሰቢያነት እንደተጠቀሙበት – ወይም ያ በትግራይ የሐውዜን ነዋሪዎች ላይ የደረሰው አጋጣሚያዊ ግፍ – ለማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ እና ሰብዓዊ ፍጡር አሳዛኝ ክስተት ሆኖ ማለፉ ምንም አጠያያቂነት የሌለው እውነታ ነው፡፡
ቢሆንም ግን – ያ ክፉ አጋጣሚ ግን – በተለይ – ለያኔዎቹ ህወኀቶች – የትግራይ ብሔርተኝነትን እንደጋራ ማዕከላዊ አጀንዳው አድርጎ – በጋራ የተጠቂነትና የተሳዳጅነት መንፈስ – ታይቶ የማይታወቅ ሕዝባዊ (ማዕበላዊ) ድጋፍና አጋርነት – ለህወኀቶች እንዳስገኘላቸው – ሳይደግስ አይጣላም በሚል ከሐውዜን ማግስት የሆነውን – እውነቱን ፍርጥ አድርገው የሚያነሱት ብዙዎች ናቸው፡፡
ያ ሐውዜንን ከነገበያተኞቿ የጠራረገው ጭፍጨፋ ሁልጊዜም ቢሆን በወገን ላይ ያንን ዓይነት ግፍን ላለመድገም በብዙዎች አዕምሮ ሲታወስ ይኖራል፡፡ ነገር ግን ያ ክፉ አጋጣሚ ለያኔዎቹ ህወኀቶች – በምንም ዓላማና ፖለቲካ ልትገዛው የማትችለው –  ኃይለኛ የፕሮፓጋንዳ መሣሪያ ሆኖ እንዳገለገላቸው ደግሞ – ሁልጊዜም አብሮ ተያይዞ መነሳት ያለበት እውነታ ነው፡፡
ዛሬ ላይ ሆኜ – ያን የዛሬ 30 ዓመት በትግራይ ምድር ያለፈ – አሳዛኝ የሐውዜን ክስተት – ከነፖለቲካዊ ቱሩፋቶቹ – አሁን ላይ የሚያስነሳን ነገር ምን ተገኝቶ ነው?
ጥሩ፡፡ ዛሬ ላይ ሆነን ወደኋላ 30 ዓመታትን የኋሊት ተንደርድረን – የሐውዜንን ትዝታ ሳንወድ በግድ ለማስታወስ የምንገደደው – ዛሬ ላይ ያንኑ ሐውዜንን ተከትሎ ግልጋሎት ላይ የዋለውን ፖለቲካዊ ቅስቀሳና ትልቅ የመሰባሰቢያ ምክንያት የማግኘት ዓይነት – በዓይነቱ ያንኑ የሚመስል ተመሣሣይ አካሄድ – በሶማሊ ክልል ልዩ ኃይሎች ተፈናቀሉ ተብለው – ዕድሜልካቸውን ሲኖሩበት ከነበሩበት ምድር – አንዲወጡ ስለተደረጉት – እና ወደ ተነሱበት እና መኖሪያቸው ወደሆነው ወደትክክለኛ ሥፍራቸው ከመመለስ ይልቅ – የኦሮሚያ የፖለቲካ አቀንቃኞችና አስተዳዳሪዎች – እነዚያን የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑ የሶማሊ ተፈናቃዮች – በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ማስፈርን – የእርዳታ ማሰባሰብን – ወገናዊ ቅስቀሳን – እና በኦሮሞዎች ላይ ደረሱ የሚባሉ ሰብዓዊ ኪሣራዎችን ብቻ በማጉላት መጮኽን ስለምን መረጡ???
