>
5:13 pm - Thursday April 19, 3663

የኦነግ/ ኦዴግ የቆየ አቋምና የአማራው የህልውና ትግል...!!! (አያሌው ፈንቴ ያቀረበው ጥናት - የመጨረሻው ክፍል)

የኦነግ/ ኦዴግ የቆየ አቋምና የአማራው የህልውና ትግል…!!!

የታሪክ ተመራማሪው አያሌው ፈንቴ ያቀረበው ጥናት የመጨረሻው ክፍል

 

*…ገላሳ ዲልቦ፣ አቢዩ ገለታ፣ አባ ጫላ ለታ፣ አባ ቢያ፣ ቦሩ በረካ፣ ሌንጮ ባቲ፣ ዳውድ ኢብሳና ሌሎች….
ባለፉት 26 በላይ ዓመታት በተለያዩ ጊዜያት የኦነግ / የኦዴግ አመራሮች የኢትዮጵያን አንድነት በተመለከተ ስለሚያራምዱት አቋም በተለያዩ ሚዲያዎች (አሜሪካ ድምፅ፣ SBS እና ጦቢያ) ተቀምጦ እናገኛለን፡፡ አመራሮቹ ምን ይላሉ? የሚለውን ስንዳስስ፣ ከብዙ በጥቂቱ የሚከተሉትን ተመሳሳይ አቋሞች እናገኛለን፡-
† ጦቢያ (በነሀሴ 17 ቀን 1993 ዓም)፡-
«ኦነግ ከአነሳሱ “የኦሮሞ ሕዝብ በቅኝ ግዛት የተያዘ ሕዝብ ነውና ነፃ መውጣት አለበት” ባይ ነው። ከነፃ ኦሮሚያ በመለስ
ድርድር ውስጥ መግባት “ለአበሾችና ለኢትዮጵያውያን መንበርከክና ማደር ነው” የሚሉ በአንድ ወገን ተሠልፈዋል። እነኚህም፤
(1ኛ) ገላሳ ዲልቦ – የቀድሞ የደርግ የሕዝብ ድርጅት ጉዳይ ጽ|ቤት ካድሬና የኦነግ ዋና ፀሀፊ የነበረው፣
(2ኛ) አቢዩ ገለታ – በእናቱ የጎጃም አማራ የሆነውና በደርግ የመጀመሪያዎቹ ዓመታት የአሩሲ ክፍለ ሀገር ዋና አስተዳዳሪና እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስም የኦነግ የውጭ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው፣
(3ኛ) አባ ጫላ ለታ – የሌንጮ ለታ ወንድምና የኦነግ ሠራዊት አዛዥ የነበረ።
እነኚህ “የኢትዮጵያ ጉዳይ አያገባንም ባዮች” ናቸው። ሌላው ወገን ደግሞ “አቋማችን የዓለምንና የአካባቢያችንን ሁኔታ ያገናዘበ ሊሆን ይገባል። ለኦሮሞ ሕዝብ ብዛትና ሀብት የሚመጥን ቦታና መብት ለኦሮሞ ሕዝብ ከተሰጠ፣ ከቀሪው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር መኖር የማይቻልበት ምክንያት የለም” የሚለው ቡድን አመራሩን ይዟል። በዚህ ቡድን ውስጥ፤
(1ኛ) አባ ቢያ – በ1966 ዓ.ም ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ጅማሮ ላይ የከፋ ዋና አስተዳዳሪ የነበረው፣
(2ኛ) ሌንጮ ባቲ – የኦዴግ የውጭ ግንኙነት ኃላፊው፣
(3ኛ) የአሁኑ የኦነግ ፀሀፊ ዳውድ ኢብሳ ይገኙበታል።»
† የአሜሪካ ድምፅ (2005 ዓ.ም)
በግሪጎሪያን 2012 ታህሳስ መጨረሻ ላይ ቦሩ በረካ ኦነግን ወክሎ በአሜሪካ ድምፅ እንዲህ አለ፡-
«ከመገንጠል ውጭ አማራጭ የለም ይልና፣ እንደ ኦሮሞ ብናስብ፣ ይህን የመሰለ ብዙሀን ሕዝብ፣ ይህን የመሰለ የኢኮኖሚ ጀርባ የሆነ አገር እያለን፣ በቆዳ ሥፋትም በጣም ሠፊው ክልል ሆኖ እያለ፣ ሁልጊዜ የኦሮሞ ሕዝብ ወደጎን የተገፋ ነው” ብሎናል። የኦነግ አቋም ያው እንደጥንቱ ነው።»
† SBS (2007-8 ዓ.ም)
በግሪጎሪያን 2014 የኦዴግ ሰዎች በ SBS ተጠይቀው እነ ሌንጮ ባቲ የሚከተለውን ማብራሪያ ሰጡ፡-
