>

ፍሬወይኒ መብርሃቱ እንደ ፋና ወጊ! (አበጋዝ ወንድሙ)


ፍሬወይኒ መብርሃቱ እንደ ፋና ወጊ!

አበጋዝ ወንድሙ

 

የኢትዮጵያን ሰራተኞች በሚመለከት ሰሞኑን ሁለት መጣጥፎች በድረ-ገጾች ወጥተው የማንበብ እድል ገጥሞኝ ባንደኛው እጅግ ሳዝን ፣ ሁለተኛው ግን ተስፋ እንድሰንቅ አድርጎኛል ።

የመጀመሪያው ሃዋሳ የኢንዱስትሪ መናኸሪያን አስመልክቶ ኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲ የሚገኘው የስተርን የንግድና ሰብአዊ መብት ማእከል ( New York University’s Stern Center for Business and Human Rights)ያዘጋጀው መጣጥፍ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ሲ ኤን ኤን ( CNN) በየዓመቱ በዓለም ዙሪያ በጎ ሥራ በመስራት አርአያ የሚሆኑ ጀግኖችን ለተመልካቾቹ የሚያስተዋውቅበት፣ ብሎም የሚመርጥበት ዝግጅት ላይ የወጣችው ወይዘሮ ፍሬወይኒ መብርሃቱና፣ ማርያም ሴባ የተሰኘው ፋብሪካዋ ናቸው።

ሃዋሳ ያሉት ፋብሪካዎችን አስመልክቶ የኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲው ጥናትን አሳዛኝ የሚያደርገው፣ ሰራተኛው የሚከፈለው ደሞዝ በሌላ ሶስተኛ ዓለም ከሚገኙ መሰል ፋብሪካ ሰራተኞች እጅግ ዝቅ ያለ (ከመጨረሻ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ በሚገኙት ባንግላዴሽና በርማ ያሉ ሰራተኞች ከሚከፈላቸው ዝቅተኛ ከሚባል ደሞዝ፣ የኛ ሰራተኞች የነሱን ደሞዝ 27% ብቻ ነው የሚያገኙት!) ደሞዝ መከፈላቸው ብቻ ሳይሆን ፣ በሌላ ስፍራ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ መሰል ፋብሪካዎች ከሚከፍሉት በግማሽ ያነሰ መሆኑ ነው።

ይሄ ባለፈው ወር Apparel Insider የተሰኘ መጽሄት 52 ፋብሪካዎችን ጎብኝቶ ከ1000 በላይ ለሚሆኑ ሰራተኞች መጠይቅ አዘጋጅቶ ባቀረበው ጽሁፍ የተገለጸ ነው።

የኒውዮርክ ዩኒቨርሲቲው ጥናት በግልጽ እንደሚያሳየው በብዙ ተስፋ ተሞልተው ወደ ፋብሪካው የተመሙት ሰራተኞች ከመጡ በዃላ በሚያጋጥማቸው አስከፊ የሥራና የኑሮ ሁኔታ በመመረር በአጭር ጊዜ ውስጥ በገፍ ስራቸውን ጥለው ይሄዳሉ። ፋብሪካዎቹ የሚከፍሏቸው ደሞዝ ከመጡበት ገጠር ያሉ ዘመዶቻቸውን ለመደጎም ይቅርና ለራሳቸው ለሰራተኞቹ፣ለቤትም ሆነ ለቀለብ ስለማይበቃቸው፣ በርከት ብለው አንድ ክፍል መተኛት ወይንም እስከ ሶስት ሰዓት የሚፈጅ መንገድ(ከሚያስከተለው ድካምና ስጋት ጋር ) መጓዝ የሚገደዱ መሆናቸውንም ጥናቱ ያሳያል።

ጥናቱ እንደሚጠቁመው ሰራተኞቹ ላይ የሚደርሰው ሁኔታ በአጠቃላይ ሲታይ፣ ሰብአዊ መብታቸውን ከመጣስ እንደማይተናነስና፣ ይሄም ከቀጠለ የፋብሪካዎቹን ህልውና የሚፈታተን ስለሚሆን፣ መስተካከል ይገባቸዋል የሚላቸውን መጠቁሞች ለመንግሥትና ለፋብሪካው ባለ ንብረቶችም አሳስቧል።

