>

ባለአስር ነጥቡ የመቐለ ስብሰባ የአቋም መግለጫ

ባለአስር ነጥቡ የመቐለ ስብሰባ የአቋም መግለጫ
በትግራይ ክልል  አስተባባሪነት ከ38 ያላነሱ ፓርቲዎች ከነሐሴ 20 እስከ 21 ቀን 2011 ዓ.ም በመቐለ ከተማ ተገናኝተው ሕገ መንግስትንና ህብረ ብሔራዊ የፌደራሊዝም ስርዓት የማዳን አገር አቀፍ ስብሰባ ካካሄዱ በኋላ የሚከተለውን የአቋም መግለጫ አውጥተዋል።
***
ሀገራችን ኢትዮጵያ የብዝሃነት ሃገር እንደመሆንዋ ልዩነታችንን እውቅና ሰጥቶ ሊያስተናግድ ካልቻለ አገዛዝና ጭቆና ህዝቦቿ ለመታደግ በየዘመኑ በተደረገው በማያቋርጥ ህዝባዊ ትግል በዓላማውና እና ይዘቱ ብዙሀነትን ሊያስተናግድ እና ዲሞክራሲያዊው ስርዓት ለመገንባት መሰረት የጣለ ህገ መንግስት በብሔሮች፣ ብሔረ ሰቦች፣ ህዝቦች ይሁንታ ፀድቆ ህብረ ብሔራዊ ፌደራላዊ ስርዓት ከተመሰረተ ሶስት ዓስርት ዓመታት ሊሆነን ነው። በነዚህ ሶስት አስርት ዓመታትም በሁሉንም ዘርፍ የተገመዘገቡ ውጤቶች ብዙ ናቸው።
በነዚህ ዓመታት ውስጥ ህብረ ብሄራዊ ፌደራሊዝም ስርዓት ለሃገራችን አዲስ ከመሆኑ ጋር፣ እኛ ኢትዮጵውያን እንደብዝሃነታችን በመስተጋብራችን ውስጥ በርካታ ቅራኔዎች የነበሩን እና አሁንም ያልተፈቱ በመሆናቸው የፌደራሊዝም ስርዓቱ ያስገኛቸው ውጤቶች አዳዲስ የተፈጠሩ ችግሮችን በማጉላት ተሸፍነዋል። በሌላ በኩል ዲሞግራፊ ሽግግር ሊመጥን የማይችል መንግስታዊ አመራር ሰጭነት የአቅም ውስንነት፣ ይህንንም ተከትሎ የተንሰራፋው ኪራይ ሰብሳቢነት የፖለቲካ ኢኮኖሚ ጎልቶ መታየቱ ህዝቡን ለሪፎርም እንዲነሳሳ ካደረጉት ጥቂቶች ናቸው።
ኢህአዴግ በሃገሪቱ እየተፈጠረ ለመጣው ህዝባዊ እምቢተኝነት ምላሽ ለመስጠት ጥልቅ ተሃድሶ አደርጋለሁ ብሎ ነበር። ከዚህም ተነስቶ የአመራር ለውጥም እስከ ማድረግ ደርሷል። በዚህ አዲሱ አመራር የመጀመርያው ሰሞን ህዝቡን ያነቃቃ እና ተስፋ የሰነቀ ተወስደዋል። ኢህኣዴግ የሚመራው መንግስት መሻሻል እየታየበት እንደሆነ ህዝቡ ተረድቶ ጊዜ ይሰጠው በሚል በጎ አስተሳሰብ ለሪፎሪሙ የበኩሉን ድጋፍ በመስጠት አስተዋፅኦ አድርጓል። ይሁን እንጂ የለውጡ ፈላጊና ባለቤቱ የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦች እና ሕዝቦች መሆናቸው ተዘንግቶ የለውጡ ተጠቃሚዎች መሆን ሲገባቸው በአንፃሩ በማንነታቸውና በብሄራቸው መገደል፣ መፈናቀልና ጥቃት እየደረሰባቸው ይገኛል። በሌላ በኩል ይህንን የለውጥ ሂደት እንደ አጋጣሚ በመጠቀም አንዳንድ ግለሰቦችና ቡድኖች የኢትዮጵያ ህዝብ አንድነትና ጥንካሬ ከማይፈልጉ የውስጥና የውጭ ሃይሎችን አስተሳሰብ በመጋራት ከመቸውም ጊዜ በላይ ህብረ ብሄራዊ ፌደራላዊ ስርአቱን ለማፍረስ እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ። ስርኣቱን የማፍረስ ተግባር የጀመረው ደግሞ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ግልፅ እየሆነ የመጣው የብሄሮች፣ ብሔረ ሰቦች፣ ህዝቦች ህገ መንግስታዊ መብቶቻቸው እየተናደ መምጣቱ፤ ዜጎች በሁሉም የሃገሪቱ ቦታዎች የመዘዋወር፣ ሰርቶ የመኖርና ሃብት የማፍራት ሕገ መንግስታዊ መብቶች አለመከበራቸውና የሕዝቦች ሰላምና ደህንነት አደጋ ውስጥ መግባቱን፤ በአጠቃላይ የህግ የበላይነት ለማስከበር የመንግስት ሚና ዜጎችን ሊታደግ አለመቻሉ ሃገራችን ወዴት እያመራች ለመሆኑ የዕለት ተእለት የሃገራችን ፓለቲካዊ እንቅስቃሴ በግልፅ ይጠቁመናል። በአጭሩ ህገ መንግስታችንና በዚህ ላይ የቆመው ህብረ ብሄራዊ ፌደራል ስርዓታችን የህልወና አደጋ ተጋርጦበታል።
የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሔረ ሰቦች፣ ህዝቦች በኑሮ ውድነት፣ ከቦታ ቦታ ለመዘዋወር ባልተቻለበት፣ በሕገ መንግስቱ የተረጋገጠላቸው መብቶችና ነፃነቶች በተጣሰበት ወቅት የትግራይ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ተነሳሽነቱን በመውሰድ “ህገ መንግስትንና ሕብረ – ብሄራዊ ፌደራላዊ ስርኣትን የማዳን ሀገር አቀፍ መድረክ” ማዘጋጀቱ ሕብረ ብሄራዊ ፌደራላዊ ስርኣትን ማዳን ማለት ዛሬ ሃገራችን ኢትዮጵያ ከገጠማት የመበታተን አደጋ መታደግ በመሆኑ በእኩልነት የተመሰረተ አንድነታችንን ጠብቀን ኢትዮጵያን እንደ ሃገር የማስቀጠል ተግባር ነው ብለን እናምናለን። የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስትና ህዝብ ምስጋና ሊደርሳቸው ይገባል።
ስለዚህም ከነሐሴ 20 – 21/2011 በመቀሌ ከተማ በተደረገው ሀገር አቀፍ መድረክ ከመላው ኢትዮጵያ ጥሪ ተደርጎልን የተሳተፍን ኢትዮጵውያን በመድረኩ በምሁራን የቀረቡትን ጥናታዊ መነሻ ፅሑፎች አድምጠን ባደረግነው ሰፊ ውይይትና ተሳትፎ የጋራ መግባት ላይ ደርሰናል። በዚሁም መሰረት ባቋቋምነው የጋራ አስተባባሪና አመቻች ኮሚቴ አማካይነት የተሰማማንባቸው ጉዳዮች ወደ ተግባር እንዲቀየሩ የሚኪተለውን የአቋም መግለጫ በጋራ አውጥተናል፦
1. ህብረ ብሄራዊ ፌደራላዊ ስርኣቱ አደጋ ላይ ነው ሲባል የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦች፣ ህዝቦች ነፃነትና መብቶቻቸው አደጋ ላይ ወድቋል ማለት ነው። በሌላ በኩልም እነዚህ ነፃነትችና መብቶች እንዲጣሱ መንቀሳቀስ የፌደረሽን ምክር ቤት ተቋማዊ ህልውናውን መፈታተንም ጭምር በመሆኑ ህገ መንግስቱንና ህብረ ብሔራዊ ፌደራላዊ ስርኣቱን ለማዳን የተጀመረውን ሃገር አቀፍ መድረክ በሁሉም ብሄራዊ ክልሎች እና በሁለቱም የከተማ መስተዳደሮች ተመሳሳይ መድረኮች እንዲፈጠሩ ሁሉም ያገባኛል የሚሉ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
2. የኢፌዲሪ ህገ – መንግስት የህዝቡን አንድነትና ልዩነት ተገንዝቦ በህዝቦች ይሁንታ የፀደቀ የሁሉንም ብሔሮች፣ ብሔረ ሰቦች ህዝቦች የቃል ኪዳን ሰነድ በመሆኑ ሁሉም የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች የምንገዛበት እንዲሁም ሁለንተናዊ የጋራ ደህንነታቻንና አብሮነታችን አደጋ ሲያጋጥመው የብሄር፣ የቋንቋ፣ የሃይማኖት፣ የፆታ፣ የእድሜ በአጠቃላይ ብዝሃነታችን ሳይገደብን ህብረ – ብሄራዊ ፌደራል ስርኣቱ በህገወጦች እንዳይናድ በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ቃል እንገባለን።
