>

ጋዜጠኛ በፈቃዱ ሞረዳ ከ 16 ዓመት የስደት ዘመን በኋ ላ (ጸሀፊ ዘነበ ወላ)

“አንድ እንጀራ ለመብላት አንድ ሺህ አንድ አማራጮች ነበሩኝ – እኔ ግን ሙያውን ስለምወደው ፈተናው ደስ ያሰኘኝ ነበር!!!”
ጋዜጠኛና ደራሲ በፈቃዱ ሞረዳ 
ጸሀፊ ዘነበ ወላ

ጋዜጠኛና ደራሲ በፈቃዱ ሞረዳን ላለፉት ሶስት አስርት ዓመታት አውቀዋለሁ፡፡ ቀደም ብሎ አብዮታዊ ሠራዊት ውስጥ የአየር ወለድ መኮንን ሲሆን፤ 12 ጊዜ ከአየር ላይ ከዘለለ በኋላም የጦር ኃይሎች የሬዲዮ ፕሮግራም ባልደረባ ሆኖ ሰርቷል፡፡ በሽግግር ወቅት በግል መጽሔቶች ላይ ሲሰራ ከቆየ በኋላ የራሱን ‹ጦማር› የተሰኘች ሸንቋጭ ጋዜጣ መስርቶ በአዘጋጅነት መሥራት ጀመረ፡፡ በፍቃዱ አንድም ቀን ተረጋግቶ አይቼው አላውቅም፣ ሁሌም ሕይወቱ በጥድፊያ የተሞላች ነች፡፡ እንዲያም ሆኖ ወ/ሮ ፀሐይ ማሞን አግብቶ መናንና አሜንን ወለደ፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲም ስነጽሑፍና ቋንቋ ለመማር ተጣጥሯል፡፡ በጋዜጣው ሥራ እየተከሰሰ በርካታ ጊዜ ታስሯል፤ ታፍኗል። መሰደዱን ስሰማ ደግ አደረገ ነው ያልኩት፤ ሕይወቱ አደጋ ላይ እንደነበረች ይሰማኝ  ነበር። አትሙች ያላት ነፍስ፣ ከ16 ዓመታት የአሜሪካ ኑሮ በኋላ ወደ አገሩ መጣና ቁጭ ብለን አወጋን፤ ግሩም ቃለ ምልልስ ወጣው፡፡
‹‹ስትራመድ ትፈጥን ነበር ብለህኛል። ጊዜውም እየፈጠንክ እንድትራመድ ያስገድድሃል፤ በግል ፕሬሱ ሥራ ስጀምር “አሌፍ” መጽሔት፣ በኋላም “ህብር” ላይ ዋና አዘጋጅ ሆኜ እሰራ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ “ጦማር” ጋዜጣ ልክ በ1985 ዓ.ም ሥራ ጀመረች፡፡ እንደሚታወቀው ለሙያው ቅርብ ነኝ፡፡ ቀደም ብሎም ጦር ኃይሎች የሬዲዮ ፕሮግራም ውስጥ እሰራ ነበር፡፡ በአጠቃላይ ሙያውን መውደድ ብቻ ሳይሆን ሥራ ፈጥሮ ሰርቶ ለማደር የተደረገ ጥረት ነው፡፡
“ወቅቱ በርካታ ፈተና ነበረው፤ የቀድሞ መንግስትን ሲያገለግሉ ነበር ተብሎ በጠላትነት የምንፈረጅ፣ በአይነ ቁራኛ የምንታይ ሰዎች ነበርን፤ ትግሉ ከመንግስት ጋር ብቻ ሳይሆን፣ ከማህበረሰቡም ጋር ነበር ማለት ይቻላል። ዘርፉ አዲስ ነበር፣ ይህንን አዲስ ዘርፍ የግል ጋዜጣን ማጣጣም መቻል አዲስ የሆነ ነገር ነበር፡፡ በሙያው ውስጥ ካለህ የሙያው ስነ ምግባር አለ። አንባቢህ ወደ ኋላ ይጎትትሀል፡፡ የተጋጋለ የሚጮህ (ሴንሴሽናል) ነገር ይፈልጋል፤ እሱን ካላቀረብክ ገበያ የለም፡፡ እሱን ካደረግክ ደግሞ ከስርዓቱ ጋር ትጋጫለህ። በዚህም ክስ ተመስርቶብህ ፍርድ ቤት መቅረብ የግድ ይሆናል፡፡ ከ1985 ዓ.ም እስከ ምርጫ 1997 ዓ.ም በትንሹ ከአስራ አምስት ቀን እስከ 6 ወር ታስሬያለሁ፡፡ በቁጥር ብናስቀምጠው ወደ ስምንት ጊዜ ያህል እስር ቤት ተመላልሻለሁ፡፡”
“አይከብድም?”
“ይከብዳል፡፡ አንድ እንጀራ ለመብላት ከዚያ በኋላ አንድ ሺህ አንድ አማራጮች ነበሩኝ። እኔ ግን ሙያውን ስለምወደው ፈተናው ደስ ያሰኘኝ ነበር፡፡ ‹ቻሌንጅ› ከባድ ነው፤ ግን ደስ ያሰኘኛል፤ እውነቱን ለመናገር ሕብረተሰቡንም በአስተሳሰብ ወደ ላይ መሳብ አለብኝ በሚል እምነት አቅማችን በፈቀደ መጠን እኔና ጓዶቼ በአያሌው ለመስራት ጥረናል፡፡ የእኛ ጋዜጣ አንባቢዎቻችንን ያለመ ነበር፡፡ መካከለኛውን ክፍል መያዝ አለብን የሚል ነው እምነታችን። ‹ሚድል ክላስ› ስል ሐብት ሳይሆን በእውቀት መካከለኛው ክፍል አለ። እነሱን ለማግኘት ነው እንሰራ የነበረው፤ ልምዱም ሕይወቱም፣ ትምህርቱም ታክሎበት፣ የሕብረተሰባችንን አስተሳሰብ ስታየው ታች ነው ያለው፡፡ ይህንን ሕብረተሰብ እኛ ከላይ ምን እንዳለ እንዲያይ ወደ ላይ ለመሳብ እንጥራለን። ሕብረተሰቡ ደግሞ ወደ ታች ይስበናል፡፡ እንዲህ አይነቱ ፈተና ውስጥ ነበር፡፡”
‹‹አንዴ ከዚህ ከአዲስ አበባ ታፍነህ ተወስደህ ነበር?››
‹‹በእኛ ጊዜ ፖሊስ ሙሉ ስልጣን አለው፤ ይደውላል፣ ና ትባላለህ፣ ማዕከላዊ ወይም አንዱ ፖሊስ ጣቢያ ትጠራና ትሄዳለህ፡፡ እዚህ ቁም ይልሀል፣ ትቆማለህ፡፡ ወዲያው የሚያናግርህ የለም፡፡ የፈለገህን ፖሊስ ስትጠይቅ፣ ለሌላ ስራ ሄዷል ትባላለህ። እዚያው ማደር የግድ ነው፡፡ በነጋታው ከተፈታህ እሰየው ነው። ግን አይሆንም፤ እንዲህ አይነቱ መጉላላት በወር በሁለት ወር፣ ቢበዛ በአራት ወር አንዴ የሚገጥመን ፈተና ነበር፡፡
“ታፍኜ የሄድኩት ቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ነው፡፡ ወንጀል ሆኖ ለእንዲህ አይነቱ ችግር የዳረገኝ፣ አንድ አስተያየት ጋዜጣችን ዓምድ ላይ ጽፈን ማውጣታችን ነው፡፡ ይህ ‹ኦፖኒየን› ከክልሉ የተላከልን ነበር፡፡ ቤንሻንጉልን ስትመለከት በክልሉ ውስጥ አንድ አምስት ሕብረተሰብ አለ፡፡ በርታ ጉሙዝ እያልን ልንጠራ እንችላለን። ከእነዚህ ውስጥ አብዛኛው በርታ ነው። እነሱ በወቅቱ የክልሉ ፕሬዚዳንት በነበረው ያረጋል አይሸሹም አስተዳደር፣ ደስተኞች አልነበሩምና፣ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ሕጉን ጠቅሰው፣ የራሳቸውን ክልል ለመመስረት ጥያቄ አቀረቡ፡፡ በወቅቱ የምክር ቤቱ አፈ ጉባኤ ወ/ሮ አልማዝ መኮ ነበረች፡፡ እኛ የዚህን ደብዳቤ ኮፒ አገኘን፣ በዚያው ላይ ተመስርቶ የተፃፈልንን ደብዳቤ መሰረት በማድረግ፣ አቀናጅተን ለህትመን አበቃን፡፡ ይህ ነው የጦማር ወንጀል። ይህ ውሸት አይደለም፤ ይህንን እውነት ለምን አወጣችሁ? ነው፡፡
