>
5:13 pm - Thursday April 18, 2735

ለኦሮምኛ ግእዝ ከላቲን ምን ያህል እንደሚሻል የሚያመላክቱ ነጥቦች !?! (ግርማ ካሳ)


ለኦሮምኛ ግእዝ ከላቲን ምን ያህል እንደሚሻል የሚያመላክቱ ነጥቦች !?!
ግርማ ካሳ
አቶ በቀለ ገርባ በመቀሌ ለምን የግእዝ ፊደል እንዳለ ላቲን መጠቀም እንዳስፈለገ ተጠይቀው ሲመልሱ የግ እዝ ፊደል ብቃት እንደሌለውና የተሻለው ላቲን መሆኑ በጥናት ስለተረጋገጠ ነው የሚል ምላሽ ሰጥተዋል። አቶ በቀለ ላቲን የተመረጠው በፖለቲካና በጥላቻ ምክንያት እንዳልሆነምው ነው የገለጹት።
ሆኖም በርካታ ምሁራንና አክቲቪስቶች ኦሮምኛ ከላቲን ይልቅ በግእዝ መጻፉ በብዙ መስፈርቶች የተሻለ እንደሆነ ሳይንሳዊ በሆነና መረጃ ላይ ባተኮረ መንገድ ያስረዳሉ።
ለኦሮምኛ ግእዝ ከላቲን ለምን እንደሚሻልል አክስቀመጣቸው ምክንያቶች አንዱ ሳይንሳዊ የሆነው ምክንያት የሚከተለው ነው።
ከሳይንስ አኳያ – ኦሮምኛን በኮምፒተር በተሟላ መልኩ መጻፍ ይቻላል
ኦሮምኛ በኢትዮጵያ ቀለማት ቢፃፍ የተሻለ ነው ሲባል፣ አንዳንድ የድሮ ፖለቲከኞችና የቀድሞ ታጋዮች የሚያቀርቧቸው ሰበቦች፣ “አንዳንድ የኦሮምኛ ቃላት በተለምዶ ግዕዝ በሚባለው ኢትዮጵያዊ ፊደላት ሊፃፉ አይችሉም፣ ለታይፕራይተርም አይመቹም፣” የሚሉ ናቸው። ይህ ግን እውነት አይደለም። ለምሳሌ አይቻሉም ተብለው የነበሩት ፊደላትና ቃላት በኦሮሚያዊትዋ ልጅ፣ በሰንዳፋው ተወላጅ በዶክተር አበራ ሞላ መላ እነሆ ተችለዋል።
ዸዹዺዻዼዽዾዿ
ዹፌ፣ ዻባ፣ ባዻዻ፣ ዼራ፣
ልክ እንደ ላይኛዎቹ ፊደላትና ቃላት፣ የኦሮሞ ቀለማት ሁሉ በኢትዮጵያ ፊደላት ተቀርፀው በተግባር ለመዋል እየጠበቁ ነው። እድሜ ለዶክተር አበራ ሞላ እ.ኤ.አ. ከ1987 ጀምሮ በሶፍትዌር ደረጃ ተዘጋጅተው ገበያ ላይ ውለዋል። የአንዱን ቃል ከሌላው መለያ የማጥበቂያ ምልክቶችም ተበጅቶላቸዋል። ዶክተር አበራ ሞላ፤ የግዕዝ ፊደላት ለኦሮምኛና ለሌሎቹም ዋና ዋና ቋንቋዎቻችን መፃፊያ ብቁ እንዲሆኑ ለ35 ዓመታት ያህል ለፍተውባቸዋል። ስለዚህ የኢትዮጵያ ፊደላት የላቲኑን ሊተኩ የማይችሉበት ምንም ምክንያት የለም። አውቆ የተደበቀን ቢጠሩት አይሰማም ካልተባለ በቀር። የኢትዮጵያ ፊደላት ኦሮምኛን ለመክተብ ብቁ ከመሆናቸውም በላይ ብዙ ጥቅም ያላቸው መሆናቸውን የሚመሰክሩ ሰነዶች ተዘጋጅተዋል። ዊኪፔድያ ውስጥ ገብተው የዶክተር አበራ ሞላን የምርምር ውጤት ይመልከቱ። የአዲስ አበባው ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ባዩ ይማም በበኩላቸው፤ በዚህ ጉዳይ ላይ ቀደም ብለው ሰፊ ጥናት አካሂደዋል።