“ኢትዮጵያ እንደ አገር አንድነቷ ተጠብቆ በሰላም ልትኖር የምትችለው ፌደራል (የጎሳ) የሆነ ሥርዓት ውስጥ ስትተዳደር ነው የሚል አመለካከት አለን። ይህ ማለት ኢትዮጵያ ውስጥ የማንነት የፖለቲካ ጥያቄ ስላለ መልስ ሰጥተን፣ የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች ቋንቋቸውን የማስከበር፣ የፖለቲካ መብታችውን የመጠቀም፣ የተፈጥሮ ሀብታቸው ላይ የማዘዝ፣ ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር፣ ከሌላ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ጋር ደግሞ አብሮ የሚያስተዳድራቸው የፌደራል አወቃቀር እንዲኖራቸው ነው የምንመኘው” ሲል የገለጸው ሌንጮ ባቲ፣ በተጨማሪም የኢትዮጵያ አስተዳደር “በብሔሮች መዋቀሩ ትክክል ነው፣ ባለው ህገ መንግሥት መታገል እንችላለን” ብሏል።
ጠያቂው፡- አሁን እንዳለው ቋንቋን መሠረት ያደረገ ፌዴራሊዝም ነው ወይስ እንደ አሜሪካና አወስትራሊያ ዓይነት? ብሎ ይጠይቃል፡፡
ሌንጮ ባቲ ሲመልስ፡- «ይህ አሁን ያለው ቋንቋን መሠረት ያደረገ ፌዴራላዊ አወቃቀር ትክክለኛ ነው። ግን ዲሞክራሲያዊ ስላልሆነ የፖለቲካ ችግሮች እየታዩ መጥተዋል።»
ጠያቂው፡- አዲስ አበባን በተመለከተስ? ብሎ ይጠይቃል፡፡
ሌንጮ ባቲ ሲመልስ፡- «ፊንፊኔ ላይ ነፍጠኛው ከሰሜን መጥቶ የራሱን ባህል አስፋፍቶ ኑሯል፣ የኦሮሞ ነች፣ የፌዴራል ከተማ ነች። በታሪክ ባለቤትነት የኦሮሞም ዋና ከተማ ሆናለች።»
እንግዲህ ከላይ በተጠቀሰው መልክ የቀረቡትን የኦሮሞ ድርጅቶች መሪዎች አቋሞች ስንፈትሽ እነኚህ የተጠቀሱት የኦነግና የኦዴግ ልዩነቶች፣ ልዩነቶች ሳይሆኑ ኦነጎች ካለው ከኢትዮጵያ ሁኔታ በመነሳት ለአንድ ዓይነት ግብ ሁለት የተለያዩ የታክቲክ አካሄዶችን በመጠቀም፣ ሥነ ልቦናችንን ጠንቅቀው ስለተረዱት፣ በሌሎቻችን ላይ የተለያዩ ጫናዎችና የማደነጋገሪያ ሽወዳ በማስቀመጥ የሚፈልጉትን ነገር ተግባራዊ ለማድረግ ነው።
ከሦስት ዓመት በላይ ያስቆጠሩት ኦነግ እና ኦዴግ ብለው አንድ ዓይነት ግብ ያላቸው፣ ነገር ግን ሁለት ሥም ያላቸው ድርጅቶች ሌላውን ህብረተሰብ ግራ በማጋባትና እርስ በርሱ በመከፋፈል ድጋፍ ለማሰባሰብ ጭምር፣ በሁለት አቅጣጫ ብቅ ብለው ግንጠላውን ሲያፋጥኑ ይስተዋላሉ።
ኦነግ ነኝ ባዩ ቦሩ በረካ «ብዙ ሕዝብ፣ ሠፊ መሬትና ሀብት ያለን ሆነን ስለተገፋን እንገነጠላለን» ይለናል። ባንዲራውም በየሰላማዊ ሰልፉና በየስብሰባው የምናየው ነው።
ኦዴግ (ውስጡ ኦነግ የሆነ ልብ ሊያማልልና ሊያታልል ካባውን ገልብጦ የመጣውን) ድርጅት የሚመሩት የኦነግ መሥራቾች እነ ሌንጮ ለታ፣ እነ ዲማ ነጎ፣ እነ ሌንጮ ባቲ ወዘተ ናቸው። ዲማ ነጎ ከዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ ጋር በአሜሪካ ድምፅ ቃለምልልስ ቀርቦ ስለ ባንዲራው ተጠይቆ ሲመልስ ባንዲራችን ከኦነግ ጋር አንድ ነው ብሏል።
ሁለት የተለያዩ ድርጅቶች ሆነው አንድ ዓይነት ባንዲራ መጠቀም በራሱ ያላቸውን “አንተ በዚህ ሥራ እኔ በዚያ ልሥራ“ የሚል ውሥጣዊ የታክቲክ አሠራር እንጅ፣ የእነርሱም አቋም “የጎሳን ፌዴራሊዝም መሠረት ያደረገ ለኦሮሞ ሕዝብ ብዛትና ሀብት የሚመጥን ቦታና መብት ለኦሮሞ ሕዝብ ከተሰጠ ከቀሪው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር መኖር የማይቻልበት ምክንያት የለም” ነው።
ጥያቄው ግን ካልተሰጠስ? ወይም እንደሚመኙት ካልሆነስ? ነው፡፡ ጦርነት ሊከፍቱ ነው? ወይስ ሊገነጠሉ?