“በዚህም ስልክ ተደውሎልኝ ምንጩን ንገረኝ ተባልኩ፡፡ እንደማልችል ተናገርኩ፡፡ ምናልባትም ከእለታት በኋላ ሲቪል ልብስ የለበሱ ሰዎች ቢሮዬ መጥተው አሁንም ምንጩን ጠየቁኝ። ምንጩን መግለፅ የምችለው በሕጉ መሰረት ለፍርድ ቤት ነው፡፡ ለዛውም ለአገር ደህንነት የሚያሰጋና ይህንንም መረጃ መስጠት አገርን ማዳን መሆኑን ካመንኩበት ነው የምሰጠው፤ ፍርድ ቤትም በዚህ ጉዳይ አያስገድደኝም፤ ብዬ ተከራከርኩ፤ አንደኛው መታወቂያውን አሳየኝ፤ ፖሊስ ነው፡፡
‹‹እንሂድ አለኝ፤ የፍርድ ቤት መጥሪያ እንዳለው ጠየቅኩት፣ ከቤንሻንጉል ክልል የመጣውን አሳየኝ፡፡ የቤንሻንጉል ክልል ፖሊስ በእኔ ላይ ስልጣን የለውም፤ የፕሬስ ሕጉ ምን ይላል? ድንበር ተሻጋሪ በሆኑ የፕሬስ ውጤቶች ላይ ለተፈፀመው ወንጀል ስልጣኑ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ነው ይላል። ይህንን መሰረት አድርጌ ስከራከራቸው፤ ቀደም ብለው ተዘጋጅተውበታል፤ ከወረዳ 13 ፖሊሶች አራት ሰዎችን ይዘው መጡ። እነርሱ መጥሪያ ሰጡኝ። ይሄኔ ስልኬን አወጣሁና በወቅቱ የነፃ ፕሬስ ጋዜጠኞች ማህበር ፕሬዚዳንት ለነበረው ክፍሌ ሙላት ደውዬ ያለሁበትን ሁኔታ አሳወቅኩኝ። ወረዳ 13 ወስደው ለሰዓታት ትንሽ አቆዩኝ፤ ከቤንሻንጉል የመጡ ሌሎች ፖሊሶች ነበሩ፡፡ አንዱ የክልሉ አቃቤ ህግ ሲሆን ሌላው የፖሊስ ሠራዊት አባል ነው፡፡ ወደ አዲስ አበባ ፖሊስ መዛወር ነበረብኝ፣ ትንሽ ቆይተው የሚለቁኝ ስለመሰለኝ ወደ እዚያም የሚያጓጉዘን መኪና በመጥፋቱ፣ እኔ ታክሲ ኮንትራት ከፍዬ በራሴ ወጪ፣ በፖሊስ ታጅቤ ወደ እስር ቤት ሄድኩኝ። ለአራት ቀን ሶስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ታሰርኩ። በኋላ ሳጣራ አራት ቀን እዚያ የቆየሁት የቤንሻንጉል የህግ ሰዎች እስኪዝናኑ ነበር፡፡”
‹‹ከዚያስ?››
‹‹መኪና አቅርበው ወደ ወለጋ ጉዞ ጀመርን፡፡ ይህንን ገጠመኜን “ከግንፍሌ እስከ አሶሳ” በሚል ርዕስ በተከታታይ ጋዜጣው ላይ ፅፌዋለሁ። ነቀምቴ ዞን እስር ቤት አስገቡኝ፡፡ እስር ቤት ምን ያጋጥመኛል፣ ወደ 26 የሚጠጉ እስረኞች አሉ፤ ከእነዚህ ውስጥ 16 የመከላከያ ሠራዊት አባላት ናቸው፡፡ በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ሲዋጉ ቆይተው ወደ ትውልድ አገራቸው ከተመለሱ በኋላ ወደ መከላከያ ሠራዊት አንመለስም አሉ። ከያሉበት ቀበሌ ተለቅመው ለእስር ተዳረጉ። አራቱ ልጆች ደግሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪ የነበሩና ታፍነው ነቀምቴ የተወሰዱ ሲሆን ለሶስት ዓመታት ያህል በእግር ብረት ታስረው የቆዩ ናቸው። መፀዳጃ ቤት ሲሄዱም ከእግር ብረታቸው ጋር ነው፡፡ እነዚያ ልጆች ወላጆቻቸው የት እንዳሉ አያውቁም!”
“ወንጀላቸው ምንድነው?”
‹‹ኦ.ኤል.ኤፍ ይለጠፍባቸዋላ፡፡ ምን ችግር አለው፡፡ በጊዜው መፈረጅ ብቻ ለወንጀለኝነት በቂ እኮ ነው፡፡ የሁሉንም ታሪክ መሰብሰብ ነበረብኝ፡፡ የሁሉንም ውጣ ውረድ በልቤ መዘገብኩኝ፡፡ በቂ ጊዜ ነበረኝ፤ ለሶስት ሳምንት ስለታሰርኩ ያጋጠመኝን ኢ-ፍትሀዊ የሆነ ነገር ሁሉ ለመሰብሰብ እድል ነበረኝ፡፡
‹‹ወደ ኋላ ልመልስህ፡፡ ይህ ገጠመኜ ደግሞ አዲስ አበባ ፖሊስ የሆነ ነው፡፡ እዚያ አራት የወላይታ ልጆች ሁለት አመት አዲስ አበባ ፖሊስ ታስረዋል፡፡ ማነው ያሰራቸው? አይታወቅም፡፡ ልጆቹ ሁለት ዓመት ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ታስረዋል፡፡ ይህም የመረጃ ግብአት ሆኖኝ ከተፈታሁ በኋላ ጻፍኩት፡፡ አቶ ሙሉ ነጋ የሚባሉ ጠበቃ ነበሩ፡፡ እኚህ ሰው በዚህ ጋዜጣ መረጃ ላይ ተመስርተው የልጆቹን ፋይል አስወጥተው፣ ክስ መስርተው ተሟገቱላቸው፡፡ በመጨረሻም ልጆቹ በነፃ እንዲለቀቁ አደረጉ፡፡”
‹‹የነቀምቴዎቹስ?››
‹‹ወታደሮቹ ተለቀቁ፡፡ አድዋ ላይ ሆነው ደውለው ስላሉበት ሁኔታ አበሰሩኝ። የተማሪዎቹ ልጆች አባት መረጃው በጋዜጣው አማካኝነት እንደደረሳቸው ጉዳያቸውን ተከታተሉ፣ በኋላም ቢሮዬ ድረስ መጥተው አመሰገኑኝ፡፡ ከደስታቸው ብዛት እግሬ ላይ ሁሉ ወድቀው ነበር፡፡ ይሄን ይሄንን ስታይ ጋዜጠኝነትን ብወድ አይፈረድብኝም፡፡”
‹‹ቀጥሎስ?››
‹‹ወደ አሶሳ ተጓዝኩ፡፡ አሶሳ ፖሊስ ጣቢያ ገባሁ፡፡ ወረዳ ፍርድ ቤት ቀረብኩ፤ ለምን እንደዚያ እንደፃፍኩ ነው ዳኛው የሚጠይቁኝ። እኔ ደግሞ ስከራከር ክቡር ፍርድ ቤት፤ ይህ ስልጣን የእናንተ አይደለም። የዋስ መብት ይከበርልኝና፣ ስልጣን ባለው ፍርድ ቤት ነው፣ ጉዳዬን አቅርቤ መከራከር ያለብኝ፣ ስል ሙግት ገጠምኩኝ፡፡”
‹‹ሕግ ተምረሃል እንዴ?››
‹‹አንድ አነባለሁ፡፡ ሁለት በየጊዜው ስለምታሰር መብትና ግዴታዬን እንዳውቅ መልካም አጋጣሚን ፈጥሮልኛል፡፡ ሌላው የሕግ አዋቂ ጓደኞች አሉኝ፤ ሁሉም ያልገባኝን ስለምጠይቅ ያስረዱኛል፡፡ ስለዚህ መብትና ግዴታዬን አሳምሬ አውቃለሁ፡፡”
‹‹ዳኛው ምን ምላሽ ሰጡህ?››
‹‹ዳኛው በጣም ተናደዱ! ስማ በእኛ ክልል እናንተ እንደምታስቡት አይደለም፡፡ በእኛ ክልል የሰውም የአህያም መብት እኩል ነው አለኝ! ይህቺን ያዝኩና ሊጠይቀኝ ለመጣ አንድ ጓደኛዬ አለ፡፡ የተባልኩትን ነገርኩት፤ ይሄን አዲስ አበባ ለሚገኙ ባልደረቦቼ ደወለና ነገራቸው፡፡