እነዚያን ከመኖሪያቸው በኃይል የኦሮሞ ተወላጅ ነዋሪዎች – በህገወጥ መንገድ ያፈናቀሏቸውን ኃይሎችና አካሎች በአስቸኳይ ለህግ አቅርቦ – ነዋሪዎቹን ግን – ወደኖሩበት – መንደራቸውን ወደቀለሱበት – ወደዚያው ወደሚገባቸው የተፈናቀሉበት ትክክለኛ ቀዬአቸው እንዲመለሱ ለምን አልተደረገም? ወደነበሩበት መኖሪያቸው እንዲመለሱ ቢደረግና – ተመሣሣይ ኢሰብዓዊ ተግባራት እንዳይፈጸሙ ተገቢው መንግሥታዊ ክትትልና ጥበቃ ቢደረግ ኖሮ – በሚሊዮኖች ደረጃ የደረሰውን ሰብዓዊ ቀውስ እዚያው ባጭሩ መግታት – እዚያው ላይ መልሶ ማቋቋም – እዚያው ላይ መፈናቀሉን ማብቃት አይቻልም ነበር ማለት ነው?
እነዚያ በሚሊየን የሚቆጠሩ የኦሮሞ ተወላጅ ነዋሪዎችን – ወደትክክለኛ መኖሪያቸው እንዲመለሱ ከማድረግ ይልቅ – በኦሮሚያ ሕዝብ ዘንድ ትኩስ እይታና አትኩሮት (‹‹አቴንሽን››) እንዲያገኙ በሚያደርግ ሁኔታ – ሰዎቹን በኦሮሚያ ክልሎች ውስጥ እንዲጠለሉ – በተለያዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች አዲስ መኖሪያ ሥፍራና ኩርማን መሬት እንዲሰጣቸው – ዳግም በማያውቁት አካባቢ እንደ አዲስ ኑሮን እንዲጀምሩ ማድረግ – በምን ዓይነት መሥፈርት ነው ቅድሚያ የተሰጠውና ዓይነተኛ አማራጭ ተደርጎ የተወሰደው??
ህግ ባለበት ሀገር ውስጥ – በዚህ አሳዛኝ ሰብዓዊ ቀውስ የተፈናቀሉ ዜጎችን – ወደ ኖሩበት ህጋዊ መኖሪያቸውና አካባቢያቸው ስለመመለስ ከማሰብና – ያንኑ የሚያረጋግጥ ተግባር እንዲወሰድ ከመጣጣር ይልቅ – ስለምን የኦሮሚያ ፖለቲከኞችና አስተዳዳሪዎች – ልክ እንደፍልስጥዔም ቀብርተኞች – የተፈናቀለውን ሕዝብ ከየኖረበት ክልል በወሳንሳ ይዘው – በኦሮሚያ ሕዝብ መሐል ማጓጓዙንና መበተኑን – ስለምን እንደ ዓይነተኛና ዘላቂ አማራጭ ቆጠሩት??
ወይስ – ድሮ የሐውዜን ጭፍጨፋን ተከትሎ ህወኀቶች ክስተቱን ወደዓይነተኛ የፖለቲካ ፕሮፓጋንዳ መሣሪያነት በማዋል ሕዝባዊ ብሐየርተኛ የድጋፍ ማዕበል ለመፍጠር ተጠቅመውበታል እንደተባለው – ልክ እንደዚያው ሁሉ – የአሁን የኦሮሚያ ፖለቲከኞች፣ አክቲቪስቶች፣ እና የኦህዴድና ኦነግ የመሣሠሉት – ህዝባዊ ድርጅቶችና የፖለቲካ አቀንቃኞቻቸው – ይህን ያህሉን ግዝፈት ያለው ሰብዓዊ ቀውስ ወደነበረበት እንዲመለስ የማድረግን ጉዳይ ሁለተኛ ጆሮአቸውን ብቻ መስጠቱን ለምን መረጡ??