ደግነቱ ለእነኚህ ድርጅቶች ተራው የኦሮሞ ሕዝብ ድጋፉን መንሳቱ ነው።
ማሳሰቢያ! ወያኔና ኦነግ ከአገሪቱ መሬት የዝሆን ድርሻቸውን ወስደው አማራውን እርቃኑን ካስቀሩ በኋላ የእነ ሌንጮ ቡድን «የኦሮሞ ሕዝብ ብዛት አለው፣ ሀብቱም ተዝቆ አያልቅም፣ ክልሉም ሰፊ ነው፣ በዚያው ልክ ተጠቃሚ መሆን አለበት፣ ይህ ካልተደረገልን የኢትዮጵያ አንድነት አይታሰብም» ሲል፤ ኦነግ ደግሞ እንገነጠላለን የሚሉትን የልጆች ማስፈራሪያ አንግቧል።
ይህንን ከገፉበት፣ አለቃ ገብረ ሀና “እዚያም ቤት እሳት አለ” እንዳሉት፣ በኦሮሞ ወረራ ወቅት በኦሮሞው የተዋጡ የሌሎች ሕዝቦች መኖሪያ የነበሩ በሌላም ስመ ይታወቁ የነበሩ የኢትዮጰያ ግዛቶች ወደ ቀድሞው ሥማቸው መመለስ እና ነባር ነገዶችም የባለቤትነት ቦታቸውን መልሰው መያዝ ይኖርባቸዋል። ለዚህ ደግሞ የሚከፈለው መሥዋዕትነት ተከፍሎም ቢሆን ይሆናል እንጅ ወያኔና ኦነግ የሸነሸኑትን ተቀብለን አንኖርም።
ይህ ሲሆን የሚኩራሩበት ሀብትም ክልልም እና የሕዝብ ብዛትም ይመናመናል፣ ምክንያቱም የሌሎችን ቦታና ሀብት ስለወሰዱ፣ የኦሮሞ ሕዝብ የሚባለውም በግዳጅ የተያዙትም የተለያዩ ነገዶች ሲለዩ ይኮሰምናል። ከዚያ በኋላ ሁላችንም ልካችንን እናውቃለን። “የሰው በልቶ አያድሩም ተኝቶ” እንደሚባለው የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር በምንግባባበት መንገድ መግባባታችን አይቀሬ ነው።
የወያኔ ትግሬዎች ላይ ማተኮር ሲገባ ለምንድነው ስለ ኦነግ የሚነሳው? የሚሉ ተችዎች ካሉ መልሱ “የወያኔ ትግሬዎች የአማራውን ዘር ለማጥፋት ቀደም ሲል በሥውር አሁን ደግሞ በግልፅ ጦርነት ሥለአወጁበት፣ አማራው በወያኔ ትግሬ ላይ ከማተኮር አልፎ፣ የሞት የሽረት ትግል ሥለሚያካሂድ በአማራው ላይ ያተኮራችሁ ተችዎች ከአማራው ራስ ወርዳችሁ በወያኔ ላይ እንድታተኩሩ ምክሬን እለግሳለሁ።
በኤርትራ ያሳዬነውን ንዝህላልነት በተመሳሳይ ሁኔታ በእነኦነግና በመሥራቾቹ ሊደገም ዳዴ ሲል በመገንዘባችን “ከኋላ ወየው ጠንቀቅ ብለህ ቆየውን” መምረጣችን የግድ ነው።
መታወቅ ያለበት ጉዳይ አብሮ በመኖር ሁሉም ተጠቃሚ ነው፣ በመለያየት ሁሉም ተጎጅ ነው፣ አማራው ይህንን ጠንቅቆ በመረዳቱ ያላንዳች መታከት፣ ተቻችለን እንኑር ብሎ እየሞተም ለምኗል፣ አሁንም ቢዘገይም ተሟጦ አላለቀምና አብሮና ተሳስቦ ለመኖር ማንኛውም ነገድ ያስብበት።
ወያኔም ተለምኖ ነበር፣ ልመናው ለኢትዮጵያ አንድነት ሲባል ነበር፣ ግን እንደፍርሀት ቆጠረው። የግፉ ፅዋም ሞልቶ ሲፈስ ውጤቱ እንደምናየው ሆኗል። ከእንግዲህ የፈጀውን ጊዜ ይፈጃል እንጅ አንላቀቅም። ከትግሬ ጋር አብሮ መኖር የሚያከትም ከሆነ፣ የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ከተከዜ ወዲህ ብቻ ሳይሆን ከተከዜም ወዲያ እሥከ አምባላጌና ማይጨው ያለውን መሬታችንን እናስመልሳለን።