3. ከነሐሴ 20 – 21/2011 ዓ/ም በመቐለ ከተማ ብሔሮች፣ ብሔረ ሰቦች፣ ህዝቦች ብሎም ሃገራቸውን ኢትዮጵያን ለማዳን የተካሄደው አገር አቀፍ መድረክ መነሻ ሆኖ የዜጎች ሰላምና የሕግ የበላይነት እስኪረጋገጥ ድረስ በሁሉም ብሄራዊ ክልሎች፣ በአዲስ አበባና ድሬዳዋ ከተሞች ተመሳሳይ መድረክ እንዲፈጠር የፌደራልና የክልል መንግስታት የበኩላቸውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ሀገር የማዳን ጥሪያችንን እናቀርባለን።
4. በዚህ ሃገር የማዳን መድረክ የተደረሰባቸውን መግባባቶችና የአቋም መግለጫዎችን ወደ ተግባር ለመቀየር ለተቋቋመው አገር አቀፍ አስተባባሪ ኮሚቴ የሚያደርገው እንቅስቃሴ ሁሉም ባለድርሻ አካላትና ህዝቡ ድጋፍና እገዛ እንዲያደርግላቸው ጥሪ እናስተላልፋለን።
5. ህብረ – ብሄራዊ ፌደራል ስርኣቱን ከአደጋ መታደግ የኢትዮጵያዊነትን እንደ ሃገር ማስቀጠልና የሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የጋራና የተናጠል ሃላፊነት በመሆኑ የመንግስትና የግል የመገናኛ ብዙሃን ተገቢውን መረጃ እየተከታተሉ ከህዝቡ እንዲያደርሱና በልዩ ልዩ ፕሮግራም ግንዛቤ እንዲፈጥሩ ሃገር የማዳን ጥሪ እናቀርባለን።
6. የሃይማኖትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ሃገርን በማዳን አላማ ስኬት የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ጥሪ እናቀርባለን።
7. ህገ – መንግስታዊ ስርኣቱን ማዳን ማለት በህገ – መንግስቱ የተገለፁቱን ድንጋጌዎች ማክበር እና መተግበር ማለት ነው። በመሆኑም ህገ – መንግስቱ በሚፈቅደው ህጋዊ አግባብ መጭው ምርጫ በጊዜው እንዲተገበር በአፅንኦት እናሳስባለን።
8. ኢትዮጵያ ሀገራችን የሰው ዘር መገኛ ታላቅ ሃገር በመሆኗ ለአፍሪካ ሃገሮች በፀረ – ቅኝ ግዛት የነፃነት ትግላቸው ወቅት ተሳትፎ የነበራት ነበረች። ዛሬም ቢሆን በሰላም ማስከበሩና በአለም አቀፍ ፓለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ተሳትፎ በማድረግ ለአለም ብዙ አስተዋፅኦ ያላት ሃገር ናት። ኢትዮጵያን የሚወዱ አለም አቀፍ ድርጅቶችና ሀገሮች ከገጠመን የአደጋ ስጋት ለመታደግ አዎንታዊ ድጋፋቸው እንዳይለየን ጥሪ እናቀርባለን።
9. በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ውስጣዊ ውህደነቱና የአላማ አንድነቱ በከፍተኛ ግራ መጋባትና መጓተት ውስጥ የሚገኘው ገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ ፣ በህዝቦቻችን በአጠቃላይ እና በሕብረ – ብሄራዊ ፌደራሊዝም ቀጣይነት ላይ ይህ ቁመናው ያዘለውን አደጋ በመገንዘብ ህጋዊና ታሪካዊ ኃላፊነቱን እንዲወጣ በአፅንኦት እንጠይቃለን።
10. ከህዝቦቻችን የተለያዩ አዳጊ ፍላጎቶች በመነጨ የሚያስፈልጉ የተለያዩ ህጋዊና ሕገ – መንግስታዊ መሻሻሎች ተገቢ ናቸው ብለን እናምናለን። ይሁንና እነዚህ እርምጃዎችና ማሻሻያዎች ህገ – መንግስታዊ መንገድ የተከተሉ እና የኢትዮጵያን ብሄሮች ፣ ብሄረሰቦች እና ሕዝቦች ሉአላዊ ስልጣን የማይጋፋ እንዲሆን ለሁሉም ወገኖች በአፅንኦት እናሳውቃለን።
ነሃሴ 21/2011
መቐለ
Filed in: Amharic