ግዕዝ በዶክተር ኣበራ ሞላ ኮምፕዩተራይዝድ ሆኖ ለዓማርኛ ተመድበው ከተረፉት ሦስት መርገጫዎች ኣንዱ ለኣፋን ኦሮሞ (Afan Oromo) ሲሆን ሌላው ለትግርኛ ተሰጥቶ የቀረው ለኣገው/ቢለን ሥራ ላይ ውለዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ በ፲፱፻፹፫ ዓ.ም. የመንግሥት ለውጥ ጊዜ የአንድ ድርጅት ኦሮሞ ምሁራን ተሰብስበው ከግዕዙ ይልቅ ላቲን ይበጀናል በማለት ግዕዙን (Ethiopic Oromo syllabary) ስለተዉት የሚከተሉትን መጋራት ሳይጠቅም ኣይቀርም።
፩. ጥንትም ቢሆን ፊደላት በእጅ ጽሑፍ ሲጻፉ ላቲን ከግዕዙ በፍጥነት የተከተበበት ጊዜ ኣልነበረም። ምክንያቱም ግዕዝ ኣንድን ድምጽ በኣንድ ቀለም ሲያሰፍር ለኣብዛኛው የላቲን ድምጾች ሁለት ቀለሞች ስለሚያስፈልጉት ነው።
፪. የላቲንና ግዕዝ ቀለሞች በማተሚያ መሣሪያዎች ሲከተቡ የሁለቱም ቀሎሞች መረጣዎች ኣጠቃቀሞች እኩል ነበሩ። በእዚህ ዘዴ የኦሮምኛ ዓማርኛ ተርጐሚያ በ1850 ግድም በኣቶ ሓብተ ሥላሴ (Lexicon) እና ለኦሮምኛ ሥነጽሑፍ የመጀመሪያው አዲስ ኪዳን ከጥቂት ዓመታት በኋላም ሚስዮኑ ክራጵፍ (J.L. Krapf) በ፲፰፻፸፩ ዓ.ም. በራሱ ስም ያሳተመው ይህንኑ የነአለቃ ዘነብን ፲፰፻፷፪ ዓ.ም. ሥራ “ቁልቁሎታ መጻፎታ ከኩ ሐረዋ” ነበር።  ኣለቃ ዘነብ ወደ ፲፰፻፸ ዓ.ም. ግድም የ“ኦሮምኛና ኣገውኛ መዝገበ ቃላት” ጽፈዋል ይባላል። የኣስቴር ጋኖን የትርጕም መጽሓፍ በመጠቀም በ፲፰፻፹፯ ዓ.ም. የታተመም የኦሮምኛ ሓዲስ ኪዳን፣  መጫፈ ቁልቁሉ በ፲፰፻፺፱ እ.ኤ.ኣ. (፲፰፻፺፪ ዓ.ም.) በቅዱስ አናሲሞስ ነሲቡ፣  እና ከእዚያም ወዲህ እንደነ በሪሳ የኣሉ ጋዜጣዎች በግዕዝ ፊደል በኦሮምኛ ታትመዋል። ቀደም ብሎም በግዕዝ ፊደል በኦሮምኛ ከቀረቡት መረጃዎች ኣንዱ ጀምስ ብሩስ የወሰደው የ1790 የኦሮምኛ ትግጉም ጽሑፍና ሌላም ኣለ። በእጅ የጽሕፈት መሣሪያ ዘመን ታይፕራይተር ዓማርኛን ስለኣልጻፈ ላቲን ብልጫ ነበረው።