የኢትዮጵያ አንድነት የተደመሰሰውና የጠፋው ወይም ያለቀለት የትግሬ ወያኔዎችና ኦነግ በሽግግር መንግሥት ተብዬው 1983 ዓ.ም ተሰብስበው አገሪቱን ሲሰነጣጥቁና ሕዝቡንም ሲያመሰቃቅሉት ነው። ይህም አካሄዳቸው፣ አፈፃፀማቸው፣ ከህገ መንግሥቱ አንቀፅ 39 ጀምሮ በጎሳ እሥከመሸንሸን መድረሳቸው ቁልጭ አድርጎ የሚያሳዬን ቢላዋ እንደተሳለልን ነበር።
ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አማራው ለእርድ እንደቀረበ ፕ/ር አሥራት ወልደዬስ ቀድሞ ሥለገባቸው ከባልደረቦቻቸው ጋር በመሆን መዐሕድን በማቋቋም የእሳት አደጋውን ለማጥፋት ሲጥሩ፣ ከትግሬው ወያኔ ባልተናነሰ መልኩ ራሱ አማራ ነኝ ባዩ ጭምር ፀረ-አማራነትን በማሥተጋባት ታገላቸው፣ ታገለን። እኛም በየአገሩ የነበርን ወገኖች ጥቂትም ብንሆን “አማራ ብሎ መነሳት ዕብደት ነው” እያለ የገዛ ወገናችን የጭቃ ጅራፉን ቢያጮህብንም ምንም ሳይበግረን እሥከቻልን ብንጥርም ሁሉም ነገር ከፕሮፌሰር አሥራት ጋር አረፈ።
አማራው ወገናችን በአማራነት አልደራጅም ብሎ የራሱን ድርጅት አፍርሶ፣ በምኞትና በፍላጎት ብቻ ታጥሮ በተጨባጭ የሌለንና ያለቀለትን የኢትዮጵያን አንድነት መፈክር ይዞ ሲንገዛገዝ፣ ጠላት ያለማቋረጥ ለ25ዓመታት በአማራነት እየመረጠ ሲቀጠቅጠው፣ ሲያባረው፣ ሲያጠፋውና ሲገለው ኖረ።
ይህን ሁሉ ዓመታት ጠላት ለመጠናከር እና ብዙ ነገር ለማውደም ጊዜ ከማግኘቱም በላይ፣ አማራውን በአማራነት እየገደለው በኢትዮጵያ አንድነት መንገዛገዙ፣ ቀሪውን አማራ ከማስጨረስና የአማራውን ሠቆቃ ከማራዘም በስተቀር መፍትሄ እንደማያመጣ የተረዳው፣ ትናንት ከእርሱ አብራክ የወጣው ወጣት አማራነቱን አጉልቶ ብቅ ሲል የተሰማኝ ደስታ ወሰን የለውም። ሥመኘው የኖርኩትም አማራው ለማንነቱ ቆርጦ ሲነሳና ሲታገል ማየት ነበር። እደግ ተመንደግ እለዋለሁ። እኔም እሥከህይወቴ ፍፃሜ ከጎኑ ነኝ።
የሞረሽም ያልተቋረጠ የቅስቀሳና የማንቂያ ሥራዎች ተግባራዊ ሆነዋል፣ የሚያስመሰግነው ነው። አማራ ብለው ለተነሱት የአማራ ድርጅቶችም ሆነ ግለሰቦች አክብሮታችን ትልቅ ነው። በተለይ ደግሞ አሁን እንደጀመራችሁት ተቀራርባችሁ አንድነታችሁን እያጠናከራችሁ በሄዳችሁ ቁጥር ሁላችንም እንደ አንድ ሰው ማሰብ እንጀምራለን፣ ጊዜውም ሩቅ አይደለም።
