>
5:21 pm - Sunday July 21, 9399

የቢራ ፋብሪካ “ጁንታ” መኖሩን ስንቶቻችን እናውቃለን? (ግርማ በላይ)

የቢራ ፋብሪካ “ጁንታ” መኖሩን ስንቶቻችን እናውቃለን?

ግርማ በላይ


አገር በትህነግና ኦህዲድ ሠራሽ ችግሮች እንደአንጋሬ ተወጥራ ባለችት ወቅት ስለቢራ ማውራት ቅንጦት መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ቢሆንም የተቀሰፍንበት ጦርነት አቅጣጫውና ዓይነቱ ብዙ ስለመሆኑ ይህ አሁን የማነሳው ጉዳይ አንዱ አመላካች ነውና በመጠኑ መዳሰሱ ጉዳት የለውም፡፡

ከቀደምት የቢራ ፋብሪካዎች ውስጥ ይካተታል፡፡ በስም እንትና ነው ማለቱ ከህግም ከሞራልም አኳያ ትክክል ባለመሆኑ በሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ስም እምላለሁ የዚያን የወያኔ ማፊያ ቢራ ፋብሪካ እዚህ ላይ በስም አልጠራውም፡፡ ከፈለጉ ግን ቄሶች ይጥሩት፡፡ ቄስና ጠላ መቼም ….፡፡ እያደረሰብን ያለውን በደል ግን እገልጻለሁ፡፡ የበደሉን መነሻም እንዲሁ፡፡ መንግሥት የለንም እንጂ ቢኖር ኖሮ መዘጋት የነበረበት እጅግ ግፈኛና ሻጥረኛ ፋብሪካ ነው፡፡ 

ይህ አንጋፋ የቢራ ፋብሪካ የሚያመርተውን ድራፍት ቀደም ሲል ጃቦምውን በብር 2.50 እንዳልጠጣን አሁን በአማካይ ብር 30 ሆኗል፡፡ ይህ ደግሞ በልማዳዊው አጠራር ለእንደኔ ዓይነቱ “ንዑስ ከበርቴ” የሚቀመስ አልነሆም፡፡ በወር የብር 5 እና 6 ሽህ ደሞዝተኛ የጤፉ ዋጋ እንደዚያው 6 እና 7 ሽህ ብር ገብቶ ከንፈር ለማታረጥብ አንዲት ብርጭቆ ድራፍት ብር 30 ማውጣት ከባድ ኪሣራ ነው፡፡ እሱን እየተከተሉ ባለአበሻ አረቂዎች ባቅማቸው መለኪያውን ብር 10 አስገብተውታል፡፡ የት እንሂድ?

ይህን የቢራ ፋብሪካ ጨምሮ በርካታ የንግድ ድርጅቶች በወያኔዎች ወይም በወኪሎቻቸው ቁጥጥር ሥር ሆነው ብዙ ብር እየሰበሰቡ በምሥጢርና በመያድ (ኤንጂኦ) ስም ወደ ትህነግ እንደሚልኩ ይነገራል፡፡ ወያኔ ኢኮኖሚውን በእጅ አዙር እንደተቆጣጠረ ነው፡፡ ገንዘብ ደግሞ ለማንኛውም ዐመፅ ማካሄጃ የደም ሥር ነው፡፡ ኢትዮጵያ እየተወጋች ያለችው እንግዲህ በሁሉም አቅጣጫ እንደሆነ የሚነገረው ከዚህ አንጻር ትክክል መሆን አለበት፡፡ እኔው በምጠጣው ድራፍት ወገኖቼ የሚገደሉበትን ጥይት እገዛለሁ፤ ሁለት ጉዳት፡፡ የኔ ገንዘብ አላግባብ ይዘረፋል፤ ያ የተዘረፈ ገንዘብ ወደ ትህነግ ሄዶ ጥይትና ስንቅ መግዣ ይሆናል፡፡

ይሄ የቢራ ፋብሪካ ጥጋበኛ ነው፡፡ ዋጋ ሲጨምር ዐይን የለውም፡፡ ከፈለገ በወር ሁለቴም ሦስቴም ሊጨምር ይችላል፡፡ መንግሥትም ሆነ ሌላ አካል ሃይ አይለውም፡፡ ሌላው የሚገርመው ነገር ለሥራ አስኪያጁ የሚከፈለው ወርኃዊ ደሞዝ አንድ ሚሊዮን የሚጠጋ ነው፤ ከነጥቅማጥቅሙ እንዲያውም ከአንድ ሚሊዮንም ያልፋል፡፡ እንደሰማሁት የዚህ ሰው ደሞዝ በወር ብር 900 ሽህ ነው – እንዳልኳችሁ ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች ሳይደመሩ፡፡ አንድ ተራ ሱፐርቫይዘር ራሱ ከ60 እና 70 ሽህ ብር በላይ እንደሚከፈለው እንሰማለን፡፡ ለአንድ ኮማሪ ቤት ኃላፊ ይህን ያህል ደሞዝ መመደብ አነጋጋሪ ነው፡፡

