>
5:13 pm - Thursday April 19, 6553

የሐረሬ ክልል ምክርቤት ጉዳይ...!!! (ኤርሚያስ ለገሰ)

የሐረሬ ክልል ምክርቤት ጉዳይ…!!!

ኤርሚያስ ለገሰ

*.. የቀድሞ ሐብሊና ኦህዴድ ( የአሁን የሐረሬና የኦሮሞ ብልፅግና) ውስጣዊ ስምምነት
 
አንዳንድ ወዳጆቼ ከሳምንታት በፊት የሐረሬ ክልል ምክርቤት ጉዳይ ተወዳዳሪዎቹም ሳይታወቁ አስቀድሞ “የተበላ ዕቁብ” ነው ማለቴን የበለጠ እንዳፍታታው ጠይቃችሁኛል። ስሌቱ በጣም ቀላል ነው። የሒሳብ አስተማሪ ወይም ተማሪ መሆን አይጠይቅም። በአጭሩ የሐረሬን ክልላዊ ሕገ መንግሥት ገለጥ ገለጥ አድርጎ ያነበበ እና የቀደምት ልምዱን የቀመረ ሰው ጥያቄው በቀላሉ ይመለስለታል።
               1. ጥሬ ሐቆች
1.1.    የሐረሬ ክልል ምክርቤት 36 ወንበሮች አሉት።
1.2.    ከ36 ወንበር ውስጥ 18 በቀጥታ ለሐረሬ ብሔረሰብ የተሰጠ ነው። ከዚህ ውስጥ 14ቱ በየትኛውም ጫፍ ያለ ሐረሬ ተሰብስቦ እርስ በራስ የሚመራረጡበት ነው። የተቀረው 4 ወንበር በጀጐል ልዩ ምርጫ ዞን ውስጥ ለሚኖሩ ሐረሬዎች ብቻ ለምርጫ የሚመደብ ነው። በአገሪቱ የምርጫ ሕግ የሚመራ ቢሆን ኖሮ ጀጐል አንድ ወንበር አይመደብለትም ነበር። ይህም ሆኖ ሐረሬዎች 14ቱ ምደባዎች እና 4ቱ የሐረሬ ብሔረሰብ ምርጫ ካልተዛመዱ ( 1 ወንበር ቢቀነስ እንኳን) ክልላዊ አስተዳደራዊነታቸውን ያጣሉ። “የሐረሬ ክልላዊ መንግስት” የሚባለውን ስያሜ ብቻ ይዘው ይቀራሉ። በዚህም ምክንያት ሰማይ ዝቅ ቢል፣ ምድር ከፍ ቢል የትኛውም ፓርቲ ድርሽ እንዲል አያደርጉትም።
1.3.   ከ36 ውስጥ 18 ወንበር ለኦሮሞ ድርጅቶች (ኤሊቶች) የተሰጠ ነው። ለኦህዴድ( የኦሮሞ ብልፅግና) እነዚህ ወንበሮች ለድርድር የማያቀርባቸው የህልውና ወንበሮቹ ናቸው። የክልላዊ መንግስቱ ቋንቋ ሐሬሪኛ እና ኦሮምኛን እንዲሁም የስልጣን እኩል ክፍፍልን የሚያስጠብቁት በእነዚህ ወንበር አማካኝነት ነው።
   2. የቀድሞ ሐብሊና ኦህዴድ ( የአሁን የሐረሬና የኦሮሞ ብልፅግና) ውስጣዊ ስምምነት
2.1.  ሁለቱም 18 እኩል እኩል ወንበር ይዘዋል።
2.2.   ምንጊዜም የክልሉ ፕሬዚዳንት ሐብሊ፤ ምክትል ፕሬዝዳንት ኦህዴድ ይሆናሉ። ሌሎችን የስልጣን ቦታዎች በእኩሌታ ይካፈሉታል።
2.3.     የክልላዊ መንግስቱ የስራ ቋንቋ በእኩሌታ ሐረሬኛ እና ኦሮምኛ ብቻ ይሆናሉ።
2.4.      የክልሉ አንደኛ ዜጎች ሐረሬና ኦሮሞ ብቻ ናቸው። ሌሎቹ በሙሉ ሁለተኛ ዜጐች ናቸው። ይህም በፓለቲካ ስልጣን፣ በኢኮኖሚ ዘርፍና በቢሮክራሲ ሽግግር የሚገለጽ ነው።
ማስታወሻ ፡- የአማራ ብልጽግና (ብአዴን) በተቃውሞ ድምፅ (Protesting Vote) መባረር አለበት የሚል አቋም ያራመድኩበት አንዱ ምክንያት ይህ ነው።
Filed in: Amharic