መደምደሚያ! የአማራ ማንነቱ በወያኔ ትግሬዎችና በሌሎች ፀረ-አማራ ኃይሎች ሥለተካደና ሊያጠፉት ሥለሚቅነዘነዙ እንዲሁም የመኖር ዋስትናውና ህልውናው አጠያያቂ በመሆኑ የራሱን ማንነት ለማሥከበር ቆሟል። አማራው ዛሬ ከምድረ ገፅ ከመጥፋቱ በፊት ለራሱ ህልውናና ለማንነቱ ብቻ እንደሚዋደቅ መታወቅ አለበት። ይህም መብቱ መሆኑን መቀበል የግድ ነው።
ይህንን መብቱን ለማስከበር ሲታገልና ሲዋደቅ ችግሩን ተረድተው ከጎኑ ከመቆም ይልቅ፣ ቀደም ሲል እየተጠቃና ሳይገል እየሞተ በተጓዘበት መንገድ እንዲቀጥልና እንዲያልቅ የሚመኙ ካሉ ምኞት ብቻ ሆኖ ይቀራል። በአማራው ላይ ግፍ የሠሩና የሚሰሩ የዘር ቡድኖችን እያቀማጠሉ*፦
(1) “አማራው በአማራነት መቆሙ ወያኔ በቀደደው ቦይ መፍሰስ ነው” ለሚሉት ጠላቶች መልሳችን “ያረጀ ያፈጀ የማዘናጊና ትጥቅ አስፈች ንግግር ስለሆነ ተቀባይነቱ አክትሟል” ነው፣
(2) “አማራውን አክራሪ” ሆኗል ለሚሉት ኃይሎች፣ አማራው ሞቶ እነርሱ መኖር የሚመኙና ከወያኔ ለይተን የማናያቸው ጠላቶች ሥለሆኑ፣ መልሳችን “የከረረው ይበጠስ” ነው።
ከእንግዲህ አማራው አምርሯል፣ የጀመረውንም ከፍፃሜ ሳያደርስ እንደማይቆም እቅጩን አውቆ አብሮ መቆም ነው፣ አለዚያ ከአማራው ራስ ወርዶ አርፎ መቀመጥ ወይም የራስን ሥራ መሥራት ነው።
አማራው በትግሉ ማንነቱንና ህልውናውን ያሥከብራል፣
አያሌው ፈንቴ
ተፈጸመ፡፡
*የግርጌ ማስታወሻ፡- በ2009 ዓ.ም የተሠራው ይህ አሁን ያለንበትን ሁኔታ ራሱ አስቀድሞ የተነበየ አስገራሚ የምርምር ጽሑፍ በጥናት መልክ እና በመጽሐፍ ከወጣ በኋላ ባሉት ጊዜያት፣ በሀገራችን የተከሰቱ አንዳንድ ሁኔታዎችን ማስታወስ አስፈላጊ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ይህ ጥናት ከቀረበ በኋላ በኢትዮጵያችን አራት አንኳር ነገሮች ተከስተዋል፡-
1ኛ/ ኦነግ ከአሸባሪ ድርጅትነት ተሰርዞ በህጋዊ መንገድ ከነትጥቁ ወደ ሀገር ውስጥ ገብቶ እየተንቀሳቀሰ ነው፣
2ኛ/ የወያኔ (ህወኀት) ኃይል ከኢህአዴግ የጎሳዎች ግንባር ወጥቶና ከማዕከላዊው መንግሥት ሥልጣን ተገፍቶ ጦርነት ተከፍቶበታል፣ የወያኔ ሀይል ተሸንፎ ከተሞችን የለቀቀ ሲሆን፣ በገጠር ውጊያ ላይ ነው፣ በኦዴፓ-መራሹ መንግሥት የሚደገፍ የለዘብተኛ ወያኔዎች ጊዜያዊ አስተዳደር መቀሌ ላይ ተመስርቷል፣
3ኛ/ በኦዴፓ የሚመራ ሆኖ አዴፓን (ብአዴንን) እና ሌሎች የብሔር ድርጅቶችን ያቀፈ የኢህአዴግ መንግሥት ‹‹ብልጽግና›› በሚል አዲስ መጠሪያ ወያኔና ኦነግ አስቀድመው የመሠረቱትን የጎሳ ፌዴራሊዝም አገዛዝ አጠናክሮ ቀጥሎበታል፣
4ኛ/ በእነ ሌንጮ ባቲ የሚመራው ኦዴግ ወደ ሀገር ውስጥ በህጋዊ መንገድ ገብቷል፣ ከኦዴፓ ጋርም በህዳር 2011 ዓ.ም (በጎርጎሮሳውያን በህዳር 29 ቀን 2018) የውህደት ስምምነት ተፈራርሟል (#Ethiopia፣ DireTube፣ 29 Νοεμβρίου 2018 •
የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) እና የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኦዴግ) ተዋህደው መቀጠል የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ሰነድ ተፈራረሙ)፡፡
በተከታታይ ላስነበበን እጅግ ጠቃሚ ጥናት ለታሪክ ተመራማሪው አያሌው ፈንቴ ከልብ የመነጨ ምስጋናን አቀረብን፡፡
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!
_________
ዋቢ መፃሕፍት፣
Ω ይልማ ደሬሳ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ በ16ኛው ክፍለ ዘመን፣ ብርሀንና ሰላም ማተሚያ ቤት፣ አዲስ አበባ፣ 1959 ዓ.ም
Ω ተክለፃዲቅ መኩሪያ፣ የግራኝ አህመድ ወረራ፣ ብርሀንና ሰላም ማተሚያ ቤት፣ አዲስ አበባ፣ 1966 ዓ.ም
Ω ሞረሽ ወገኔ ዐማራ ድርጅት፣ ምጽአተ አማራ፣ ዋሽንግተን ዲሲ፣ 2009 ዓ.ም
Ω ሚጉኤል ዴ-ካስታሆንዝ፣ የፖርቹጋሎች ጀግንነት፣ ተርጓሚዎች ዶክተር ሙራድ ካሚልና አቶ ዮናስ ቦጋለ፣ ተስፋ ማተሚያ ቤት፣ አ.አ.፣ 1952 ዓ.ም
Ω ጦቢያ፣ ኦነግ፣ አ.አ.፣ ነሐሴ 17 ቀን 1993 ዓ.ም.
Ω አባ ኒቆዲሞስ አሰፋ፣ በኢሳት ቃለ ምልልስ
Ω ቦሩ በረካ (የኦነግ አመራር)፣ በአሜሪካ ድምፅ ቃለ መጠይቅ፣ 2005 ዓ.ም. (በጎርጎሮሳውያን 2012)
Ω ሌንጮ ባቲ (የኦዴግ አመራር)፣ በSBS ቃለ መጠይቅ፣ 2007-2008 ዓ.ም. (በጎርጎሮሳውያን 2014)
Ω Alvarez, Francisco: Verdadeira Informacao፣ የግራኝ አህመድ ወረራ በተባለው የተክለ ጻዲቅ መኩሪያ መፅሐፍ ውስጥ የተተረጎመ
Ω Rossini, Conti: Storia di Etiopia, Corpusco 1958 Liber Axume Corpusco 1962
Ω Cerulli, Enrico: Studi Etiopia-Storia di Harar
Ω Bassett, Rene: Etudes Sur L´histoire d´Ethiopie (ከአረብ ፋቂህ አብደል ቃድር መፅሐፍ ተወስዶ በዚህ ጥናት ወስጥ የተተረጎመ)
Ω Guidi, Ignazio: Histoire genti Galla, Corpusco, Louvian, 1960 (በ1530ዎቹ አባ ባሕርይ ሥለኦሮሞዎች አመጣጥ በግዕዝ በእጃቸው የፃፉት ማስታወሻ በዚህ ጥናት ውስጥ ተተርጉሟል)
Ω Manroe, Jones: Histoire de L´Abissinie, 1936 Roma
Ω Pereira, E.: Chronica de Susenyos, Corpusco, 1962
Filed in: Amharic