እለታዊ አዲስ ላይ መሰለኝ ‹‹የቤኒሻንጉል ዳኛ የሰውም አህያንም መብት እኩል ነው ብለዋል ተብሎ ተዘገበላቸው ዜናው ቤንሻንጉል ደረሰ፡፡ በዚህ አበደ፡፡ ኳስ ጨዋታ አሶሳ ላይ ይካሄድ ነበር፡፡ ዳኛውን አገኙትና ደበደቡት። በርታዎች በፍቃዱ የታሰረው በእኛ ምክንያት ነው የሚል መረጃ አላቸው፤ በመጨረሻም ቀለብ ወደምታገኝበት ሂድ አለና አሶሳ ወህኒ ቤት ተላኩ፡፡ የታሰርኩት በርታዎች መካከል ነው፤ ቀደም ብሎም የሰራሁት ዜና ነበር፤ በቤኒሻንጉል ጉዳይ በዚህ መረጃ ላይ ከሱዳን ጠረፍ ተይዘው ለእስርና እንግልት የተዳረጉ 12 የሃይማኖት አባቶች የጉምዝ ብሄረሰብ ተወላጆች ነበሩበት። ወስደው ያሰሩኝ እነዚህ ሰዎች መካከል ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ማን እንደሆንኩ አወቁ፤ ለወደፊት ሥራዬ መረጃ መሰብሰብ ጀመርኩ፡፡ በዚህ ጥሩ ምቾት ተፈጠረልኝ፡፡ ከማን ጋር መግጠም እንደሌለብኝ፣ ማን ምን እንደሆነ የእስር ቤቱን ምንነት አብራሩልኝ፡፡
‹‹ለሶስት ሳምንት ያህል ቆየሁ፡፡ እዚህ ጋ እንድፈታ ከፍተኛ ጥረት ያደረጉ ተቋማትን ማንሳት አለብን፡፡ አንደኛው ክፍሌ ሙላት ነው፡፡ ሌሎቹ CPJ (Committee to Protect Journalists), IFJ (International Federation of Journalists and IPI (International Press Instituite) አባል ስለነበርኩ፣ ክፍሌ በዚህም በዚያም ተሯሩጦ ሰፊ ሽፋን ተሰጠው። በጥቂት ቀናት ውስጥ የኔ ጉዳይ የቪኦኤ ርዕሰ አንቀፅ ሆነ፡፡ የቪኦኤ ኤዲቶሪያል በ52 ቋንቋዎች ነው የሚተላለፈው፡፡ ሶስቱ የአገራችን ቋንቋዎች ናቸው፤ እስር ቤት እያለን እኔም አዳመጥኩት። እስረኛው በሙሉ በታላቅ ደስታ አጨበጨበ። እኔ ያለሁበት ክፍል ብቻ አይደለም፤ ጎረቤት እስረኛ ሁሉ በጭብጨባና በሆታ ድጋፉን ገለጠ።
“እስረኛው ሁሉ ‹‹ነገ ወጪ ነህ!›› አለ፤ ያሉት አልቀረም፤ በሚቀጥለው ቀን ፖሊስ መጣና፣ እቃህን አዘጋጅ አለኝ፡፡ ምቹ መኪና ወህኒ ቤቱ ድረስ መጣልኝ፣ ከፕሬዚዳንቱ ቢሮ ነው መኪናው የተላከልኝ፤ የፍትህ ቢሮ ኃላፊው ዘንድ ቀረብኩና አነጋገረኝ፣ የሰሩት ስራ ትልቅ ስህተት የነበረበት ነው፤ መንግስት ራሱ ነው ሕግን የጣሰው፡፡ ይህንንም ፕሬሶቹ ሰፊ ሽፋን ሰጥተውታል። ሲፒጄ ለሚያስፈልገኝ ወጪ ገንዘብ ልከው ስለነበር ሆቴሌን፣ የአውሮፕላን ቲኬት ሁሉ ተሸፍኖልኝ፣ ወደ አዲስ አበባ በሰላም መጣሁ፡፡ እዚህ ላይ አንድ ነገር ነገር ልጨምርልህ?”
‹‹ማለፊያ!››
‹‹በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ላይ የዘገብነውን ዜና  ከየት እንዳገኘነው ምንጩን ጠይቀውኝ ነበር ብዬሃለሁ?››
‹‹አዎን!››
‹‹እዚያ ሆኜ ሳጣራ ኃይላይ የሚባል ሰው ነው ደዋዩ፣ የኃይላይን ማንነት ሳጣራ፣ አሶሳ ውስጥ ኢህአዴግ ከመግባቱ ፊት ‹‹ግሪን ሆቴል›› ውስጥ አልጋ አንጣፊ የነበረ ሲሆን፤ ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ በኋላ ኃይላይ ከአልጋ አንጣፊነት በእምርታ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ የደህንነት ቢሮ ኃላፊ ሆኖ ተሾሟል። ይህ ሰው ነው የዜና ምንጭህን አምጣ እያለ ሲመረምረኝ የነበረው።”
‹‹አምጣ አታምጣ ይኖራል፡፡ በእንዲህ አይነት ወቅት ‹አልሞት ባይ ተጋዳይነትም› አለ፡፡ ምስጢርህን ለመደበቅ በምታደርገው ትንቅንቅ መደብደብ ደርሶብሃል? አየር ወለድ መሆንህስ ጠቀመህ?››
‹‹አንድ ጊዜ ድብደባ ደርሶብኛል፡፡ የመታኝ ሰው የማዕከላዊ ምርመራ ኃላፊ የነበረ መቶ አለቃ ታደሰ መሰረት የሚባል ሰው ነው፤ የማዕከላዊ ፈላጭ ቆራጭ ነበር፤ በኋላ ኢህአዴግ ከስልጣን ሲነሳ ብሔራዊ ባንክ አሮጌ ብር ሲቃጠል ክንውኑን የሚከታተል ሰራተኛ አድርገውታል አሉኝ፡፡ ይህ ሰው አንድ ጠዋት ፈለገኝ፡፡ ምንድነው አልኩት? በወቅቱ የኦነግ ሰዎች ናቸው ተብለው የሚሳደዱ ድምፃውያን ነበሩ፡፡ ዳዊት መኮንን፣ ዑመር ሱሌይማንና ሌሎቹም  ከየመንገዱ ከያሉበት እየተለቀሙ፣ አዳማ አንድ መጋዘን ውስጥ አጎሯቸው፡፡ ሰዎች ይህንን መረጃ እየተከታተሉ ይልኩልናል። እኛም በመረጃው መሰረት በምን አይነት መኪና እንደተጓዙ፣ የሰሌዳ ቁጥሩን ሁሉ በዝርዝር እየተቀበልን፣ እስካጎሯቸው መጋዘን ድረስ ዘገብን፡፡ ቤተሰቦቻቸው ይህ መረጃ አልነበራቸውም፡፡ በእኛ ጋዜጣ አማካኝነት ዘመድ ወዳጅ የት እንዳሉ መረጃ አገኘ። እኔ እህቴን ክፍለ ሀገር ሸኝቼ ወደ ቢሮ እየተመለስኩ ነበር፤ ድንገት ክብድ ብሎኝ ዞር ብዬ ሳይ የሆኑ ሰዎች እየተከተሉኝ ነው፤ ከፊትም እንዲሁ፤ ጸጥ ብዬ ጉዞዬን ቀጠልኩ፤ ቢሮ ገባሁና መረጃ ስጠይቅ በክትትል ላይ ነኝ፤ ከቢሮ ማዶም አንድ መኪና ቆማለች። እኛ ከቢሮ ሳንወጣ የእለት ሥራችንን ማከናወን ቀጠልን፡፡ ምሳ ሰዓት ደረሰ። አሁንም እንደተከበብን ነው፡፡ ለኢሰመጉ ደውለን ያለንበትን ሁኔታ አሳወቅን፡፡ ሻምበል ገረመው ይባላል፤ ይህንን ጉዳይ የሚከታተለው። ቀደም ብሎ የአዲስ አበባ ወንጀል መከላከል ኃላፊ ነበረ፤ ቢሮ መጣ። አብሮን ሆኖ ስንሰራ ቆይተን ለምሳ ወጣን። ሶስት መኪኖች ይከተሉኝ ጀመር፤ ብቻዬን ማግኘት ግባቸው እንደሆነ ተጠራጥረናል። አልተነጣጠልንም፡፡ አራት ኪሎና ሄደን ምሳ በላን፤ ሻይ ጠጣን፡፡ ክትትሉ እንደቀጠለ ነው፤ ማንን ነው የሚከታተሉት? ማንን እንደሚፈልጉ ለማወቅ ፈልገን ለሁለት ተከፍለን፣ ግማሾቻችን ወደ ፒያሳ፤ የተቀረነው ወደ ለገሀር ለመሄድ ወስነን ተበታተንን፡፡ ሰዎቹ የፒያሳውን ትተው ወደ ለገሀር ያቀናነውን መከታተል ያዙ፡፡ እኔን ነበር የሚከታተሉት፡፡ ስታዲየም ስንደርስ ኢሰመጉ ቢሮው ሣህለሥላሴ ህንፃ ላይ ነው። እዚያ ደርሰን ስንወርድም በ‹ወያኔ› ቶዮታ እየተከታተሉን ነው፡፡ መንገድ ስናቋርጥ ይከታተለን የነበረው መኪና ቆሞ አሳለፈን። ቢሮው በህንፃው ስምንተኛ ፎቅ ላይ ነው። ገባን፡፡ የኢሰመጉ ሰዎች እዚያው አሉ፤ እነ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም፣ እነ ዶ/ር ታዬ አሰፋ፣ (ነብሳቸውን ይማር) ጋሽ ተስፋዬ አገኙኝ፡፡ ሁኔታውን ነገርኳቸው፡፡ አሁን ለአንተ የማወጋህን ፕሮፌሰር መስፍን በህይወት እያሉ ባወጋህ ደስ ይለኝ ነበር፤ አልሆነም፡፡ የህይወቴ ታሪክ አካል ነውና ላንተ ላጫውትህ–”
