>
5:13 pm - Monday April 19, 6032

የሐዋሳው የኢህአዴግ ጉባኤ እና የለውጥ ሂደቱ ፈተና! (ኤርሚያስ ለገሰ ዋቅጅራ)

የሐዋሳው የኢህአዴግ ጉባኤ እና የለውጥ ሂደቱ ፈተና!
ኤርሚያስ ለገሰ ዋቅጅራ
ለህውሓት ከአዴፓ ይልቅ የአብርሃ ደስታ አረና ፓርቲ ወዳጁ ነው!
* ለአዴፓ ከህውሓት ይልቅ አብን ወዳጁ ነው!
* በሀሳብ መተጋገዝ ካየነው ለዶክተር አቢይ አህመድ የሚቀርበው ዶክተር ደብረፂዮን ሳይሆን ዶክተር ብርሃኑ ነጋ ነው!
የህውሓት አመራሮች ” ቲም ለማን!” ከምድረገፅ ለማጥፋት መጥፎ እልህ ውስጥ ገብተው የቀበሮና ጃርት ጦርነት ( The Hedgehog Theory) ውስጥ ተዘፍቀዋል!
 
 ግንባር ፈጥሬያለሁ የሚል አንድ የፓለቲካ ድርጅት በተመሰረተበት መሰረታዊ አቋሞቹና መስመሮች ዙሪያ የማይታረቅ ልዩነት ከፈጠረ የመፍረስ እድሉ ሰፊ ነው። በመሬት ላይ ያለው ተጨባጭ ሃቅም የሚያመላክተው የተፈጠረው ልዩነት በአንድ ግንባር ውስጥ ተሰባስቦ የሚያስቀጥል አይደለም። ከተፈጠሩት የመስመርና መሰረታዊ አቋሞች ልዩነት በተጨማሪ የተናጠል ፓርቲዎቹ አመራር ዙሪያ ያለው ግንኙነት የመተማመን እጦት የሰፈነበት የጠላት ግንኙነት ሆኗል።
የቀድሞው ብአዴን የአሁኑ አዴፓ ከህውሃት ጋር በጠላትነት ከመፈራረጃቸው ባሻገር ጨዋታቸው ኢኮኖሚስቶቹ ” የአውራ ዶሮ ጠብ” (Chicken Games)  መሆኑ በግልፅ ወጥቷል። ለህውሓት ከአዴፓ ይልቅ የአብርሃ ደስታ አረና ፓርቲ ወዳጁ ነው። ለአዴፓ ከህውሓት ይልቅ አብን ወዳጁ ነው። ልዩነታቸው እኔ የወከልኩትን ሕዝብ የበለጠ የሚጠቅም አጀንዳ አለኝ የሚለው ላይ ነው። በሀሳብ መተጋገዝ ካየነው ለዶክተር አቢይ አህመድ የሚቀርበው ዶክተር ደብረፂዮን ሳይሆን ዶክተር ብርሃኑ ነጋ ነው። የህውሓት አመራሮች ” ቲም ለማን!” ከምድረገፅ ለማጥፋት መጥፎ እልህ ውስጥ ገብቶ የቀበሮና ጃርት ጦርነት ( The Hedgehog Theory) ውስጥ ተዘፍቀዋል። በተለይ አቶ ደመቀ መኮንን፣ ገዱ አንዳርጋቸው፣ ዶክተር አምባቸውን የመሳሰሉ የአዴፓ አመራሮችን ለማጥቃት ቀን ከሌት ስትራቴጂ ሲነድፉ እና በዙሪያቸው ሲያደቡ የምናይበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ቀበሮ እንዲህ ነው የሚያደርገው። እርግጥ ብዙ ጊዜ ቀበሮ አይሳካለትም።
