>

ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ፈተና ውስጥ ነን - እንደሀገር እና እንደህዝብ ተፈትነን እንጂ ወድቀን አናውቅም!!!  (ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ) 

ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ፈተና ውስጥ ነን – እንደሀገር እና እንደህዝብ ተፈትነን እንጂ ወድቀን አናውቅም!!!

 ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ – 

 

‹‹ኢትዮጵያን የመበታተኛው ሰአት አሁን ነው›› – ግብጽና ሱዳን፡፡
 
ክፍል አንድ – መነሻ
.
ሀገራችን የአፍሪካ የውሃ ማማ ‹‹the water tower of Africa›› ይሏታል፡፡ ብዙ ሀይቆች አሏት፤ ብዙ ወንዞች አሏት፡፡ ምድር የተሸከመችው ትልቁ ወንዝ አባይ አላት፡፡ ብዙዎቹ የውሀ ሀብታምነታችንን ሲነግሩን እኛም ስንዘፍንለት፣ ለልጆቻችን በየተረቱና በየጂኦግራፊ ትምህርቱ ስናስተምረው ቆይተናል፤ ኖረናል፡፡
 ‹‹አባይ አባይ፣ 
 የሀገር ሀብት የሀገር ሰላይ››
.
 ‹‹አባይ ጉደል ብለው፣ አለኝ በትህሳስ፤
 የማን ልብ ይችላል፣ እስከዚያው ድረስ፡፡››
.
ስለተፈጥሮ ሀብታችን ስንዘምርና ስንተርት አድገን፣ ሀገራችንን የድርቅና ረሃብ ምሳሌ ሆና መዝገበ ቃላት ውስጥ አግኝተናታል፡፡ ለወንዞቻችንና ለሀይቆቻችን እየዘፈንን ውሃ ሲጠማን፣ ስንራብ ኖረናል፡፡ አባይን የሚያክል 64% ኮረንቲ የማመንጨት እምቅ ሀብት ይዘን፣ የእናቶቻችንና የእህቶቻችን አይን በጭስ ይጠፋል፡፡ እንኳን ትልልቅና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎችን የእህል ወፍጮና ዳቦ ቤት በኮረንቲ እጥረት በፈረቃ ይሰራሉ፡፡
 
48 ሚሊየን ህዝብ የሚኖርበትን፣ አርባ ከመቶ የሆነውን የሀገራችን ምድር  የሚሸፍን፣ አባይን ይዘን ለዓመት ቀለባችን የምዕራባውያን እጅ እንመለከታለን፡፡ 40 ሚሊየን ሆነን፣ 50 ሚሊየን ሆነን፣ 60 እና 70 ሚሊየን ሆነን እንዲህ ኖረናል፡፡ ዛሬ መቶ እና መቶ ሃያ ሚሊየን ሆነን እንዲህ ልንኖር አንችልም፡፡ 
 
ለውሀ ሀብታችን በተለይ ለአባይ እየዘፈንን ተጠምተንና ተርበን የኖርነው፣ መስኖ ያላለማንበት፣ ኮረንቲ ያላመነጨንበት፣ ያላደግነው ስንፍና እና ድህነት አስሮን ነው፡፡ ሁለቱንም ግን መርጠናቸው አይደለም፡፡ ኢትዮጵያውያን ሰነፎች ብንሆን ጣልያንን እጅ ነስተን እንቀበለው ነበር፡፡ የአምስት አመት የአርበኝነት ተጋድሏችን ስንፍና ሲያልፍ እንደማይነካን ያረጋግጣል፡፡ ‹‹ነፃነቱን ለማስጠበቅ አምስት ዓመት ያለበቂ ስንቅና ትጥቅ በዱር ገደሉ የተዋደቀ፣ ረሃብና ጥማት ያላንበረከከው ህዝብ እንዴት በስንፍና ለድህነት ተንበረከከ?›› የሚለው ተገቢ ጥያቄ ነው፡፡
 