‹‹ጥሩ!››
‹‹ከፕሮፌሰር መስፍን ጋር ስናወጋ ባንተ ጉዳይ ክንፈ ዘንድ ደውዬ ነበር አሉኝ፣ ክንፈ የደህንነት ከፍተኛው ኃላፊ ነበር። እሺ ምን ተባባላችሁ? አልኳቸው፤ ክትትል እየተደረገብህ እንደሆነም ያውቃል፤ አንድ ነገር ቃል እንድትገባ ነግሮኛል አሉኝ፤ ምንድነው? አልኳቸው፡፡ ጦማርን (ጋዜጣውን) ዳግመኛ ላለማተም ቃል ከገባህ፣ ክትትሉ ይቆይና ወደ ቤትህ መሄድ ትችላለህ ብሎኛል፡፡
‹‹ከእርሳቸው ጋር በስልክ ሌሊት ሌሊት እየተደዋወልን፣ አምስት ስድስት ሰዓት የምናወራበት ጊዜ አለ፡፡ በጣም እንቀራረባለን። የሚገርመው ሌሊት እንደማይተኙ አውቃለሁ፤ እኔም እንቅልፍ የለኝም! በጣም እንቀራረባለን፡፡
‹‹እርስዎ ምን አሉ?›› አልኳቸው፡፡ ‹‹እኔ ያልኩት ምን ያደርግልሀል፤ አንተ ምላሽህን ስጠኝ!›› አሉኝ ‹‹ከፈለጉ እዚሁ ይሰቅሉኛል እንጂ ጋዜጣውን አቆማለሁ ብዬ ቃል አልገባም፡፡ ይህንን ንገሩት አልኳቸው፤ ወደ ባልደረቦቻቸው ብቅ ብለው ‹‹እንግዲያውስ ከአስራ አንድ ሰዓት በኋላ እዚህ ቢሮ ውስጥ እንዳይቆይ!›› አሉና ወጥተው ሄዱ፡፡
‹‹ከዚያስ እንዴት ከዚያ ቢሮ ወጣህ?››
‹‹ሌላ የሚደንቅ ድራማ እዚያ ቢሮ ውስጥ ሰርተን፣ እኔ የማመልጥበት ሁኔታ ተመቻቸ። የዚያን እለት አዲስ አበባ ስታዲየም ውስጥ አንድ የተመልካችን ቀልብ የሳበ የእግር ኳስ ጨዋታ ይካሄድ ነበር፡፡ ይህ የኢሰመጉ ቢሮ የሚገኘው ስታዲየሙ ፊት ለፊት ነው፡፡ (ላሊበላ ሬስቶራንት) እዚህ ሕንፃ ላይ የሚኖሩ ሰዎች በዚህ ጊዜ ተሰብስበው ሕንፃው የመጨረሻ ወለል ላይ ወጥተው ጨዋታ ይመለከታሉ፡፡ ከሚከታተሉኝ የደህንነት ሰዎች ሶስቱ ሕንፃው የመጨረሻ ወለል ላይ ሕዝቡን ተቀላቅለው፣ ኳስ ጨዋታውን እየተመለከቱ ይከታተሉኛል። ምድርም እንዲሁ ሕንፃው ሁለት ሊፍት አለው፣ ይህንን ተዉንና በወዲያ በኩል ባለው ሊፍት የኢሰመጉ ዘበኛ አሮጌ ካፖርታቸውን አልብሰው፣ ከልለው እዚያ ድረስ ወሰዱኝ፡፡ ስወርድ ሊፍቱን አስጠግቶ ዶ/ር ታዬ መኪናውን አቁሞ ጠበቀኝ፡፡ ኮፈኑ ተከፈተልኝ፤ እጥፍጥፍ ብዬ ገባሁ፤ ይዞኝ እልም አለ፡፡
‹‹ገረመው የሚባል ጓደኛዬ ጋ ሄድኩ። ከዚያም ካዛንቺስ አብዬ ቤት መጣሁ፤ እንዲህ እየተሽሎከሎኩ እየኖርኩኝ ለጋዜጣው መፃፍ አላቆምኩም፤ ‹‹በገዛ አገሬ፣ ተሳደድኩ እንደ አውሬ›› በሚል ርዕስ ተስተናግዷል። ከማዕከላዊ በአስቸኳይ እንዲመጣ የሚል መልዕክት ለጋዜጣ ዝግጅት ክፍላችን ተደውሎ ተነገረ። ይህንን ነበር እኔ የምፈልገው፤ ጥሪው ሕጋዊ ከሆነ አክብሬ እገኛለሁ፡፡ ቤተሰቤም ሆነ ጓደኞቼ የት እንዳለሁ ያውቃሉ፤ ስለዚህ በጓደኞቼ ታጅቤ መቶ አለቃ ታደሰ መሠረት ዘንድ ቀረብኩ፡፡ እንዳየኝ ከወንበሩ ላይ ተነሳና መጥቶ ፊት ለፊቴ ቁጭ አለ፡፡ ‹ምን አባክ ነው የፃፍከው?› አለኝ፡፡
‹‹ምን አባቴ ነው የፃፍኩት?›› አልኩት
‹‹ኦሮሞዎች ታሰሩ ብለህ ነው የፃፍከው፤ ኦሮሞ አልታሰረም፤ የታሰረው ኦነግ ነው፤ የት እንደደረሱም አይታወቅም ብለሀል!›› አለኝ
‹‹አዎን ቤተሰቦቻቸው አያውቁም፤ ይህን  የምትለኝን አስተባብዬ ልፃፍ?›› አልኩት፡፡
ይህን ጊዜ ሽጉጡን አወጣና በሰደፉ አናቴን ኳ! አደረገና ፈነከተኝ፡፡
‹‹በዚህ ሽጉጥ ጭንቅላት አባትህን ባፈርስህ ምን አባትህ ትሆናለህ?!›› አለኝ
‹‹ምንም አባቴ አልሆንም እሞታለሁ!›› አልኩት፡፡ ከዚያ ምንም ማድረግ አልቻለም። ጨቅጭቆኝ ጨቅጭቆኝ፣ ጉዳዩም አየር ላይ ስለወጣ በመጨረሻ፣ ማስተባበያ ታመጣለህ አለኝ! ደሜን ጃኬቴን አውልቄ ግንባሬ ላይ ጠምጥሜ አቆምኩት፡፡ ከዚያ የዋስ መብቴ ተከብሮ ወደ ቤቴ ሄድኩኝ፡፡ የዚያን እለት መመታቴንና ማልቀሴን አስታውሳለሁ፡፡;
‹‹በርካታ ክሶች ነበሩብህ?››
‹‹አዎን! ሰባት ይሆናሉ፤ በጣም የሚያስቁም አለባቸው፡፡ አንደኛው ኢንጂነር ግዛው በሚባሉ ሰው ላይ የዘገብነው ነው፤ በወቅቱ የሙገር ሲሚንቶ ሥራ አስኪያጅ ነበሩ፡፡ እዚያ ስላለ ሙስና ዘገብን፡፡ በተላከልን ደብዳቤ ላይ ተመስርተን ነው ጋዜጣችን ላይ ያወጣነው። በዚህም የኢንዱስትሪውን ሰላም ለማናጋትና የኢንጂነሩን ስም ለማጥፋት ነው ብለው ከሰሱን። እኛ 10,000 ብር ዋስ ጠርተን ከተለቀቅን በኋላ፣ ጸረ-ሙስና ኮሚሽን ኢንጂነር ግዛውን በሙስና ወንጀል ከስሶ አሳሰራቸው፡፡ ልብ አድርግ፤ በሌላ ችሎት እርሳቸውን ወንጀለኛ አድርጎ ከስሶ፣ እኛን ደግሞ ስማቸውን አጥፍታችኋል በሚል ወንጅሎ፣ የሚያጥላላህ መንግስት ነው የነበረው፡፡ ጠበቃዬ አቶ ደርቤ ተመስገን ይህንን አያይዘው፣ ከእኛ ፋይል ጋር እንዲያያዝ ጠየቁ። አቃቤ ሕግ እንደማያዋጣው ሲያውቅ “ክሴን አንስቻለሁ” አለ፡፡
“ሁለተኛው፤ አንዱ ካህን ታቦት ሰርቀዋል ተብለው ክስ ይመሰረትባቸዋል። ኮልፌ ወረዳ ፍርድ ቤት ያጣራበትን የምርመራ ፋይል፣ የተፈረደባቸውን፣ ፍርድ ቤቱ የመያዣ ትዕዛዝ ያወጣበትን ማስረጃ አግኝተናል፤ ቄሱም ታስረው የዋስ መብታቸውም ሳይጠበቅ ከእስር ቤት አስወጧቸውና ወደ ሰሜን የአገራችን ክፍል ተላኩ፡፡ ዘመነ አባ ጳውሎስ ነበር፤ ሰውዬውም የትግራይ ተወላጅ ናቸው፡፡
