>

በግብረ ሕማማት ውስጥ የሚገኙ እንግዳ ቃላት እና ትርጉማቸው (ቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅ)

በግብረ ሕማማት ውስጥ የሚገኙ እንግዳ ቃላት እና ትርጉማቸው:-

ቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅ
በግብረ ሕማማት ውስጥ ወደ ግእዝም ሆነ በኋላ ወደ አማርኛ ሳይተረጎሙ የተቀመጡ የዕብራይስጥ፣ የቅብጥ እና የግሪክ ቃላት ይገኛሉ፡፡ የእነዚህ ቃላት ትርጉም የሚከተለው ነው፡፡
ኪርያላይሶን
ቃሉ የግሪክ ሲሆን አጠራሩ «ኪርዬ ኤሌይሶን»ነው፡፡ «ኪርያ» ማለት «እግዝእትነ» ማለት ሲሆን «ኪርዬ» ማለት ደግሞ «እግዚኦ» ማለት ነው፡፡ ሲጠራም «ኪርዬ ኤሌይሶን» መባል አለበት፡፡ ትርጉሙ «አቤቱ ማረን»ማለት ነው፡፡ «ኪርያላይሶን» የምንለው በተለምዶ ነው፡፡ ይኼውም ኪርዬ ከሚለው «ዬ» ኤላይሶን ከሚለው ደግሞ«ኤ» በመሳሳባቸው በአማርኛ «ያ»ን ፈጥረው ነው፡፡
ናይናን
የቅብጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙ «መሐረነ፣ ማረን» ማለት ነው፡፡
እብኖዲ
የቅብጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙ «አምላክ» ማለት ነው፡፡ «እብኖዲ ናይናን» ሲልም «አምላክ ሆይ ማረን» ማለቱ ነው
ታኦስ፦
የግሪክ ቃል ሲሆን ትርጉሙ «ጌታ፣ አምላክ» ማለት ነው፡፡ «ታኦስ ናይናን» ማለትም «ጌታ ሆይ ማረን» ማለት ነው፡፡
ማስያስ
የዕብራይስጥ ቃል ሲሆነ ትርጉሙ «መሲሕ» ማለት ነው፡፡ «ማስያስ ናይናን» ሲልም «መሲሕ ሆይ ማረን» ማለት ነው
ትስቡጣ
«ዴስፓታ» ከሚለው የግሪክ ቃል የመጣ ሲሆን ትርጉሙም “ደግ ገዥ” ማለት ነው
አምንስቲቲ ሙኪርያቱ አንቲ ፋሲልያሱ
የቅብጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙም «ተዘከረነ እግዚኦ በውስተ መንግሥትከ- አቤቱ በመንግሥትህ አስበኝ» ማለት ነው፡፡
አምንስቲቲ ሙዓግያ አንቲ ፋሲልያሱ
የቅብጥ ቃል ሲሆን «ተዘከረነ ኦ ቅዱስ በውስተ መንግሥትከ -ቅዱስ ሆይ በመንግሥትህ አስበን» ማለት ነው፡፡
አምንስቲቲ ሙዳሱጣ አንቲ ፋሲልያሱ
የቅብጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙም «ተዘከረነ እግዚአ ኩሉ በውስተ መንግሥትከ- የሁሉ የበላይ የሆንክ ወይ በመንግሥትህ አስበን» ማለት ነው ።
~
(የቅብጥ ቋንቋ ጥንታዊ የምስር ልሳን ፊደሉ ከጽርእ ፊደል አንድነት ያለው። )
Filed in: Amharic