ለዚህ ጥያቄ መልስ የኢትዮጵያና የግብፅ የግንኙነት ታሪክ ትልቅ ድርሻ አበርክቷ፡፡ ግብፆች ክርስትና ከመስፋፋቱና ለኢትዮጵያ ጳጳስ ከመመደባቸው በፊት ለኢትዮጵያ ነገስታት ስጦታ በመስጠት ወዳጅነትን በመመስረት ስለአባይ እጅ ይነሱን፣ ያባብሉን ነበር፡፡ ጳጳስ መመደብ ከጀመሩም በኋላ፣ የወሩን ቀናት ሙሉ በሙሉ በሚባል መጠን የማይሰራባቸው ሰንበቶች በማድረግ፣ ገበሬው መሬት ሳይጭር – ቅጠል ሳይበጥስ እንዲቀመጥ በእምነት በማሰር ስንፍና የኑሮው አካል፣ ድህነትን ቤተኛው አድርገውለታል፡፡ አቅም ያፈረጠሙ ሲመስላቸው በጦርነትም ሞክረዋል፡፡ በተለይ አስዋንን ገድበው፣ የስዊዝ ካናልን ከተቆጣጠሩ በኋላ፣ በመልክአ ምድራዊ አቀማመጣቸው ላይ የስዊዝ ካናል ባለቤትነታቸው ተጨምሮ ባስገኘላቸው የምእራባውያን የማይለወጥ ወዳጅነት በመጠቀም ኢትዮጵያን በድህነት አማቅቀው እስረኛ አድርገው ቆይተዋል፡፡ 
ከንጉስ ኃይለሥላሴ ዘመን ጀምሮ አባይን የመገደብና ለኮረንቲ ኃይል የመጠቀም ሀሳብ ሲነሳ በሀገራችን የውስጥ ጉዳይ በመግባት ተቃዋሚ እያደራጀች፣ በገንዘብ እየደገፈች፣ መሳሪያ እያስታጠቀች እያበጣበጠችን ዛሬ ድረስ አለች፡፡
 
ምዕራባውያን ግብፅን እስከፍላጎቷ ተሸክመዋት ኖረዋል፡፡ ከእንግዲህ ግን ግብፅን እንጂ ኢትዮጵያ ላይ ያላትን ፍላጎት አዝለው ሊኖሩ አይችሉም፡፡ ለእኛ የታላቁ ህዳሴ ግድብ የኮረንቲ ማመንጫ ግድብ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ እውን ሉአላዊነቷን አለም ያወቀላት ነፃ ሀገር መሆኗን ማረጋገጫ ነው፡፡ ለእኛ ኢትዮጵያውያን ህዳሴ ግድብን ውሃ አትሞሉም፤ ከአባይ ኮረንቲ ማመንጨት አትችሉም ማለት፤ ባንዲራችሁን በአደባባያችሁ ሰቅላችሁ ማውለብለው አትችሉም›› ከሚለው የቅኝ ገዥዋ የኢጣልያ የድፍረት ሙከራ ምንም ልዩነት የለውም፡፡ ጣልያን ያወረደው ሰንደቅ አላማችን ተመልሶ እስኪውለበለብ አባቶቻችን አምስት አመት ተጋድለዋል፡፡ የህዳሴ ግድብን ሞልተን፣ ኮረንቲ አመንጭተን ሉአላዊነታችንን ለማረጋገጥ እኛ ብቻ አይደለንም የልጅ ልጆቻችን ለዘለዓለም ይጋደላሉ፡፡ ‹‹ለነፃነታችን ጣልያንን እንኳን አሸንፈናል›› እንዳልነው ‹‹ከድህነት ለመውጣት አባይንም ገድበናል›› ብለን አፋችንን ሞልተን እስከምንናገርበት እስከዚያች የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የብስራት ቀን ድረስ ማንኛውንም አይነት መስዋእትነት እንከፍላለን፡፡
 