“እኛም ይህንን መረጃ ከያዝን በኋላ ‹‹በታቦት ስርቆት የተጠረጠሩት ቄስ ተሰወሩ›› የሚል ዘገባ አወጣን፡፡ በዚህ ቤተ ክህነት ከሰሰችን፡፡ የዋስትና መብታችን ተከብሮ፣ ገንዘብ አስይዘን ክርክር ጀመርን፣ ጠበቃዬም ያሉትን ማስረጃ ሁሉ አያይዞ ለፍርድ ቤቱ ሲያቀርብ፣ አቃቤ ሕግ እንደማያዋጣው ሲያውቅ “ክሴን አንስቻለሁ” አለ፡፡
“ሌሎቹም ሶስቱ ጉዳዮች የአንባቢዎቻችን አስተያየት ናቸው፡፡ አንደኛው በወቅቱ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አመፅ አድርገው ነበር፡፡ ይህ አመፅ ተስፋፍቶ በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተቀጣጠለ፡፡ አንዱ ታዛቢ ወወክማ ላይ ቆሞ ያያል፡፡ ተማሪዎቹ ወደ አራት ኪሎ ይወጣሉ፣ ፖሊስ መንገድ ዘጋ፣ አንደኛው መተኮስ ጀመረ፡፡ ተማሪዎች መውደቅ ጀመሩ፣ የተቀሩት ድንጋይ በመወራወር ተቃውሟቸውን አጧጧፉ። ይህንን ያስተዋለ ሰው ፃፈልን፣ ‹አተያይ› የሚል አምድ ነበረን፡፡ ይህንን ትውልድ ማረቅና ለተሻለ እድገት መጠቀም ሲቻል፣ ይህ አይነቱ ጭካኔ ለምን? ሲል ይጠይቃል። አቃቤ ሕግ  ከዚህ ውስጥ አንዲት አንቀፅ አወጣና ከሰሰን፡፡ አራተኛው፤ ከመከላከያ ሠራዊት ጋር የተያያዘ ነው፤ ከአንድ ደርዘን በላይ የሚሆኑ የመከላከያ ሠራዊት አባላት በዘር ጉዳይ ተጠርጥረው ትጥቅ እንዲፈቱ ተደረገ፡፡ ይህ የሆነው ከምርጫ 97 በኋላ ነው፡፡ እኛ ይህንን መረጃ  ስናገኝ ዘገብነው፣ አቃቤ ሕግም ክስ መሠረተብን፡፡
“በወቅቱ ፋይል በዛ ተባለና ዳኝነቱን ከሶስት ዳኞች ወደ አንድ ዳኛ ተቀየረ። በአስረኛ ወንጀል ችሎት ክርክርና የማርኬቲንግ የአደንዛዥ ዕፅ ጉዳይ የሚያይ ችሎት አለ፡፡ የእኛን ጉዳይ ያይልን የነበረው ዳኛ አሰፋ አብርሃ ነበር፡፡ ከአምስቱ በሁለቱ ጥፋተኛ ተባልኩ፡፡ የቅጣት ማቅለያና ማክበጃ የሚባል ነገር አለ፤ ይህንን ጠበቃዬ አቀረበ፡፡ ለፍርድ በሚቀጥለው አርብ ተቀጠርን፡፡”
‹‹ከዚያስ?››
‹‹ከዚያማ ፍርድ ቤት በምመላለስ ጊዜ በተለይ በ1997 ዓ.ም ሰኔ እና ሌሎቹ ወራት ከተማው ውስጥ የነበረው እንቅስቃሴ አስፈሪ ነበር፡፡ አንዳንዴ አዲስ አበባ ዝግትግት ይላል፡፡ አንዴ ቀጠሮ ኖሮኝ በመሀል ግርግር ተነሳና ከተማው ታንክ በታንክ ሆነ፡፡ ባለቤቴም አብራኝ አለች፣ ቀስ ብለን እንጓዝ ተባብለን መኪናችንን ስናስነሳ፣ አንዲት ሴት እጇን እያራገበች ተማፀነችን፣ አሳፍሩኝ ነው የምትለው፡፡ ጫንናት፤ ወደ ሽሮ ሜዳ አካባቢ የምትኖር ሲሆን ስራዋ እዚሁ ፍርድ ቤት ውስጥ ነው፤ የልጆች እናት ነች፤ ስለ ልጆቿ ትጨነቃለች፡፡ የዚህ የእኔ ዳኛ ፋይል አቅራቢ ነች፡፡ እየሸኘናት ከባለቤቴ ጋር ስልክ ተለዋውጠዋል፡፡ በሰላም ቤቷ አደረስናት፤ ረቡዕ ቀን ስልክ ደውላ ‹ባለቤትሽ አርብ የሚቀርብ ከሆነ ብርድ ልብስ ይዞ ይምጣ፡፤ ዳኛው በአንድ ፋይል አንድ አመት ከስድስት ወር ፈርዶበታል፡፡” አለቻት፡፡ ሁለተኛው ፋይል ላይ፣ የመከላከያው ጉዳይ ሁለት አመት ያከናንበኛል፡፡ ይህንን እንዳወቅን ከባለቤቴ ጋር ተነጋገርኩኝ፡፡
“በፊት ደፋር ነበርኩ፤ ካገባሁና ከወለድኩ በኋላ በጣም ፈሪ ሆንኩኝ፡፡ ባለቤቴም “ፍርድ ቤት የምትቀርብ ከሆነ ፍርድህን አውቄያለሁ፤ ስለዚህ ከዚህ በኋላ እስር ቤት አንተን መጠየቅ አልችልም፤ ለእኔ ፊርማችንን ቀድደህልኝ ወደ እስር ቤት ትሄዳለህ፤ አልያም ትሰደዳለህ፤ ምርጫውን ለአንተ እተወዋለሁ” አለችኝ፡፡
“ጋዜጠኝነት ውስጥ ስገባ የህይወት ህጌን ልንገርህ፡፡ ምንም ዓይነት ውጣ ውረድ በህይወቴ ውስጥ ቢከሰት ራሴን አልገድልም፤ በምንም ተዓምር ከአገሬ ውጪ አልሰደድም የሚል ነበር፤ አሁን ህጌን ለመጣስ ተገደድኩኝ፡፡ መሰደድን መረጥኩ፡፡ ይህንን እምነቴን እንዳጠናክር ሌላም ችግር ተከስቷል፡፡ ይህ ደግሞ ነባሩን ህጌን ጥሼ መሰደዴን እንድመርጥ ያደርገኛል፡፡”
‹‹ምንድነው እሱ?››
‹‹አንድ ቀን አንድ ሰው ፀሐፊዬንም ሳያስፈቅድ ቢሮዬ ሰተት ብሎ ገባ፡፡ ይህ ሰው አሁን የት እንዳለ አላውቅም፤ በጊዜው በአገር ውስጥ ጉዳይ ደህንነት ትልቅ ቦታ ላይ የነበረ ሰው ነው። ስሙ አያስፈልግም፤ ጉዳዩ ነው የሚጠቅመን፡፡ በወዳጅነት ቀርቦኝ ድርጅታቸው (TPLF ማለት ነው) ለእኔ ትልቅ አክብሮት እንዳለው ነገረኝ። ጫካም የነበረ የድርጅቱ ታጋይ ነው፡፡ አንዳንድ ሥራዎችን አብረን እንድንሠራ ነው ሀሳቡ። ከቅንጅት ጋር በተያያዘ እነ ፋሲል፣ ሲሳይ፣ እስክንድር እስር ቤት ናቸው፡፡ እኔም ፍርዴን እንደተቀበልኩ እቀላቀላቸዋለሁ፤ በእንዲህ አይነት ሁኔታ ላይ እያለሁ ነው ይህ ሰው ለሥራ ፈልጎኝ የመጣው፤ እኔ ደግሞ ስላለብኝ ክስ አነሳሁበት፡፡ “እሱን ከአለቆቼ ጋር ተነጋግሬ እንወስናለን፤ ቀላል ነው” አለኝ። እሺ አልኩት፤ አሁን ወጥመዳቸው ውስጥ ገብቻለሁ፡፡ በጣም መጠንቀቅ አለብኝ፤ በሚቀጥለው ቀን “ክሶችህን አይተናቸዋል፤ አንተ ከእኛ ጋር ለመስራት ከተባበርክ ችግር የለውም” አለኝና ተስማማሁ፡፡
‹‹በሚቀጥለው ቀን ቀጠሮ ስለነበረኝ፣ ፍርድ ቤት ስሄድ ፋይሌ የለም፡፡ አቃቤ ሕግ፤ ‹ክቡር ፍርድ ቤት፤ የእርሱን ፋይል የበላይ አካል ወስዶታልና ሌላ ቀጠሮ ይሰጠኝ› አለ። ሌላ ቀጠሮ ተሰጠኝ፤ በቀጠሮው ስሄድ ፋይሉን መልሰውታል፤ ይሄንን ሰው ምንድነው? አልኩት፡፡ እርሱም ‹‹ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይፈረድብሃል፤ በአስቸኳይ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ትጠይቃለህ፣ ከዚያ በነጻ ትለቀቃለህ፤ በዚህ መልኩ የአንተ ጉዳይ ተዘጋጅቷል›› አለኝ፡፡