ወደ መሰረታዊ የመስመርና የአቋም ልዩነቶች ስንመለስ በኦዴፓ (አዴፓ)  እና በህውሓት ብሎም በኢህአዴግ መካከል ግልፁ ሆኖ ወጥቷል። ከእነዚህ ልዩነቶች መካከል ግንባሩ ይመራበት የነበረው አመለካከት፣ የትላንት ታሪካዊ ትርክቶች፣ ፕሮግራሙ የተቀዳበት ርዕዮተ አለም፣ ዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት ማዕከል ያደረገው መተዳደሪያ ደንብ (ሕገ ደንብ) በጉልህ ሊነሳ የሚችል ነው። የቀድሞው ብአዴን የአሁኑ አዴፓ ዘለግ አድርጐም የሕገ መንግስት ማሻሻያ በተለይም የወሰንና የድንበር አከላለል ተቀባይነት እንደሌለው በድፍረት ይፋ አድርጓል። ከዚህ አኳያ ብአዴን “የኢፌዴሪ መንግስት አባላት ክልሎች አከላለል በሕዝቦች እውነተኛ ፍላጐትና ንቁ ተሳትፎ ፣ ብዝኃነትንና አገራዊ አንድነትን በሚያጠናክሩ መልኩ የወሰንና የማንነት ጥያቄዎች ትኩረት ተሰጥቷቸው በህዝብ ነፃ ተሳትፎ እንዲፈቱ ብአዴን በምክንያት ላይ የተመሰረተ ትግል እናካሂዳለን” የሚል መግለጫ እስከ ማውጣት ደርሷል።
#አብዮታዊ ዲሞክራሲ እና ታሪካዊ ትርክቶቹ 
ህውሓት/ኢህአዴግ ወደ ጫካ የገባበት እና የታገለበት ቁልፍ ምክንያት የብሔር ቅራኔ ኢትዮጵያ ውስጥ ዋነኛ ቅራኔ ነው ብሎ በማመን ነው። ህውሓት በተለያዩ ጊዜያቶች ባወጣቸው ፕሮግራምም ” በኢትዮጵያ መካሄድ የሚችለውም የብሔር አርነት ንቅናቄ ነው” በማለት አስፍሯል። ህውሓት በኮሚኒስት ሃይልነት በመደራጀት በጠባብ ብሔርተኝነት መስመር (Narrow Nationalist) በመሰባሰብ የአማራ ብሔረሰብን በጨቋኝነት በመውሰድ ሌላውን ተጨቋኝ /ጭቁን አድርገው የፋሺዝም ፕሮፐጋንዳ የተከተሉበት ነው። የአማራው ብሔረሰብ እንደ ስትራቴጂካዊ ጠላት ተወስዶ የማጥፋት ስራ የተቀየሰበት ነበር። ፓርቲው አለም አቀፍ ሁኔታው በፈጠረለት ምቹ ሁኔታ ፓለቲካዊ ስልጣኑን ከተቆጣጠረም በኃላ የብሔር ቅራኔውን እንደ መሰረታዊ ቅራኔ በመውሰድ በሕገ መንግስቱ መንደርደሪያ ላይ እንዲሰፍር አድርገዋል።
ይህ ፀረ ዲሞክራሲ፣ ፀረ ሕዝብና ከፋፋይ ፋሽስታዊ የህውሓት  አቋም ለአለፉት 27 አመታት መንግስታዊ መመሪያ በመሆኑ ዛሬ የደረስንበትን ምስቅልቅል ሊመጣ ቻለ። በአሁን ሰአትም ቢሆን ህውሓት በአንደበቱ ሌላ ቢናገርም ከስትራቴጂ አንፃር በኢትዮጵያ አሁንም ቢሆን ስትራቴጂያዊ ጠላቱ የሆነው ኢትዮጵያዊነት አልተለወጠም። ጠላትና ወዳጅ በሚል ማህበረሰቡን የሚከፋፍለው አብዮታዊ ዲሞክራሲ አልተለወጠም። ከ1983 ዓ•ም• በፊት የነበረችውን ” አሮጌይቱ ኢትዮጵያ” ቀኝ ገዥነት አልተቀየረም። በአንድ አመት ውስጥ ከሁለት ሚሊዮን በላይ የምታፈናቅለው ” አዲሲቷ ኢትዮጵያ!” የአፍሪካ ነብርነት የኩሸት ትርክት አልተቀየረም።
በሌላ በኩል በኢህአዴግ ግንባር ውስጥ ያሉት ኦዴፓ እና አዴፓ የጨቋኝ/ ተጨቋኝ ትርክቱንም ሆነ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ የቆመበት ምሶሶዎችን በአጭር ጊዜ በማፈራረስ ላይ ናቸው። ለዚህም ነው የህውሓትን ጥገናዊ ለውጥ ወደ ጐን በመተው በኢትዮጵያ ህዝብ ታሪክ፣ ትግል፣ ባህልና ስነ ልቦና በአግባቡ የተገነዘበ እንዲሁም የሕዝቡን መሰረታዊ ጥቅም በሚያስጠብቅ መንገድ መንቀሳቀስ የጀመሩት። ለዚህም ይመስላል የአብዮታዊ ዲሞክራሲን የጀርባ አጥንት የሆነውን ” ዲሞክራሲ ማእከላዊነት” ከፓርቲያቸው አሰራር አሽቀንጥረው የጣሉት።