የህዳሴው ግድብ የእድገታችን ብቻ ሳይሆን የሰላማችንም ዋስትና ነው፡፡ የዓለም ታሪክ የሚያስተምረን ጥንካሬና እድገት የሰላም ዋስትና እንደሆነ ነው፡፡ በበሬ እያረሰ፣ ስንዴ እየተመፀወተ፣ . . . በአጠቃላይ በድህነት ተጠፍንጎ አለም ያከበረው ሀገር የለም፡፡ በዘመነ አክሱምና አዶሊስ በአለም ላይ የነበረን ተጽእኖ የጠፋው ከታላቅነታችን ጋር ነው፡፡ ደህነት ያስንቃል ያስደፍራል፡፡ በጥንካሬያችን ዘመን ወርቅ ተሸክመው እጅ ትነሳን ነበር – ግብፅ፡፡ ዛሬ ጠመንጃ አሸክማ አማፂ ታሰማራብናለች፡፡ ነጋ ጠባ በወዮላችሁ ትፎክርብናለች፡፡ ለዚህ መፍትሔው አንድ ብቻ ነው – ህዳሴን ከፍፃሜ ማድረስ መቻላችን ለዓለም ማሳየት፡፡ ያን ጊዜ ግብፅ በቤታችን ጉዳይ እየገባች የከፋው ማስታጠቋን ታቆማለች፡፡ 
ካስታጠቀቻቸው ጋር እየተዋጋን – ህዳሴን የሚያቆመን ምድራዊ ሀይል እንደሌለ ትማራለች፡፡ ግብፅን ከ‹‹አባይ የእኔ ብቻ ነው›› ቅዠት ማባነን የሚቻለው፣ ለፍትሀዊ የጋራ ጥቅም ማንበርከክ የሚቻለው ህዳሴን ከግብ በማድረስ ብቻ ነው፡፡ ግብፅን በምእራባውያን አንቀልባ ውስጥ ያስቀመጣት ጂኦግራፊና የስዊዝ ካናል ነው፡፡ ግብፅን ፈርጣማ ጉልበት የሰጣት ወንዛችን አባይና የአስዋን ግድብ ነው፡፡ የህዳሴ ግድብ ከምእራባውያን ጀርባ ላይ እንደማያፈናጥጠን እናውቃለን፡፡ ቢያንስ ግን ከስንዴ ድርጓቸው ነፃ ያወጣናል፡፡
 
ኢትዮጵያ ከግብፅም ሆነ ከሱዳን ጋር አባይን በፍትሐዊ መንገድ መጠቀም ነው ፍላጎቷ፡፡ ይህን ፍትሃዊ ፍላጎቷን ይዛ ነው ለድርድር የቀረበችው፡፡ ይሁን እንጂ ግብፅና ሱዳን በፍትሀዊ አጠቃቀም አያምኑም – አይቀበሉም፡፡ ቀኝ ገዢዎቻቸው ለራሳቸው ጥቅም ሲሉ የፈረሙት ውል ላይ ተጣብቀን እንሙት ነው የሚሉት፡፡ እንግሊዝ እርካሽ የጥጥ ምርት ለማረስ የግብፅ መሬትና የአባይ ውሃ ያስፈልጋት ነበር፡፡ ግብፅን በቅኝ ግዛት አባይን በፊርማ ወሰደች፡፡ የሚገርመው ዛሬም ግብፅና ሱዳን ያለ ምዕራባውያን አደራዳሪነት አንስማማም ብለው የሙጥኝ ብለዋል፡፡ ፍላጎታቸው ግልፅ ነው፡፡ ትላንት ቀኝ ገዢዎቻቸው ያስቀመጡትን ፊርማ እንዲያፀድቁላቸው ይፈልጋሉ፡፡ ኢትዮጵያ የነፃነትን ዋጋ ከማንም በላይ ታውቃለች፡፡ በምንም መንገድ ትላንት አፍሪካን ‹‹የጨለማው አህጉር›› (the black continent) ብለው እየተሳለቁ፣ በቅኝ ግዛት እያማቀቁ ሀብቷን ሲዘርፉ የነበሩ ኢምፔሪያሊስት ቀኝ ገዥዎች ዛሬም በእጅ አዙር ለራሳቸው ጥቅም ትመች ዘንድ በሉአላዊነቷ ጣልቃ እንዲገቡ አትፈቅድም፡፡ ኢትዮጵያ አፍሪካ የአፍሪካውያንን ችግር ለመፍታት ብቃት አላት ብላ ታምናለች፡፡ 
 