‹‹የምትሰራላቸው ምን እንደሆነ አውቀህ ነበር?››
‹‹እኔም ለሰውዬው ይህንን አንስቼበታለሁ፡፡ ዓላማው ምንድነው? ምንስ ነው የምሰራላችሁ? ስል ጠየቅኩት፡፡ ገንዘብ እንደሚሰጠኝ፣ ምቾት እንደሚፈጠርልኝ ቃል ገባ፡፡ በወቅቱ እዚህች ከተማችን ውስጥ በየቦታው ቦንብ ይፈነዳ ነበር። ይህንን የሚያደርገው ኦኤልኤፍ ነው። የዚህ ድርጅት ሴል የት እንዳለ፣ እነማን እንደሚያንቀሳቅሱት አንተ እንደምታውቅ፣ ድርጅታችንም መንግስትም ያውቃል፤ ስለዚህ ይህንን ግንኙነት እንድትፈጥርልን እንሻለን›› አለኝ፡፡
“ከጋዜጠኝነት ወደ ሰላይነት ልለወጥ ነው ማለት ነው፡፡ ይህ ለእኔ አደገኛ ነገር ነው፡፡ ኦ.ኤል.ኤፍ ለእኔ ፍቅር የለውም። ኢትዮጵያኒዝም አራማጅ ነው ተብዬ ስለምታሰብ፣ በፍቅር አይን አንተያይም፡፡ እነዚህ ሰዎች ደግሞ (TPLF) በተቃራኒው ነው የሚያስቡኝ፡፡ እንቢ ካልኩ የሚደርስብኝን አደጋ አውቀዋለሁ። እሺ አልኩ። ወታደር ቤት መኖሬ እዚህ ጋ ጠቅሞኛል፡፡ አንድ ቀን ውድቅት ላይ የመኝታዬ ቤት መስኮት ተደበደበ፡፡ ማነው? አልኩ፤ ይኸው የደህንነቱ ሰው ነው፤ “ውጣ” አለኝ፡፡
“ይኸው ሥራ አገናኝቶን ቢራ አብሮ መጠጣት፣ መከራከር ሁሉ ጀምረን ነበር። በድብቅ የሚያመሹበትን ቡና ቤት እስከማወቅ ደርሻለሁ፡፡ በዚያ ሌሊት ጠርቶኝ አንድ ፈቃዱ ባሪያው የምንለው፣ ጋዜጣ አከፋፋያችን አለ፤ የእርሱ ቤት የት እንደሆነ ጠየቀኝ፡፡ በእውነት አንዴ ፍቃዱ አባቱ ሞተው ሀዘን ልደርስ ሄጃለሁ፤ ከዚያ በቀር የማውቀው መረጃ የለኝም። እርሱንም አሳየኝ ብሎ መኪና ውስጥ ገብተን መሄድ ጀመርን፡፡ የእነ ፍቃዱ ለቅሶ የደረስኩበት ግቢ ጋ ስንደርስ፣ ሶስት ሴቶች ከዚያ ግቢ ወጥተው ወደ ጎዳና እየወጡ ነበር፤ ልክ ሴቶቹን ሲያይ ‹‹ከመኪናው ላይ ውረድ›› አለና ተከታተላቸው፡፡ ከሌሊቱ 8፡30 ሆኗል፤ ወደ ቤቴ ወደ ግንፍሌ በእግሬ መመለስ ጀመርኩ፡፡ ከአገር እንድወጣ ምክንያት የሆነኝ አንዱ ይህ አይነቱ አጋጣሚ ነው፡፡ እንዴት ነው ለምቾት፣ ለመኪና፣ ለቤት — ብዬ መዋቅሩን በማላውቀው፣ በማላምነው ጉዳይ ወንድሞቼን አሳልፌ የምሰጠው? ስለዚህ አገር ጥሎ መኮብለሉ የግድ ሆነ! ኬንያ እንደገባሁ ደወልኩለት፡፡
“በኬንያ በኩል ለመሰደድ የቪዛ ችግር ባይኖርም፣ ሌሎች ሁለት መሰናክሎች ነበሩብኝ። አንደኛው የገንዘብ ነው፡፡ ምንም ገንዘብ አልነበረኝም፡፡ ከምርጫ 97 በኋላ ማተሚያ ቤቶች 23 ጋዜጦችና መጽሔቶች ለሕትመት ይዘን ስንሄድ ተቀብሎ ማተሙን አቁመውታል፡፡ በህግ ባንታገድም ማተሚያ ቤቶች ሥራችንን ስለማይቀበሉ ከጨዋታ ውጪ ሆነናል፡፡ በዚህ ምክንያት በመስሪያ ቤቴ ላሉ ሠራተኞች የወራት ደሞዛቸውን ስለከፈልኩ አምስት ሳንቲም አልነበረኝም። ቀደም ብሎም ከፍተኛ የገንዘብ እጥረት ስለነበረብኝ ጋዜጣውን ለማሳተም በብድር መንቀሳቀስ ነበረብኝ። በዚህም ለልጆቹ ሁለት ሶስት ወር ደሞዝ መክፈል አልችልም ነበር፡፡ ማን ማስታወቂያ ይሰጠናል፤ ጊዜው የፈተና ወቅት ነበር፡፡ ሁለተኛ በአየር መንገድ በርሬስ የመሄዴ ጉዳይ፣ ኤርፖርቱ ላይ እታገዳለሁ ወይስ ስሜ ጥቁር መዝገብ ውስጥ ሰፍሮ እንደሆነ ማጣራቱ ሌላው ችግሬ ነው፡፡ አምላክ የሰው ድሀ አላደረገኝምና አንድ የአድዋ ልጅ ወዳጄ አለ፤ ደወልኩና አወያየሁት፡፡ አጣርቶ ሲነግረኝ ስሜ በጥቁር መዝገብ ላይ ሰፍሯል፡፡ ያለኝ አማራጭ በሞያሌ መኮብለል ብቻ ነበር፡፡
“አሁን ስሙን ብጠራው ቅር እንደማይሰኝ እገምታለሁ፤ ለወዳጄና መምህሬ ደረጄ ገብሬ ደወልኩለት፤ ጥሩ ሰዓት ደረስክ አለና አንድ ሺ ብር ሰጠኝ፡፡ ሌላ ወዳጄ የአንዱን ኤምባሲ ዲፕሎማት መኪና አመጣልኝና፣ እለቱን ወጥቼ ኢትዮጵያ ሞያሌ ገብቼ አደርኩ፡፡ ለክፉ ቀን ያስቀመጥኳት አንድ እህቴ አለች፤ ሞያሌ ነው የምትኖረው፤ ደወልኩላት፡፡ እንደመታደል አገኘኋት፤ ተቀብላኝ አሳደረችኝና በበነጋታው መንገድ መርታ ሸኘችኝ፡፡ በሚቀጥለው ቀን ስድስት ሰዓት ተጉዤ ኬንያ ገባሁ፡፡ ናይሮቢን እንደረገጥኩ መጀመሪያ የደወልኩለት ለዚህ ለወያኔ እንድሰራ ላግባባኝ ሰው ነበር፡፡ እየተደነቀ ተሰነባበትን፡፡ እዚህ ጋ ልብ በል፤ በርካታ አማራጮች ያለኝ ሰው ነበርኩ፤ አገሬ እያለሁ ያንን አማራጭ ልጠቀም ብል በሰው ሕይወትና ደህንነት ላይ ችግር የሚፈጥር ሆነ፡፡ ስለዚህ ሞራሌን ጠብቄ ስደትን ሀ ብዬ ጀመርኩ፡፡
“ኬንያ አንድ ጓደኛዬ፣ ስለሺ ወልደየስን ታውቀዋለህ? እሱ ተቀበለኝ፡፡ ኪሴ 100 ዶላር ነበር፤ ስለዚህ እነዚያ የጋዜጠኛ መብት ተሟጋች ተቋማትን የማግኘት ቀጣዩን ሂደት መከታተል ጀመርኩ፡፡ ሲፒጄ ለቤት ኪራይና የመሳሰሉ ወጪዎች እንድሸፍን 1,500 ዶላር ይልክልኛል። በዚህ ዘና ብዬ እየኖርኩ፣ ቀጣይ ህይወቴ ላይ መሥራት ጀመርኩ፡፡ ኬንያ ውስጥ ስደተኞችን ተቀብሎ የሚያስተናግደው (ዩኤንኤችሲአር) ጣጣው ቀላል አይደለም፤ ለስደተኛ የሚሰጡት ወረቀት አለ፡፡ እርሱን ተቀብዬ ለሲፒጄ ላኩት። እነሱ በቀጥታ ጄኔቭ ከሚገኘው ተቋም ጋር በመገናኘት ነገሩን መልክ አስያዙት፡፡ የአሜሪካ ኤምባሲ በእኔ ላይ የሰበሰቧቸው በርካታ መረጃዎች ነበሯቸው፤ ስለዚህም ያለ ችግር ቪዛ አገኘሁ፤ ይህንን ለማከናወን 6 ወራት ፈጅቶብኛል፡፡
‹‹ቤተሰብህስ? ማስፈራሪያና ወከባ አልደረሰባቸውም?››