አሁን ጥያቄው ኦዴፓ/አዴፓ በፓርቲ ደረጃ የያዙትን የታሪካዊ ትርክት ለውጥና የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ርዕዮተ አለም ቅያሪ በአዋሳው ጉባኤ አጀንዳ ያደርጉት ይሆን ወይ የሚለው ነው። በእኔ እምነት ሁለቱ ድርጅቶች ይህን አቋማቸውን በኢህአዴግ ደረጃ ይፋ አድርገው ለመወያየት ፍላጐት ያላቸው አይመስለኝም። ግምቴ ወደ ትክክለኛነት ከሄደ የፓርቲዎቹን አርቆ የማየት ችሎታ ሳላደንቅ ማለፍ አልፈልግም። ምክንያቶችም አሉኝ።
የመጀመሪያው ምክንያት ኦዴፓ እና አዴፓ የያዙትን አዲስ ርዕዮተ አለም ( ወደ ሊብራሊዝም የተጠጋ ግን ደግሞ ” ልማታዊ ዲሞክራሲ” የሚል የዳቦ ስም የተሰጠው) የፓለቲካ ፍልስፍና በዝርዝር ፕሮግራም አብራርተው ማቅረብ ይኖርባቸዋል። የአዲሱ ፕሮግራም ስትራቴጂያዊ የፓለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ ማህበራዊ ፣ የውጭ ጉዳይ አላማዎች ተፍታተው መቅረብ ይኖርባቸዋል። ከኢትዮጵያዊነት ፣ የዜጐችና የቡድኖች መብት ፣ ከዴሞክራሲ ተቋማት ግንባታ፣ ከመድብለ ፓርቲ ፣ ከነፃ ገበያ ፣ ከትምህርትና ስልጠና፣ ከህብረተሰቡ ስነ ልቦና፣ ከአገር ደህንት እና የውጭ ግንኙነት አንፃር ከህውሓት/ኢህአዴግ እንዴት እንደሚለዩ እና የተሻሉ እንደሆኑ ተንትነው ማሳየት ይኖርባቸዋል።
ከዚህ በተጨማሪም አሁን በስራ ላይ ያለው ቋንቋ ላይ የተመሰረተ የጐሳ ፌዴራሊዝም የልማታዊ ዴሞክራሲ አስተሳሰብን ወደ ተግባር ለመቀየር አዳጋች መሆኑን ማሳየት ይኖርባቸዋል። ቋንቋ ላይ የተመሰረተ የዘውጌ ፌዴራሊዝም እስካለ ድረስ ብሔራዊ አጀንዳን ቀርጾ ተግባራዊ ማድረግ የማይቻል መሆኑን፣ ልማታዊ መንግስት እና የቋንቋ ፌዴራሊዝም የማይታረቅ ቅራኔ እንዳላቸው ማብራራት ይጠበቅባቸዋል። ልማታዊ ዴሞክራሲ ፍልስፍና ጠንካራና አገር ወዳድ ማእከላዊ መንግስት እንዲሁም ብሔራዊ ንቅናቄ የሚፈጥሩ እቅዶች፣ ፓሊሲዎችና የፓሊሲ ማስፈፀሚያ መሳሪያዎች በቅድመ ሁኔታ መሟላትን ስለሚጠይቅ ለዚህ መዘጋጀታቸውን ማሳየት አለባቸው።
#የመተዳደሪያ ሕገ ደንብ ማሻሻያ፣
*አንድ: –  በመስከረም 1999 ዓ•ም• የወጣው የኢህአዴግ መተዳደሪያ ደንብ በመግቢያው ላይ
 ” ኢህአዴግ በአብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ፕሮግራም የሚመራና በፕሮግራሙ ላይ ለሰፈሩት አላማዎች የሚታገል ድርጅት ነው” ይላል።