፫. በዶክተሩ ኮምፕዩተራይዝድ የሆነው ግዕዝ እ.ኤ.ኣ. በ1987 ለገበያ ቀርቦ በማተሚያ ቤቶች ፊደላቱ መክተብ ስለተጀመረ ምሁራን ደስ ሊላቸውና ሳይንሱንና ቴክኖሎጅውን ማወቅና ማስተዋወቅ በተገባ ነበር። ይህ በኣለመደርጉ እ.ኤ.ኣ.  1992 [863] በፕሮፈሰር ጥላሁን ጋሜታ ወደ ላቲን ለማዞር ከቀረቡት የኣማርኛ የጽሕፈት መኪናን የሚመለከቱት ጊዜ የኣለፈባቸው ምክንያቶችም መልሶች ነበሩ። ስለዚህ በግዕዝ ፊደል በማተሚያ ፊደላት ሲጻፉ የነበሩት በኮምፕዩተር ስለቀረቡ ቴክኖሎጂው ስለተሻሻለና ስለቀለለ ጉዳዩ ይመለከተናል የኣሉት የኦሮሞ ምሁራን ሊደሰቱ የሚገባ እንጂ ወደ ላቲን የሚያስዞር ኣዲስ ምክንያት ኣልነበረም።
በጊዜውም በፕሮፌሰር ባዬ ይማም በዓማርኛ መልስ ቀርቦ ፕሮፌሰር ሚንጋ ነጋሽና ፕሮፌሰር ሳሙኤል ክንዴ ወደ እንግሊዝኛ ተርጕመውታል።
፬. ላቲን የእራሱ ችግሮች ያሉት ፊደል ነው።
በዶክተሩ ፈጠራ እየኣንድኣንዱን የግዕዝ ቀለም በሁለት መርገጫዎች መክተብ ተቻለ። ላቲን ይኸን እየኣንዳንዱን የግዕዝ ቀለም በሁለት መርገጫዎች የመክተብ ችሎታ ስለሌለው ግዕዝን በግዕዝ ፊደል መክተብ ብልጫ ኣገኘ። ስለዚህ ኦሮምኛን በላቲን ፊደል መክተብ (ቁቤ) መሻሻል ኣይደለም።
፭. ይህ በእንዲህ እንዳለ የኦሮምኛው የግዕዝ ፊደል ከሌሎቹ ጋር በዶክተሩ ኮምፕዩተራይዝድ ስለሆነ ለኣለፉት ፴ ዓመታት በኮምፕዩተር ቀርቦ በኋላም በዩኒኮድ ዕውቅና ቢያገኝም ሁሉም ባይሆኑ ኦሮሞዎች ግዕዙን እርግፍ ኣድርገው ጥለው ወደ ላቲኑ ስለዞሩ የተፈጠሩት ችግሮች ቀጥለዋል።
፮. በእጅ የጽሕፈት መሣሪያ ዘመን ታይፕራይተር ኦሮምኛን ስለኣልጻፈ ላቲን ብልጫ ነበረው። የዶክተሩ ፈጠራ ለእውሸቱ (የፈጠራ) የታይፕራይተር የአማርኛ ነገሮችና ለትክክለኛዎቹ የማተሚያ ቤቶች ፊደላት ኣጠቃቀሞች ፈውሶች (Breakthrough) ነበር። ስለ ታይፕራይተሩ ድክመት ዶክተሩ እ.ኤ.ኣ. በ1991  ስለኣቀረቡ መሣሪያው ወደ ላቲን ለመዞር ምክንያት መሆን ኣልነበረበትም። ከእዚያም ወዲህ በኮምፕዩተር የኦሮምኛው የግዕዝ ፊደል በዶክተሩ መከተብ ችሎታና የተጠቃሚዎች መኖር ግንዛቤ ውስጥ ሳይገቡ ብዙ ዓመታት ባክነዋል።
፯. ቁቤ በላቲን ዋየሎች ከሚጠቀምባቸው በተሻለ ኣፋን ኦሮሞ በግዕዙ ሊጠቀም ይችላል። የኦሮምኛን ፊደል ለመክተብ ከላቲኑ ቁቤ የግዕዝ ፊደል ይጠቅማል።
፰. መጽሓፍ ቅዱስ በከፊል እ.ኤ.ኣ. በ1841 በኦሮሞ ቋንቋ በግዕዝ ፊደል ተጽፏል።  እንዲሁም እ.ኤ.ኣ. በ1875 የኦሮሞ ሓዲስ ኪዳን በግዕዝ ፊደል
ታትሟል።