‹‹ጦማር ከህትመት ብትወጣም ቢሮአችን የተደራጀ ስለነበር ወደ 12 ኮምፒውተር ነበረን፣ የትርጉምና የጽህፈት ሥራ፣ የኢንተርኔት አገልግሎት እየሰጠን ገቢ መፍጠር ጀምረን ነበር፡፡ በዚህ ባለቤቴ፣ እኔ አንድ ቦታ ደርሼ እንዳረፍኩ ልጠራት ተስማምተን ነበር የተለያየነው፡፡ እንዳሰብነው ትተዳደርበት ጀመር፤ አሳዛኙ አጋጣሚ አንድ ቀን ማታ ቢሮው ተሰበረ፤ ኮምፒውተሮቹ፣ ማተሚያ፣ ጽህፈት ሥራ የምናካሂድባቸው ቁሳቁሶች፣ የተለያዩ ሰነዶች፣ ቃለ ምልልስ ያደረግኩባቸው ካሴቶች— አንድም አላስቀሩም ዘረፉት፤ በዚህ ባለቤቴ ተረበሸች፡፡ ወደ ቤታችን ከመዝመታቸው በፊት ቶሎ ብላ የቤቱን ቁሳቁስ እንድትሸጥ፣ ያቺ ባለውለታችን የሆነችውም መኪና ተሸጣ ከልጄ ጋር ወደ ናይሮቢ እንድትሰደድ አደረግኩ። ቤተሰብን ሲያካትት የጉዞ ፕሮሰሱ የራሱ ደንብ ስለነበረው፣ ያንን አሟልተን እነሱ ከመጡ ከአራት ወራት በኋላ፣ በአጠቃላይ ኬንያ 10 ወር ቆይቼ፣ ወደ አሜሪካን ሂዩስተን ተሻገርኩ፡፡”
‹‹እንደነገርከኝ በአጭር ጊዜ ውስጥ ነው ወደ አሜሪካ መሻገር የቻልከው፤እንደ ብዙዎቹ ስደተኞች ለረዥም ዓመታት በስደተኛ ካምፕ ውስጥ አልተሰቃየህም፤ ግን ደግሞ የመደበት ስሜት ውስጥ ገብተህ እንደነበር ትገልጻለህ፤ መነሻው ምንድን ነው?››
‹‹ማንም ሰው ወዶ ሳይሆን በግዱ ከአገሩ ሲወጣ፤ ወደደም ጠላ መደበሩ የማይቀር ነው፤ ቁጭቱ፣ ንዴቱ፣ ወይኔ ማለቱ አይቀርም፤ ድብርቱ ከባድ ነው፡፡ አሁን ሌላ መጽሐፍ ላይ ይህንኑ ድባቴን ተጠብቤበታለሁ። ኬንያ እያለሁ በአካሌ ናይሮቢ ብተኛም፣ ነብሴ እዚህ ነበረች፤ ተሹለክልኬ አዲስ አበባ ገብቼ በውድቅት ሌሊት ልጄንና ባለቤቴን አግኝቼ፣ ስሜ፣ እንደገና ተሹለክልኬ ስመጣ ነው የሚታየኝ። አንድ ግጥሜ እንደውም ይህንን ሁኔታ ነው የሚገልጸው፤ እዚያ እያለሁ በሽታን የመከላከል አቅሜ ተዳክሞ ታምሜ ነበር፡፡
‹‹ምን አይነት ህመም?››
‹‹አልማዝ ባለ ጭራ የሚባል ሕመም የሰራ አካላቴን ወረረው፤ ስደት እንዲህ አይነት ክፉ ህመም ሲታከልበት፣ ድብርት ሲያንሰው ነው። በወቅቱ እንዲህ አይነት ህመም የሚይዛቸው ሰዎች 90 በመቶ ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ሆነው ይገኛሉ፡፡ እኔም ስመረመር ኬንያዊው ዶክተር ኤችአይቪ እንዳለብኝ ነገረኝ፡፡ ከባለቤቴ ጋር ስንጋባ ምርመራ የሚባል ነገር አልነበረም፣ ተፋቀርን መዋደዱን ቀጠልንበት፡፡ ልጄ ፌናን ተወለደች፣ እኔ ተሰደድኩ፣ ስለዚህ ፖሰቲቭ መሆኔን መቀበል አልቻልኩም፡፡ ከሁለት አንዳችን ተሳስተን ይሆን? በድጋሚ ተመረመርኩ፤ አሁንም የሚያሳየው ግን ፖዘቲቭ ነው፡፡ ክፋቱ ደሞ ናሙና ተወስዶ ውጤት የሚነገረው በወር ነው፤  ይህ ማለት ደግሞ የጭንቅ ጊዜ ነው፡፡ ከበሽታው ስለ መጠንቀቅም ሆነ ችግሩ ከተከሰተ በኋላ ራስን እንዴት መንከባከብ እንዳለብን፣ እውቀቱ ስለነበረኝ፣ ጋዜጣዬም ላይ ስፅፍ ስለነበር፣ ይህ መረጃ ጥሩ ፋታ ሰጥቶኛል። ለቁስሌ ማድረቂያ የተሰጠኝን ቅባት ተቀብቼ፣ ራሴን መንከባከብ ጀመርኩ፡፡ ከአንድ ወር በኋላ የላብራቶሪ ውጤት መጣና ነፃ ነህ ተባልኩ። ይህንን ውጤት ይዤ ዶክተሩ ዘንድ ቀረብኩ። ዶክተሩም ውጤቱን አልቀበልም፤ አለ፡፡ “ኬንያ ውስጥ ፖዘቲቭ ሆነህ ጤናማ እንደሆንክ አይነት መሸዋወድ ስላለ፣ እንደገና መመርመር አለብህ” አለኝ፤ እና ምን ይሻላል? አንድ የሕክምና ስልት አለ። ‹አድቫንስድ› የሆነ ምርመራ ያስፈልግሃል ተባልኩ፡፡ ምን አማራጭ አለኝ፤ በሀሳቡ ተስማምቼ ዳግም ምርመራ ተደረገልኝ፤ አሁንም ውጤቱ እስከሚመጣ መጠበቅ ነበረብኝ። ስለ በሽታው ሳስብ በተለይ ከሁለታችን አብራክ የተከፈለችው ልጄ በጣም ታሳዝነኝ ነበር። ያም ሆነ ይህ እንደማይደርስ የለም፤ ያ የጭንቅ ጊዜ አልፎ የምርመራ ውጤቴ መጣ። ነርሷ ዘንድ ቀርቤ ልታረጋጋኝ ሞከረች፤ ስለ ኤችአይቪ ምን ያህል እንደማውቅም ጠየቀችኝ፡፡ የማውቀውን ሁሉ በደንብ ነገርኳት፤ ደስ ብሏት ሃኪሙን እንዳገኘው አመቻቸችልኝ፡፡
ዶክተሩም ‹‹የመጨረሻውን ከፍተኛ ምርመራ አድርገንልሀል፣ እድለኛ ነህ፤ ከኤች አይ ቪ ነፃ ነህ፡፡ ቀሪ ህይወትህን ግን በጥንቃቄ መምራት አለብህ” በማለት ከማሳሰቢያ ጋር ሸኘኝ፡፡ በጣም ደስ አለኝ፤ ከዚያ በኋላ ተረጋጋሁ፡፡
‹‹ሂዩስተንንስ እንዴት አገኘሃት?››
‹‹አንድ ሆስፒታል ውስጥ የፅዳት ሠራተኛ ሆኜ ነው ሥራ የጀመርኩት፡፡ በዚህ ወቅት ያለቀስኩበትም ጊዜ ነበር፡፡ ስፀልይም እግዚአብሔር ሆይ፤ የትላንት ማንነቴን እንድረሳና የዛሬውን ማንነቴን እንድቀበል ጽናቱን ስጠኝ እል ነበር፡፡ እንደገና ቤተሰብን ማቋቋም  ነበረብኝ፡፡ ተስፋዬ ገብረአብ አንድ ፅሁፉ ላይ የሰነዘራት ሀሳብ ለእኔ እንደ መሪ ቃል ጠቅማኛለች፡፡ ተስፋዬ ምን ይላል? ‹ደቡብ አፍሪቃ ተሰድጄ አንድም ቀን ‹ሜድ ኢን ደቡብ አፍሪቃ› የሆነ ህልም አይቼ አላውቅም፣ የምተኛው ደቡብ አፍሪቃ ቢሆንም ሕልሞቼ በሙሉ ከኢትዮጵያ ነበሩ› ይላል፡፡ የእኔም እንደዚያ ነው፡፡ ከኬንያም ሆነ ከአሜሪካ ጋር የተያያዙ አልነበሩም፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ናቸው፡፡ለ16 ዓመታት በአሜሪካ ኖሬያለሁ፤ አንድም ቀን ግን በአሜሪካ የተሰራ ህልም አይቼ አላውቅም።”
‹‹ከዚያ በኋላ ታክሲ መንዳት ጀመርክ አይደል?››
‹‹አዎ፤ሥራዬን ወደ ታክሲ መንዳት ስቀይር እንደ ልቤ የምፅፍ መስሎኝ ነበር፡፡ ይሄ የሥራ መስክ የራሱ የሆነ ችግር አለበት። ተሳፋሪ የአነጋገር ለዛህን ይይዝና ‹ከየት ነህ?› ይልሀል፤ በጣም ያስከፋኛል፡፡ ይሁን እንጂ ለምጄው ሁለተኛ ልጄን ወልጄ፣ ለ16 ዓመታት አሜሪካንን ኖርኩባት፡፡
‹‹መሽረፊት› የምትለው የአጭር ልብወለድ ስብስብህን ለመፃፍ ብዙ ጊዜ ወስዶብሃል?››