  * ሁለት: – የኢህአዴግ የሚመራባቸው አጠቃላይ የአደረጃጀት መርሆዎች በሚለው ክፍል ሁለት ቁጥር ሶስት ላይ ፣
    ” ኢህአዴግ ለአብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ አላማ ተግባራዊነት የሚንቀሳቀስ ድርጅት ስለሆነ በአባልነት ሊቀበልና ሊያሰባስብ የሚችለው አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ አላማን በግልፅ በፕሮግራማቸው ላይ የቀረፁ ድርጅቶችን ብቻ ነው። በመሆኑም ግንባሩ ማንኛውንም አይነት የብሄር ብሄረሰብ ድርጅት የሚያቅፍ ካለመሆኑም በተጨማሪ አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ፕሮግራሙን መቀበል ብቻም በኢህአዴግ ስር ለመሰባሰብ አያበቃም። በተግባርም ለፕሮግራሙ ተፈፃሚነት መታገል ይጠይቃል። በአባል ድርጅቶቹ የሚመለመሉ አባላትም ይህንኑ የሚያሟሉ መሆን ይኖርባቸዋል” ይላል።
* ሶስት: – አንቀጽ ሰባት የግንባሩ የአደረጃጀትና የአሰራር መርሆዎች በሚለው ክፍል፣
    ” ሁሉም የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች አገራዊውን አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ፕሮግራም በየክልላቸው የመፈፀም ግዴታ አለባቸው። በኢህአዴግ አባልነት የሚታቀፉት ድርጅቶች በዲሞክራሲያዊ መርሆዎች የሚመሩና የዲሞክራሲያዊ ማእከላዊነትን አሰራር ብቻ የሚከተሉ ናቸው። በየደረጃው የሚገኙ የኢህአዴግ አካላት ማንኛውንም ውሳኔ የሚያሳልፉት በጉዳዩ ላይ በጋራ ከተወያዩ በኃላ በድምፅ ብልጫ ይሆናል” ይላል።
*አራት: – የአባል ድርጅቶች ግዴታ በሚገልፀው አንቀጽ 12 ላይ፣
” ማንኛውም የግንባሩ አባል የሆነ ድርጅት የግንባሩን ፕሮግራም ፣ መተዳደሪያ ደንብ፣ መመሪያዎች፣ ውሳኔዎች እና እቅዶች ተግባራዊ ማድረግ እና ማክበር ይኖርበታል። የግንባሩን የአሰራርና የአመራር መርሆዎች ማክበርና መከተል ይኖርበታል” ይላል።
*አምስት: – ከአባልነት ስለመሰረዝና አባልነት በራስ ፍቃድ ስለመተው በሚለው አንቀፅ 13 በንዑስ አንቀፅ አንድ እና ሶስት ላይ፣
   ” ከላይ በአንቀፅ 12 የተዘረዘሩትን ግዴታዎች በተሟላ ሁኔታ የማይፈፅም ድርጅት ከግንባሩ አባልነት በጊዜያዊነት ሊታገድ ወይም ሙሉ ለሙሉ ሊወገድ ይችላል።”
   ” ማንኛውም የግንባሩ አባል የሆነ ድርጅት ለግንባሩ ምክርቤት አሳውቆ በፈለገው ጊዜ ድርጅቱን መልቀቅ ይችላል። የመልቀቁ ውሳኔ የሚፀናው እለቃለው ባለው ድርጅት ጉባኤ ሲወሰን ነው” ይላል።