ግብፅ በአባይ ውሃ ላይ ‹‹ታሪካዊና ተፈጥሮአዊ መብት አለኝ›› ትላለች፡፡ በእርግጥ ግብፅ ብቻ ሳትሆን 11 ሀገሮች በአባይ ላይ ተፈጥሮአዊ መብት አላቸው፡፡ አሳፋሪው ‹ታሪካዊ መብት› የምትለው ነው፡፡ እራሳቸው ቅኝ ገዢዎች ሳይቀሩ የሚያፍሩበትን የዘመን የቅኝ ግዛት ጥቁር ታሪክ በዚህ ደረጃ ማወደሳቸው አባይን እንዳንጠቀም የሚያደርግላቸው ከሆነ የትኛውንም አሳፋሪ ሸማ ለመከናነብ ወደኋላ እንደማይሉ ያሳያል፡፡
ታላቁ የህዳሴ ግድብ ለታችኛው የአባይ ተፋሰስ ሀገሮች (ለሱዳንና ለግብፅ) ምንም አይነት ጉዳት እንደማያስከትል ግልፅ ነው፡፡ ይህን በተመለከተ የቀድሞው የሱዳን የውሃ ሀብትና መስኖ ልማት ሚኒስትር፣ ጃንዋሪ 28 ቀን 2020 (ከአንድ ዓመት ከስድስት ወር በፊት) በአልጀዚራ ቴሌቪዥን ላይ ቀርበው ከተናገሩት ቀንጭቦ መመልከት ተገቢ ነው፡፡
 
“Sudan’s position is that, since this dam is a hydropower generation dam, it will not have a big effect on the amount of water that is going through to Sudan and then going to Egypt, because the loos is only the evaporation, which is only 26 m3 per/year.”
 
ሱዳናዊው እንዳሉ ግድቡ ሁለቱ ሀገራት ላይ የሚያስከትለው ጉዳይ የለም፡፡
እንዲያውም
• ለአካባቢው ሀገራት ርካሽ የኮረንቲ ሀይል ያቀርባል፤
• በሱዳን ላይ የሚደርሰውን የጎርፍ አደጋ ይከለከላል፤
• ዓመቱን ሙሉ የማይዋዥቅ የውሀ ፍሰት እንዲኖር ያደርጋል፤
• የውሀ ትነትን ይቀንሳል፤
• ደለልን በመቀነስ የሱዳንና የግብፅ ግድቦችን ውሃ የመያዝ አቅም ከፍ ያደርጋል፡፡
 
የሚገርመው ይህ ለሱዳንና ለግብፅ ጠፍቷቸው አይደለም፡፡ ጉዳዩ ግድቡ ስለሚጎዳቸው አይደለም፡፡ የሚያስፈራቸው፣ እንቅልፍ የሚነሳቸው ውሃ የማጣት ስጋት አይደለም፡፡ ግብፅ በጣም ሰፊ የከርሰ ምድር ውሃ አላት፤ የባህርና ውቅያኖስ ውሃ እያጣራች መጠቀምም ትችላለች፡፡ እንቅልፍ የሚነሳቸው የኢትዮጵያውያን የእንችላለን መንፈስ ማዳበር ነው፡፡ ለዘመናት ከየትኛውም ሀገር ብድርና እርዳታ እንዳናገኝ ጉሮሮአችንን አንቀው፣ ጦርነትና ግጭት እየፈበረኩ ሰላማችንን ነስተው የሰለቡትን የእንችላለን መንፈስ መቀዳጀታችን ነው የሚያስፈራቸው፡፡ ፈሩም – አልፈሩ፣ የጦርነት ልምምድ አደረጉም – አላደረጉ፤ አዝለዋቸው ለሚኖሩት ምእራባውያን ከሰሱ -አልከሰሱም፣ ከእንግዲህ የህዳሴ ግድብን ከመጠናቀቅና ኮረንቲ ከማመንጨት የሚያቆም ሀይል የለም፡፡ 
ህዳሴ ግድብ በጅምር የሚቀረው የሱዳንና ግብፅ ሰንደቅ አላማቸውን በሙሉ የኢትዮጵያ ግዛት ማውለብለብ ሲችሉ ብቻ ነው፡፡ ያ እንደማይሆን ደግሞ ከእነሱ በላይ የሙጥኝ ያሏቸው የቀድሞ ቀኝ ገዢዎቻቸው ምእራባውያን ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡
Filed in: Amharic