ወይዘሮ ፍሬወይኒ መብርሃቱ በገጠሪቷ ኢትዮጵያ ተወልዳ ያደገችና በአሜሪካን ሀገር በኬሚካል ምህንድስና ትምህርቷን የተከታተለች የ 54 ዓመት ሴት ወይዘሮ ነች።

በ ሲ ኤን ኤን ( CNN) ቴሌቪዥን የቀረበው ሃተታ እንደሚጠቁመው፣ ፍሬወይኒ አሜሪካን ሀገር የዛሬ 26 ዓመት ለትምህርት በመጣችበት ወቅት በአንድ መደብር ለግብይት ገብታ ሳለ ያየቻቸው የሞዴስ ምርጫዎች ፣ ምርጫ አልባ የነበሩትና ሀገር ቤት ጥላቸው የመጣቻቸው ወጣት ሴቶችን እንድታስታውስ ግድ አላት ።

ፍሬወይኒ እንድምትተርከው፣ የ 13 ዓመት ልጅ ሆና የመጀመሪያ የወር አበባዋ ሲመጣ ትልቅ ድንጋጤ ውስጥ ከመግባቷም በላይ፣ ስታድግ በአካባቢው እንደ እርግማን ይታያል መባሉን መስማቷ፣ ራሷ መጥፎ ሰው እንደሆነች ወይንም ልዳር ነው የሚል ፍራቻም እንዲያድርባትና ፣ አካባቢዋ እንደነበሩት ወጣት ሴቶችም የተሰማትን ስሜት ለማንም ሳትናገር ወይንም ሳታማክር በፍርሃትና ዝምታ ውስጥ ትኖር እንደነበር ትውስታዋ ነው።

በህብረተሰቡ ውስጥ ከነበረውና ካለው ዃላ ቀር አስተሳሰብም በላይ ግን፣ የወር አበባን አስመልክቶ በቂ እውቀትና ግንዛቤ አለመኖር ፣የሞዴስ አለመታወቅ ወይንም አለመኖር ተዳምረው ወጣት ሴቶች ላይ የነበረው ጫናም የወጣትነት ትዝታዋ ነበር።

የልጅነቷ ትውስታ አሜሪካን ሀገር መጥታ ካጋጠማት ሁኔታ ጋር ተዳምሮ ሀገሯ ተመልሳ ፋብሪካ አቋቁማ ይሄንን ችግር ለመቅረፍ ትልቅ መግፍኤም ሆናት።

ፍሬወይኒ የዛሬ 14 ዓመት በራሷ ዲዛይን የተሰራና የባለቤትነትም ፓተንቱም የሷ የሆነ፣ ደጋግሞ መጠቀም የሚቻል ሞዴስ ፈጥራ፣ ፋብሪካ አቋቋመች።

በአሁኑ ሰዓት ይሄ ፋብሪካ በዓመት አስከ 750,000 ሞዴሶች በዓመት የሚያመርት፣ ለ 43 ሴቶች የስራ እድል ሊፈጥር የቻለ ተምሳሌታዊ ፋብሪካ ለመሆን በቅቷል።

ይሄ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሴቶች አህቶቻችንን ችግር ሊያቃልል የቻለ ስራ፣ በራሱ ለፍሬወይኒ ትልቅ ክብር እንዲሰጣት የሚያደርግ ከመሆኑም በላይ ፣ ፋብሪካዋን የመሰረተችበትና የምታካሂድባቸው መርሆዎች ደግሞ፣ በሀገራችን ላሉትም ሆነ ለወደፊት ለሚቋቋሙት ፋብሪካዎች በአርአያነት ተወስደው አንደ የሁኔታው መተግበር ይኖርበታል የሚል እምነት አለኝ።