እንግዲህ ከላይ ለመጠቃቀስ የሞከርኳቸው (ከቁጥር አንድ እስከ አራት) የኢህአዴግ መተዳደሪያ ደንብ በኦዴፓ እና አዴፓ ሙሉ ለሙሉ ተጥሰዋል። የመጣሳቸው ውጤትም ከኢህአዴግ አባልነት የሚያሳግድ አሊያም የሚያስወግድ ነበር። ህውሓት በድሮው ቁመና ቢኖር ኖሮ ሕግ ተጥሷል ብሎ እርምጃ እስከመውሰድ ይሄድ ነበር። ነገር ግን ጥርሱ የወላለቀ ቀበሮ በመሆኑ ማድባቱን ቢቀጥልም መርህ ተጣሰ፣ ህገ ደንብ ተሸረሸረ ብሎ የሚናከስበት ሁኔታ የለም። ይህ ለህውሓት የሞት ሞት ነው። ወደ አዋሳም የሚጓዘው በተሸናፊነት መንፈስ ውስጥ በቃሬዛ ተጠቅልሎ ነው። እንደ እውነቱ ከሆነ ከጉባኤ አንፃር ህውሓት በታሪኩ ውስጥ እንዲህ ተሰባብሮ፣ ወገቡን በእንጨት ደግፎ፣ ከዘራ ይዞ የገባበት ጊዜ የለም። እርግጥ በጉባኤው ላይ አስመሳይ ሳቁን በማሳየት ደስተኛ ሆኖ ለመታየት የማይቆፍረው ድንጋይ አይኖርም።
በሌላ በኩል የኢህአዴግን መተዳደሪያ ደንብ የጣሱት ኦዴፓ እና አዴፓ ሰአታት በቀሩት የአዋሳ ጉባኤ ምን ሊያደርጉ ይችላሉ የሚለውን ግምት አስቀምጦ መሄድ ያስፈልጋል። በእኔ እምነት ሁለቱ ፓርቲዎች የኢህአዴግ መተዳደሪያ ደንብ ይሻሻል ብለው አጀንዳ የማሲያዝ መብት ቢኖራቸው የሚያደርጉት አይመስለኝም። አለማድረጋቸውም ተገቢ ይመስለኛል። አሁን ያሉበት “የማፈራረስ ምእራፍ” በህጋዊ መንገድ መሄድን አይጠይቅም። በድርጅቱ ድርጅታዊ አሰራር መሄድ የሚጠቅመው ህውሓትና በሶስቱ ድርጅቶች ውስጥ ያሉትን ፀረ ለውጥ ሃይሎች ብቻ ነው። ሲጀመር የዚህ መተዳደሪያ ደንብ ባለቤት ህውሓት በመሆኑ የመቀበል ግዴታ የለባቸውም። ሲቀጥል አዴፓ አሁን ከተፈጠረው አዳጊ አገራዊና ክልላዊ ሁኔታ ጋር አብሮ የሚራመድ የፓለቲካ ፕሮግራምና መተዳደሪያ ደንብ እንዲኖር እታገላለሁ በማለት ከገለፀው መግለጫ ጋር የሚጣጣም ነው። ሲሰልስ እውነተኛ ለውጥ እንዲኖር ከተፈለገ ይሄ ህገ አራዊት ተቀዳዶ መጣል ይኖርበታል። ነገር ግን ኦዴፓ እና አዴፓ አሁን ያሉበት ቁመና ለእንደዚህ አይነት የድፍረት ውሳኔ የሚያደርሳቸው አይደለም።
በመሆኑም የለውጥ ሀይል የሆነው ” ቲም ለማ” ከአዋሳ ጉባኤ ለማሳካት ቆርጦ መነሳት ያለበት የኢህአዴግን አመራር መቆጣጠር ሊሆን ይገባል። የድርጅቱ ሊቀመንበርነት እና ምክትል ሊቀመንበርነት ከዶክተር አቢይ እና አቶ ደመቀ መኮንን እጅ መውጣት የለበትም። ይሄ በምንም ተአምር ለድርድር መቅረብ የለበትም። አለበለዚያ በኢህአዴግ ውስጥ የተለኮሰው የለውጥ ጅማሮ ሊደናቀፍ ይችላል። ለውጥ ፈላጊው የኢትዮጵያ ህዝብም ከወዲሁ ማስጠንቀቂያውን መላክ ይኖርበታል። በዚህ ጉዳይ የለውጡ ዋነኛ ባለቤት የኢትዮጵያ ሕዝብ ቢሆንም የለውጡን ትንሹ ሞተር እያሽከረከሩ ያሉት በቲም ለማ ውስጥ የተሰባሰቡት አመራሮች ናቸው። ስለዚህም ለውጡ እንዳይቀለበስ ከለውጥ ሐዋርያዎቹ ጐን እንቁም!!
Filed in: Amharic