ይህን ያህሉን ግዝፈት ያለው ሰብዓዊ ቀውስስ ሁለተኛ ጆሮአቸውን በመስጠት – እና ይህን ያህል ስፋት ያለውን ሀገራዊ ሰብዓዊ ቀውስ – ለታላቅ የፖለቲካ ድጋፍ ማሰባሰቢያ ዓይነተኛ መሣሪያ አድርገው በመጠቀም – ሕግ የሌለበት፣ የኑሮ/የህይወት ዋስትና ባልተከበረበት ሀገር ነው እየኖርን ያለነው፣ እኛ ኦሮሞዎች ተለይተን እየተጨፈጨፍን ነው፣ ተለይተን እየተፈናቀልን ነው፣ የኦሮሞ ተወላጆች ተለይተው ተጠቂዎችና ተሳዳጆች ሆነዋል የሚሉ – እና ልክ ሐውዜንን ተከትሎ በመላ ትግራይ ተወላጆች ዘንድ እንዲሰራጩ እንደተደረጉት – የጋራ ሰብዓዊ ብሔርተኛ አጋርነትን – ታላቅ የጋራ ኦሮሞአዊ ግንባርን፣ በተለያዩ የሐገሪቱ ክፍል ባሉ የኦሮሞ ተወላጆች መካከል ነበሩ የሚባሉትን ልዩነቶች ሁሉ አስወግዶ – ታላቅ የጋራ ኦሮሞነትን – ታላቅ ኦሮሞነትን ማዕከል ያደረገ ትኩስ (‹‹ሴንሴሽናል››) ብሔርተኛ መሰባሰቢያ አጀንዳን ፈጥሮላቸው ይሆን???
እና ነጥቤ – ልክ የያኔውን የዕለተ ዕሮቡን የሰኔ 15/1980 የሐውዜንን ታላቅ ሰብዓዊ ቀውስ – ህወኀት ታይቶ ወደማይታወቅ ሕዝባዊ ብሔርተኛ ማዕበል ማሰባሰቢያ መሣሪያ አድርጎ እንደተጠቀመበት ሁሉ – ልክ እንደዚያው – አሁንም – በኦሮሞ ፖለቲከኞች ዘንድ – ይህን ከሱማሊ-ክልል ኦሮሞዎች እንዲፈናቀሉ የመደረጉን ይህን ታላቅ ሀገራዊ ሰብዓዊ ቀውስ – እንደ ዓይነተኛ በኦሮሞነት ዙሪያ ሁሉንም ፖለቲከኞች የሚያሰባስብ ትኩስ ጉልበት ያለው ታላቅ ብሔርተኛ ማዕበልን መቀስቀሻ እና መሰባሰቢያ – ኃይለኛ የፕሮፓጋንዳ ጠቀሜታ ሰጥቷቸው ይሆን ወይ? ያ የሶማሊ-ተፈናቃይ – ወደ ኦሮሚያ መልሶ-ሰፋሪ – ጉዳይ – ለኦሮሞ ፖለቲከኞችና አክቲቪስቶች – እግረመንገዱን – ወይም በቀውሱ ማግስት – «ሣይደግስ አይጣላም!» ሆኖላቸው ይሆን ወይ?? – ጥያቄዬ ያ ነው፡፡ ጨርሼያለሁ፡፡
«An unexamined life is not worth living.” «ያልተመረመረ ሕይወት ፤ መኖር የሚገባው ሕይወት አይደለም፡፡» እንዳለው ሃቀኛው ፈላስፋ Socrates (ሶቅራጠስ) – ለማንኛውም – የሄድንበትን አኳኋን በእርጋታ እናጢነው፣ እንፈትሸው፣ እንመርምረው – እና ሕግ ባለበት ሀገር ላይ ሌሎችን አባርሮ መቀመጥ አይቻልምና – አሁንም ሆነ፣ መቼውኑም ቢሆን – ከመኖሪያቸው «የተፈናቀሉ» ኢትዮጵያውያን ዜጎችን – ወደዚያው ወደቀደመው መኖሪያቸው በአስቸኳይ ተመልሰው በሠላም መብታቸው ተጠብቆ የሚኖሩበትን አማራጭ – መቼውኑም አንዘንጋው፡፡ እንዲያውም ቅድሚያ እንስጠው፡፡ አበቃሁ፡፡
አምላክ ሕዝቦቻችንን ሁሉ አብዝቶ ይባርክ፡፡ የጃጋማ ኬሎ ሀገር፣ የብዙሃን እናት፣ እምዬ ኢትዮጵያ ሀገራችን፣ ለዘለዓለም ትኑር፡፡
ፎቶግራፉ (ከከበረ ምስጋና ጋር)፡-
«Ethiopian young girls worn in distinctive Oromo traditional clothing  and ornaments on the streets of Harar in January 1966 (1958 E.C).jpg»
Filed in: Amharic