>

ሌሎችን ይነክሳል ብለህ የተዉከው ውሻ...!!! (ዳንኤል ክብረት)

ሌሎችን ይነክሳል ብለህ የተዉከው ውሻ…!!!
ዳንኤል ክብረት
አሜሪካ ታሊባንን ስትረዳ ያሰበቺው ሶቪየት ኅብረትን ለመውጋት ነበር፡፡ ቢን ላደንን ስታሠለጥን ሌሎችን ለመውጋት እንዲረዳት ነበር፡፡ በመጨረሻ ግን ትልቁን ኪሣራ ያተረፈቺው ራሷ አሜሪካ ሆነች፡፡ ሌላውን እንዲነክስ ያሠለጠነቺው ውሻ ራሷን ነከሣት፡፡
‹ሌሎች› እንደሚል አስተሳሰብ ያለ ጎጂ የለም፡፡ ሰውን ‹ወገን›ና ሌላ ብሎ የሚከፍል አካል ሕጉንና አሠራሩን ሁሉ ለሁለት ይከፍለዋል፡፡ ‹ወገን› ለሚለውና ‹ሌላ› ለሚለው፡፡ ይህ ጉዳይ በባለ ሥልጣናትና በፍትሕ አካላት እየተዛመተ ከሄደ ደግሞ ሀገርን የሚያጠፋ ይሆናል፡፡ በቋንቋ፣ በባህል፣ በጾታ፣ በእምነት፣ በአመለካከት ብዙ ሌሎች ይፈጠራሉ፡፡ እነዚህ ‹ሌሎች› እየተገፉና እየተከፉ በሄዱ ቁጥር ብዙ ሌሎች ‹ብሶትንና ጥቃትን› ብቻ መሠረት አድርገው ይሰባሰባሉ፡፡ ያን ጊዜ ነው ሕዝባዊ አብዮት የሚፈነዳው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ክርስቲያኖችን ‹ሌሎች› አድርገው በሚያስቡ አካላት ዘንድ በክርስቲያኖች ላይ ጥቃቶች እየተሠነዘሩ ነው፡፡ ክርስቲያኖች በአሰቃቂ ሁኔታ ይገደላሉ፤ አብያተ ክርስቲያናት ይቃጠላሉ፣ የክርስቲያኖች ንብረቶች ይወድማሉ፤ ይዘረፋሉ፡፡ ሴቶች ይደፈራሉ፣ እምነታቸውን እንዲቀይሩ በኃይል ይገደዳሉ፡፡ ይህ ሁሉ ሲከናወን አንዳንድ የአካባቢ መስተዳድር ኃላፊዎችና የጸጥታ አካላት በዝምታ ይመለከታሉ፤ ከቻሉም የተደረገውን አልተደረገም ብለው ይክዳሉ፡፡ የመስተዳድር አካላትና የአካባቢ የጸጥታ አካላቱ ራሳቸውን የሚመዝኑት ‹የራስ ወገን› ከሚሉት አቅጣጫ ብቻ ሆኗል፡፡ እነርሱ ‹ሌሎች› የሚሏቸውን ከአደጋ አይጠብቁም፤ መብታቸውን አያከብሩም፣ በአሰቃቂ ሁኔታ ሲገደሉም በዝምታ ይመለከታሉ፡፡ ለምን? ተብለው ሲጠየቁ ‹እየሞቱ ያሉት ሌሎች ናቸው› ይላሉ፡፡ ዜጎችን ‹ወገኖች›ና ‹ሌሎች› ብለው ይከፍላሉ፡፡ እነርሱ ‹ሌሎች› የሚሆኑበት ዘመን ሩቅ ይመስላቸዋል፡፡ ትናንት ሌሎችን ‹ሌሎች› ሲሉ የነበሩ አካላት ዛሬ ራሳቸው ‹ሌሎች› መሆናቸውን ረስተውታል፡፡
ውሻው ሌሎችን ብቻ ነክሶ አያቆምም፤ በመጨረሻ ባለቤቱንም ይነክሳል፡፡
Filed in: Amharic