፱. በልሳነ ግእዝና በኣፋን ኦሮሞ (ግእዚፊ ኣፋን ኦሮሞቲን – Giiiziifi Afaan Oromootiin) የተዘጋጀው መጽሓፈ ቅዳሴ – ክታበ ቅዳሴ – Kitaaba Qiddaasee መጋቢት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. በኢሊሌ ሆቴል ተመርቋል። የትርጐማና የኣርትኦት ሥራው 10 ዓመታት የወሰደው ባለ ሦስት ዓምዱ ክታበ ቅዳሴ፦ የመጀመርያው ረድፍ በግእዝ ቋንቋ፣ ሁለተኛው ረድፍ በኦሮምኛ ሆኖ በግእዝ ፊደል፣ ሦስተኛው ረድፍ በኦሮምኛ ሆኖ በቁቤ ፊደል ተጽፏል ይላል ሪፖርተር ጋዜጣ። ይህ የግዕዝ ፊደል ኦሮምኛን ኣይጽፍም ለሚሉት ማፈሪያ ነው።
፲. መጽሓፍ ቅዱስ ሙሉዉን ወይም በከፊል ከ፲፭፻፮ ዓ.ም. ጀምሮ በግዕዝ ቀለሞች በማተሚያ ቤቶች ከታተሙባቸው ቋንቋዎች መካከል የግዕዝ ቋንቋ(ግዕዝኛ)፣ ዓማርኛ፣ ትግርኛ፣ ኦሮምኛ ፣ ሃዲያ፣ ሲዳሞ፣ ከምባታ ፣ ወላይታና ጌዴኦ ይገኙበታል። ስለዚህ ለዓመታት በማተሚያ ቤቶች የግዕዝ ፊደላት ሲከተብ የነበረው ኦሮምኛ ኮምፕዩተራይዝ ሆኖ ዛሬ ሥራ ላይ እየዋለ ግዕዝ ኦሮምኛን ኣይጽፍም ማለት ሳይንስ ኣይደለም።
፲፩. በኣነሰ የኆኄያት ግድፈቶች (Spelling / እስፔሊንግ) እና ስፍራዎች (Spaces) ማስከተብ ብልጫዎች የነበረው የግዕዝ ፊደል በዶ/ር ኣበራ ፈጠራ የተነሳ የግዕዝ ፊደል ሓሳብን በኣነሰ ጊዜ (Time)፣ መርገጫዎች (Keystrokes) እና ገበታዎች (Keyboards) በኮምፕዩተሮችና የእጅ ስልኮች በማስከተብ ብልጫዎቹ ወደ ኣምስት ዓይነቶች ከፍ ብለዋል። ለምሳሌ ያህል “ዘ ኲክ ብራውን ፎክስ ጃምፕስ ኦቨር ዘ ሌይዚ ዶግ።” የሚለውን ዓረፍተ ነገር ላቲን በ36 ቀለሞችና በቁቤ በ45 ቀለሞች ከመክተብ ይልቅ በግዕዝ ፊደል በ24 ቀለሞች መክተብ የተሻለ ነው።
፲፪. የቁቤ ሥርዓት እ.ኤ.ኣ. በ1992 ገደማ የተመሠረተው ኣንዱ ቀለም ኣንድን ድምጽ በመወከል ነው ተብሏል። የላቲንም ሆነ የቁቤ ቀለሞች ኣንድን ድምፅ በኣንድ ቀለም ከሚወክለው የግዕዝ ፊደል ጋር የመወዳደር ችሎታ የላቸውም። ላቲን ኣንድኣንድ ድምጾችን የሚከትበው በሁለት ቀለሞች ስለሆነ ሁሉም ቀለሞች ለየብቻቸው ኣንድ ድምጽ እንዲወክሉ እንኳን ተደርጎ መጠቀም ኣይቻልም። ለምሳሌ ያህል “d” እና “h” የ“ዽ” እስፔሊንግ ስለሆኑ “ዲ” እና “ኤች”ን በሁለት ቀለምነት ጎን ለጎን ኣስቀምጦ በ“d” እና “h” ድምጽ ሰጪነት መጠቀም ኣይቻልም። ይህ ምሳሌ የሚያሳየው ቁቤ የተመሠረተው በጥቂት የኦሮሞ
ምሁራን ማምታታትም ላይ መመርኰዙን ነው።