ከጽዳት ሠራተኝነቱም፣ ከታክሲ ሹፌርነቱም የተሻለ ጥሩ ኪነ ጥበባዊ ሥራዬን አሰብኩ የምለው አንድ በርገር ቤት ማታ ማታ ጥበቃ በሰራሁበት ጊዜ ነው፡፡ በርገር ቤቱ ውስጥ ለስድስት ወራት ያህል ነው፡፡ የሰራሁት በዚያን ጊዜ ወደ 24 ርዕስ ማለፊያ ያልኳቸውን ግጥሞች ፃፍኩ፡፡ ይህ ነው እርባና ያለው ተግባር ከወንኩ የምለው በተረፈ የህይወት ልምዴ፣ ፈተናው ውጣ ውረዱም ቢኖር፣ መጻፍ የሚገባኝን ያህል አልፃፍኩም፡፡
‹‹ሂዩስተን እያለህ ቤትህ ላይ ቃጠሎ ደርሶ ነበር?››
‹‹በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ነው” የሆነብኝ። ኬንያ የተሻለ ማስታወሻ እይዝ ነበር፡፡ እሷን ጨምሮ፣ እዚያም አሜሪካ የያዝኳቸው ሁሉ ከቤቱ ንብረት ጋር ጋየ፤ አንድ ኮምፒውተር ነበረችኝ እሷም ጋየች፤ ደግነቱ ባለሙያ ሲያያት ‹ሚሞሪ› አልወደመም፤ ተአምር ነው ለዚያ አጭር ልብወለድ ጥሪት ኖረኝ፡፡ በአጠቃላይ አሜሪካን እየኖሩ የሚጽፉ ካሉ አደንቃለሁ። የስነ ፅሁፍ ዝንባሌ ላለው ሁሉ ግን የአሜሪካንን ኑሮ አልመኝለትም፡፡
‹‹በፈቃዱ አሁን በእድሜ ጎልምሰሀል፣ በልምድም በስለሀል፤ ያለፈውን ዘመን የፕሬስ ስራዎች እንዴት ታያቸዋለህ?››
‹‹ይህንን ብዙ ጊዜ ብዬዋለሁ፤ አለማወቅን ከጥፋት አልቆጥረውም፤ ብዙዎቹ ተሰሩ የምንላቸው ስህተቶቻችንን ሳስተውል ካለማወቅ የመጡ ናቸው፡፡ ኢህአዴግም ሰንዳፋ ሲደርስ እኮ ነው ከአልባንያ ኮሚኒዝም ወደ ነፃ ገበያና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመግባት የሞከረው፡፡ እኛም በሶሻሊዝም አስተሳሰብ ነው ከዚህ አካሄድ ጋር የተገናኘነው፡፡ ስለዚህ እኛም ሕዝብም፣ መንግስትም ተለማማጆች ነበርን፡፡ ነፃ ገበያ፣ ዲሞክራሲ፣ መድብለ ፓርቲ ስርዓት መለማመጃ ጊዜ ሲሆን፤ ያንን ይመራን የነበረውም ስርዓት አልተረዳልንም፤ በዚህ ምክንያት ነው ቀደም ብሎ የነበረው መደናቆር የተፈጠረው፡፡
የእኔን የኋላ ታሪክ ስንመረምር፣ እኔ የቀድሞ ሠራዊት አባል ነበርኩ፡፡ የፈለጉትን ቢሉ የእኔ ህሊና እነሱን አይቀበልም፤ ስለዚህ ‹ኦፒኒየን› ላይ ሚዛናዊ መሆን የምችልበት ጊዜ አልነበረም፡፡ ከእነሱም ነውረኛውን አስታውሳለሁ፡፡ የፍትህ ሚኒስቴር ማህበረ ሰለሞን የሚባል ነበር፡፡ 18 ልጆች አንድ ቤት ማረሚያ ቤት ታስረን ነበር። ሚኒስትሩ ምን ያህል ‹እነ መቶ አለቃ በፍቃዱ ሞረዳ፣ ትላንት በጠመንጃ ዛሬ ደግሞ በብዕር እየወጉን ነው› ይላል፡፡ አዎን አልወዳቸውም። የኔ አቋም ያ ነበር፡፡ ዛሬ ግን ቢሆን ሚዛናዊ ለመሆን እጥር ነበር፤ እንደዚያም ሆኖ ጦማር በጊዜው ሚዛናዊ ጋዜጣ ነበር ብዬ አስባለሁ አሁን የቀድሞ የኢህአዴግ ባለሥልጣን ብታገኝ ስራዬ ብለህ ብትጠይቃቸው ይህንን ምስክርነት የሚሰጡ ይመስለኛል፡፡ አዎን በምርጫ ወቅት ኢህአዴግን፣ ቅንጅትን እገሌን አንለቅም፡፡ እንጨፈጭፋቸው ነበር። በዚህም ገበያውን ሰብረን ኮፒያችን አድጎ መውጣት አልቻልንም፤ ጥሩ ደረጃ ላይ አልነበርንም፣ ይሁን እንጂ ጊዜው የፈቀደልን ሰርተን የራሳችንን አንባቢን ፈጥረናል ብዬ አስባለሁ፡፡
‹‹ከ16 ዓመታት ቆይታ በኋላ አገር ቤት መጣህ! የህትመት ውጤቶችን የማየትና የመመዘን እድል ነበረህ?››
‹‹በድህረ ገፅ አያቸው ነበር፤ በዚህም ያሉበትን የመመዘን እድል እዚያው አሜሪካ እያለሁ ነበረኝ፡፡ እውነቱን ለመናገር በፊትም የማውቃቸው ሚዛናዊ ሆነው ዘልቀው ዛሬ ላይ ከደረሱት ውጪ አዳዲሶቹን ሳያቸው ትላንት ከነበረው የተለየ ነገር አላየሁባቸውም። መሻሻልም አላየሁባቸውም፡፡ ዓለምአቀፉን ሁኔታ ከፕሬስ ሚዲያ አንፃር ስታየው፣ እኛ አገር ብቻ ሳይሆን በመላው ዓለም ፕሬስ ፈተና ላይ ነው፡፡ ‹ዲጂታል› ሚዲያው በጣም ተደራሽ መሆኑ ፈተናውን አባብሶታል። ያንን ፈተና አልፎ ገበያው ላይ ተፈላጊ ለመሆን ‹ሴንሴሽናላይዝ› የማድረግ ነገር አሁንም አልጠፋም፡፡ ብዙዎቹ ላይ መሻሻል አላየሁባቸውም፡፡
‹‹መሻሻሉ እንዲመጣ ምን ያድርጉ?››
‹‹የሕትመቱ ብቻ ሳይሆን የኤሌክትሮኒክሱን ካየሁ ለእኔ እንደ ትልቅ መፍትሄ የሚታየኝ፣ በሙያተኛው እጅ ገብቶ ባለሙያው አገርን፣ ህዝብን፣ መንግስትን ማዕከል አድርጎ መስራት አለበት፡፡ አሁን ስታየው በፖለቲከኞች፣ በአክቲቪስቶች እጅ ነው ያለው፡፡ አንድም ቀን በጋዜጠኝነት ትምህርት ቤት ያላለፉ፣ ስለ ‹‹Universal code of conduct›› ብትጠይቃቸው አንድ ቃል ሊነግሩህ የማይችሉ ሰዎች፣ መገናኛ ብዙኃንን ሲመሩ ታያለህ፡፡ ይህ ችግር ታርሞ በባለሙያው መሠራቱን ለአገሬ እመኛለሁ››
‹‹አንተስ ከዚህ በኋላ ምን ታስባለህ?››
‹‹እኔ ወደ ሙያዬ እመለሳለሁ ብዬ አስባለሁ። የህትመቱን ብቻ ሳይሆን ቴሌቪዥኑን፣ ሬዲዮኑን ሁሉ አካቶ የሚይዝ ሚዲያ ይኖረኛል። ለዚህም እዚህ ከቆዩና የገንዘብ አቅም ከፈጠሩ ጓደኞቼ ጋር ተመካክሬ፣ አንዳንድ ዝግጅቶችን እያደረግሁ ነው፡፡”
‹‹የመሰናበቻ ጥያቄዬ፤ ድሮ ያስሩህ ያሳድዱህ የነበሩ የጊዜው ባለሥልጣናት፣ ዛሬ በቦታቸው የሉም፤ ምናልባትም እንዳንተ ተሰደዋል፤ ባለፉት ዓመታት አንዳቸውን አግኝተህ የተወቃቀስክበት አጋጣሚ አልተፈጠረም?”
‹‹ተስፋዬ ገብረአብ የፕሬስ ኃላፊ ሳለ፣ እኔ ‹በሪሳ› በሚባለው የኦሮምኛ ጋዜጣ፣ በ180 ብር ለመቀጠር ሞክሬ አልተቀበሉኝም፡፡ በኋላ ተስፋዬ የእፎይታ አዘጋጅ ሆኖ፣ እኔ ጦማር እያለሁ፣ እንተቻች እንነታረክ ነበር፤ በመጨረሻ ሁለታችንም ከአገር ተሰደን ተገናኘን፡፡ ያለፈውን ትተን ወዳጅ ሆንን፤ ፖለቲካዊ አመለካከቱ የራሱ ነው፡፡”
Filed in: Amharic