በ ሲ ኤን ኤን ( CNN) ቴሌቪዥን ፍራወይኒ በሰጠችው ቃለ ምልልስ የማርያም ሴባ ፋብሪካ መርሆዎች በጥቅሉ ሲታዩ የሚከተሉት ሆነው እናገኛቸዋለን

ሀ. ሰራተኞች የሚከፈሉት ደሞዝ በደረጃቸው ለአስተማማኝ ኑሮ በቂ የሆነ ፣

ለ. ለሰራተኞች በቀጣይ ኑሮዋቸውን ለማሸነፍ እንዲረዳ የነጻ ስልጠና መስጠት ፣

ሐ. ደሞዝ የሚከፈልበት የእረፍት ቀናት ለሠራተኞች መስጠት፣ (የማርያም ሴባ ፋብሪካን ስትመሰርት ስራዉ በሴቶች መሰራቱ ተማራጭ ነው ብላ በማሰቧም ሰራተኞቿ በሙሉ ሴቶች በመሆናቸው ደግሞ ከወሊድ ጋር በተያያዘ የአራት ወር ፍቃድ ፋብሪካው ይሰጣል ።)

መ. የስራ ሃላፊዎችን ከውጭ መመልመል ሳይሆን፣ ሰራተኞች በሚሰጣቸው ስልጠና የሚያዳብሩትን ክህሎት መሰረት በማድረግ ማሳደግ ላይ የተመረኮዘ የአሰራር ሂደት ናቸው።

በነ አበራ ገሙ ትግል ፣ በነ ማርቆስ ሃጎስና ሌሎችም መስዋአትነት ተቋቁሞ ለሰራተኞች መብት ይታገል የነበረው የሰራተኛ ማህበር በደርግ ጡጫ ተሽመድምዶ ፣ በኢህአዴግ ዘመን በነ ዳዊ ኢብራሂም መሪነት ለማንሰራራት ሞክሮ የነበረ ቢሆንም፣ ዳግም በደረሰበት ጉሸማ መሪዎች ሲሰደዱ ድርጅቱም፣በአካል ከመኖር ውጭ ለሰራተኛው መብት የሚታገልበት አቅምም ሆነ ወኔ ስለሌለውና፣ መንግስትም ራሱ ወረቀት ላይ ያሰፈራቸውን ህጎች እንኳን ተግባራዊ ለማድረግ ግድ ስላልሰጠው ፣ ሰራተኛው ላይ የሚደርሰው ግፍ አስከፊነቱ እየጨመረ እየሄደ እንደሆነ ይታወቃል።

የሰራተኛውን መሰረታዊ ፍላጎቶችና ጥያቄዎች ለማሟላት፣ ሰራተኛው ከመሰረታዊ ድርጅቱ እስከ ኮንፌዴሬሽኑ ድርጅቱን አጠናክሮ ለመብቱ የሚያደርገው ትግል ወሳኝ መሆኑ የሚታወቅ ነው። አሁን ባለው ሁኔታ ግን ለስሙ ያለው የሰራተኛ ማህበር በሀገር ውስጥ ከሚገኙት የፋብሪካ ሰራተኞች ውስጥ በባለ ፋብሪካዎች አምቢተኝነትና ከመንግስትም ህግ የማስከበር ፍላጎት እጦት ጋር ተዳምሮ፣ አንድ አስረኛውን አንኳን የፋብሪካ ሰራተኛ ማደራጀት እንዳልቻለ ግልጽ አድርጓል።

የሰራተኛው ማህበር ተጠናክሮ የሰራተኞችን መብት የማስከበር ደረጃ እስኪደርስ ግን ፣ እንደ ፍሬወይኒ ያሉ ማህበረሰባዊ ሃላፊነት የሚሰማቸው የፋብሪካ ባለንብረቶች የሚመሩባቸው መርሆዎች በሌሎችም ፋብሪካዎች እንዲተገበሩ፣ በማህበራዊ ፍትህ የሚያምኑ ግለሰቦች፣ ቡድኖችም ሆኑ የፖለቲካ ድርጅቶች አስፈላጊ ጫና በፋብሪካ ባለቤቶችና በመንግስትም ላይ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል።

Filed in: Amharic