፲፫. ማንኛውንም የኦሮሞ ፊደል በሦስት መርገጫዎች መክተብ ነውር ነው። ማንኛውንም የኦሮምኛ ድምጽ በሦስት መርገጫዎች መክተብ ነውር ነው።
፲፬. ጥቂት የኦሮሞ ምሁራን ዓማርኛ የማጥበቂያ ምልክት የለውም የሚሏቸውን ስሕተቶች ቀጥለውበታል። ዓማርኛ መጥበቅ የኣለበትን ቃል ከማይጠብቀው የሚለይበት ሁለት ዘዴዎች ኣሉት። ከእነዚህ ኣንዱ ከሚጠብቀው ቀለም ኣናት በላይ ኣንድ ነጥብ መክተብ ሲሆን ምሳሌውም በ፲፮፻፺ ዓ.ም. ታትሟል። ይኸንንም ኣጠቃቀም ሓዲስ ዓለማየሁ [887] በ“ፍቅር እስከ መቃብር” መጽሓፋቸው ኣስፋፍተውታል። በኣዲስ ቅርጽ ለኮምፕዩተር እንዲስማማ መጥበቅ ከኣለበት ቀለም ኋላ እንዲከተብ ተደርጎ ማጥበቂያ በዶክተሩ ፓተንትም ውስጥ ኣ.ኤ.ኣ. በ2009 ተጠቅሷል።
፲፭. የቁቤ ዋየሎች “ኤ”፣ “ኢ”፣ “ኣይ”፣ “ኦ” እና “ዩ” (“a”፣ “e”፣ “i”፣ “o” አና “u”) ስለሆኑ በቁቤ “ክታበ”ን ከ“ኪታባ” የመለየት ችግሮች ኣሉት። ይህ በኣዲስ ፊደልነት የቀረበውንም [889] ይመለከታል። ግዕዝ ሰባት እንዚራን ሲኖረው ኦሮምኛ 10 ያስፈልጉታል የተባለው ትክክል ከኣለመሆኑም ሌላ ቍጥሩን መጨመርም ስለኣላዋጣም ኣልቀጠለም።
፲፮. ይህ ግዕዝና ኦሮሚፋ ሳይንሳዊ ጽሑፍ ስለ ፊደላቱ እንጂ ቋንቋዎቹን ኣይመለከትም። የኦሮሞ ቋንቋችን መዳከም ስለሌለበት ስለ ፊደል ስንወያይ ሰለኣልፈጠርናቸው ቋንቋና ኦሮሞነት መቀላቀል ሳይንስ ኣይደለም።
፲፯. እነ “ሸ”፣ “ቸ”፣ “ኘ”፣ “ዸ”፣ “ጠ”፣ “ጨ”፣ “ጰ”፣ እንዚራኖቹንና ሌሎች ቀለሞች የኣሉትን ለኦሮምኛ የሚያስፈልጉትን ቀለሞች ትቶ እነዚህን ወደ የሌሉት የላቲን
ፊደል መዞር ሳይንስ ኣይደለም።
፲፰. የኦሮምኛ ድምጾችንና እርባታዎችን የሚወክል የፊደል ገበታ (ከኣማርኛ ታይፕራይተር፣ ዓረብኛና ላቲን) ለጊዜው የተሻለው ላቲን ነው በማለት በስሕተት የቁቤ
ኣጻጻፍ ሥራ ላይ ዋለ። ይህ ለዓማርኛው በኣለመደረጉ ዶክተሩ በመፍትሔው የደረሱለት ለኣፋን ኦሮሞ ጭምር ነው። ምክንያቱም ዓማርኛና ኣፋን ኦሮሞ በትክክለኛው የግዕዝ ፊደል ለብዙ ምዕት ዓመታት ተጠቅመዋል።  የጄምስ ብሩስና ሌሎች መረጃዎችም ኣሉ። ስለዚህ ዓማርኛውንም ሆነ ሌሎችን ቋንቋዎቻችን ለማይጽፈው የዓማርኛ ታይፕራይተር ሲባል ፊደሉን የተዉት ቋንቋዎች በኣንድኣንድ ተናጋሪዎች ስሕተት እንጂ በግዕዝ ፊደል ሲጠቀሙ በነበሩ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ስሕተት ኣልነበረም።