በዚያ ላይ ይህ ቀበጥ የቢራ ፋብሪካ በኛ ገንዘብ ሲዘባነን ላሣር ነው፡፡ ስሙ በሚጠራበት ቦታ ሁሉ በማስታወቂያ ሰበብ ብዙ ሚሊዮን ብር እየመዠረጠ ይሰጣል፡፡ ስለዚህ አንድ ብርጭቆ ድራፍት ላይ ይህን ያህል ገንዘብ መቆለሉ አይገርምም፡፡ ከሀገሪቱ የደመወዝ እስኬል ፍጹም ተቃራኒ በሆነ ሁኔታ በአንዲት ድሃ አገር ውስጥ አንድን ሰው እንዲህ አንቀባርሮ ለማኖር ከድሆች እየተገፈፈ እንዲህ ያለ ግፍ ይፈጸማል፡፡ የኢትዮጵያ ጠ/ሚኒስትር ደሞዝ፣ የኢትዮጵያ ሚኒስትሮች ደሞዝ፣ የሀገሪቱ ፕሬዝደንት ደሞዝ፣ ወዘተ. ቢታይ ምናልባት የዚህ ቢራ ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ ደሞዝ የሁሉንም ሊሆን ይችላል፡፡ የባንክ ፕሬዝደንቶችን፣ የዓለም አቀፍ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎችን ደሞዝ ብናይ እንደዚህ የተጋነነ አይደለም፡፡ የዚህ ጠላ ቤት ማነው ቢራ ጠማቂ ፋብሪካ ግን የተለዬ ነው፡፡ ምን ስለሆነ? ጠይቁ፡፡

የሌሎች ቢራ ፋብሪካዎችን የሚበጠብጠውም እሱ ነው አሉ፡፡ የሱን መንገድ እንከተል ሲሉ ደምበኞች ስለሚሸሹ ለኪሣራ ይጋለጣሉ፡፡ ዋጋ አንጨምርም ቢሉ ደግሞ በተለይ ወያኔ በነበረበት ሰዓት በመጠጡ ኢንዱስትሪ እሱ ፈላጭ ቆራጭ ስለነበር አለመጨመር አይችሉም ነበር፡፡ የመጠጥ ፋበሪካዎችን ሥራ ቅጥአምባሩን ያወጣው ይህ “እሽ አትበሉኝ የሹም ዶሮ ነኝ” ባይ የጁንታው ፋብሪካ ነው – ሀሰቴን በሆነና ኩነኔው ወደራሴ በዞረ፡፡ለማንኛውም ይህ ፋብሪካ ጥናት ይደረግበትና ድሃን ከመበዝበዝና የሀገር ሀብትን ለጠላት እያሳለፈ በመስጠት እናት ሀገርን ከማውደም እንዲቆጠብ የሚመለከተው አካል ያስብበት፡፡ ዋጋቸውን በገቢያችን መጠን ሊያደርጉ የሚፈልጉ ሌሎች ፋብሪካዎችንም አይበጥብጥ፡፡ የድርጅቱ አመራር ሆዱ ላስቲክ ሆኖ አልጠግብ ባለ ጊዜ ሁሉ የስግብግብነት ዕድፉን እኛ ላይ አይደፍድፍብን፡፡ ይህችን ማስታወሻም እባካችሁን ከ1915 እስከ 1975 ዓ.ም ለተመሠረቱ የቢራ ጠመቃ ፋብሪካዎች አሳዩልኝ፡፡ ሁሉም አላፊ መሆኑን፣ ተያይቶና ተሳስቦ መኖር ግን ደግ መሆኑንም ለእምብርት-የለሾቹ ኃላፊዎች ንገሯቸው፡፡ ስልሳ ዓመት ሲሞላው ምርኩዝ መያዝ ለሚቃጣው ምድራዊ ሰውነት ይህን ያህል ለገንዘብ መንሰፍሰፍ ጥሩ አይደለም፡፡ አንዳንዴ ሲመቸን ለወገናችንም ለሀገራችንም ማሰብን እንልመድ፡፡ ጭንቅላታችን የተሸከመው አንጎል እንጂ ድንጋይ ወይም ነጭ ጭቃ አለመሆኑን እናስብ፡፡ … 

አሃ፣ ለካንስ ዛሬ ጳጉሜ 5 ቀን 2013 ዓ.ም ነው – የ13ኛው ወር የመጨረሻ ቀን፡፡ ስለዚህ ለመጪው ዘመን መልካም ምኞቴን ብገልጽ የሚከፋብኝ አንባቢ አይኖርም፡፡ እንኳን ለ2014ዓ.ም ዋዜማ (በሰላም?) አደረሰን፤ መጪው ዓመት ይህ ዓመትና ይህን ዓመት መሰል ቀደምት ዓመታት የማይደገሙበትና በሀገራችን ሰላምና ፍቅር የሚሰፍንበት እንዲሆን ከወዲሁ እመኛለሁ፡፡ መጪው ዓመት ከወያኔ፣ ከኦህዲድ፣ ከብአዴን፣ ከኢዜማ፣ ከሲአይኤ፣ ከኤም አይ ሲክስ፣ ከሞሳድ፣ ከአውሮፓ ኅብረት፣ ከኦነግ፣ ከዐረቦች፣ ከኦነግ ሸኔ፣ ከጉሙዝ ታጣቂ፣ ከሱዳን ሸማቂ፣ ከግብጽ ጦር ሰባቂ፣ ከአባይ ወንዝ ጦስ፣ ከኮቪድ፣ ከጠኔ፣ ከስደት፣ ከመፈናቀል፣ ከእርስ በርስ ግጭት፣ ከአልጠግብ ባይነት፣ ከኑሮ ውድነት፣ ከሙስና፣ ከማይምነት፣ ከዘረኝነት፣ ከጎጠኝነት፣ ከምቀኝነት… እስከወዲያኛው የምንፋታበት ዓመት ይሁንልን፡፡ (የጠላቶቻችን አበዛዝ ግን እንዴት ያስፈራል እናንተዬ! በስመ አብ!!!)

Filed in: Amharic