፲፱. በዶክተሩ ፈጠራዎች ከ“አ” እና “ኸ” መርገጫዎች ፲፬ የግዕዝ ቀለሞች እየተከተቡ ናቸው።
፳. ቁቤ በ“a”፣ “e”፣ “i”፣ “o” እና “u” በተጠቀመው ዓይነት በ“ኣ”፣ “ኤ”፣ “ኢ”፣ “ኦ” እና “ኡ” የግዕዝ ቀለሞች መጠቀም ይችል ነበር። ኣንዳንድ ኦሮሞዎች “ቢራ” በላቲን ኦሮሚፋ “biirraa” ተብሎ የሚጻፈው ግዕዝ ስለማይችለውም ነው ይላሉ። በ“biirraa” ምትክ “ብኢኢርርኣኣ” ተብሎ በግዕዝ ፊደል መጻፍ ይቻላል። ስለዚህ ቁቤ የተመሠረተው ሳይንሳዊ ጥቅም ላይ ኣይደለም። “ቢ” እና “ራ” ቀለሞችን ዓማርኛ በኣራት ዓይነቶች ማለትም “ቢራ”፣ “ቢ’ራ”፣ “ቢራ’” አና “ቢ’ራ’” መጠቀም ይችላል።
፳፩. ኣንድኣንድ የኦሮሞ ምሁራን ግዕዝ የኦሮምኛ ቃላትን ኣይጽፍም በማለቱ በኣለማወቅ በስሕተቱ ገፍተውበታል። ጎዸቱ፣ ቶኮፋዸ፣ ዹፌ፣ ዹጉማ፣ ጀዺ፣ ዻባ፣ ዻራርቱ፣ ባዻዻ፣ ዻዻ፣ ጄዼ፣ ዼራ፣ ዽባፍ፣ ዽባ፣ ነንዾከዼስ ምሳሌዎች ናቸው።
፳፪. ጥቂት የኦሮሞ ምሁራን “ዻ” የግዕዝ ኦሮምኛ ቀለም በኣንድ ቀለም በሁለት መርገጫዎች ከመክተብ ይልቅ “dha” በማለት በሦስት ቀለሞችና በሦስት መርገጫዎች በኦሮሚፋ መክተብ የተሻለ ሳይንስ ይመስላቸዋል።
፳፫. በሚገባ ሳይታሰብበት የግዕዝ ቀለሞች በላጭነት ጥቅሞች ሳይገለጹ ታልፈዋል። ምሳሌ፦ ግዕዝ ችግር የለውም ማለት ሳይሆን የላቲን ቃላት እስፔሊንግ እድሜ ልክ ቢማሩትም ማስታወስ ኣይቻልም። በእዚህ ላይ “ኦሮሞ” የሚለው ቃል እስፔሊንግ በላቲን “Oromo” በኦሮሚፋ የኣለ በቂ ምክንያት “Oromoo” ነው።
፳፬. በኣጠቃቀም የላቲን ፊደል ከግዕዝ ሳድሳን ቀለሞች ጋር ኣንድ ዓይነት ነው። ግዕዝ እንዚራኑን በኣንድኣንድ ቀለሞች ሲወክል ላቲን ዋየሎቹን ሳድሳኑ ጎን ማስከተብ ስለኣለበት ከሰባት ጊዜ በላይ እጥፍ ስፍራዎች ያስባክናል።
፳፭. ጥቂት የኦሮሞ ምሁራን በስሕተት ኦሮሚፋ 10 እንዚራን ሲያስፈልገው ግዕዝ ሰባት ብቻ ኣለው ይላሉ። ዋየል መደራረብ ትርፉ ስፍራ ማባከን ነው።
፳፮. ጥቂት የኦሮሞ ምሁራን በስሕተት ላቲን 26 ቀለሞች ሲኖሩት የግዕዙ ብዙ ናቸው ይላሉ። የላቲን “a” ዓይነቶች ከ26 በላይ ናቸው።
ኦሮምኛን ጨምሮ እሱ ለኢትዮጵያ ቋንቋዎች የፈጸመውን ተግባር ሁሉ በሚከተለው የዊኪፒዲያ ሊንክ ማግኘት ይቻላል።
ምሁራንና አክቲቪስት ለአቶ ገዱ አንዳርጋቸው ከአንድ አመት ተኩል በፊት ከጻፉት ደብዳቤ የተወሰደ ነው።
Filed in: Amharic