>

ሕልም እልም (ዘምሳሌ)

ሕልም እልም

ዘምሳሌ


ከሰባተኛው ንጉሥ መንፈስ

በህልሜ አንድ ሌሊት አንድ ሰው
እንዲህ ብለህ ፃፍ አለኝ ታሪኩ እነሆኝ

ከጅማ ወጥቼ አባጅፋር ትቼ
ብልፅግና ጀርባ ኮርቻ ደርቼ
እያልኩ ፈረሴን ቼ ሸገርም ገብቼ
ቃልኪዳን ሰጥቼ

ሕዝብ ድብን ይበል
ፈታ ዝንጥ  ልበል
አፋችሁን ዝጉ
ባላችሁበት እርጉ

ፓርኬን አሳምሬ
አሽከሬን ደርድሬ
ካአምሀራ ቆምሬ
ትግሬን አስደንብሬ

ሰዎች ተገደሉ
ከቤት ተፈናቀሉ
ቤቶች ተቃጠሉ
ሽብርተኞች ሞሉ

እና ምን ይጠበስ  እኔ ልንፈላስስ
ደሞሳ ብደግስ  ገና ከልጅነት
ኖሬ እንደምነግስ፣  በእናቴ ትንበያ
በስሜ ስወደስ፣  እየተባልኩ ንጉሥ
በኢትዮጵያ ንገስ
በአፄዎቹ  መንበር  ፊጥ በል ተኩነስነስ

ገና  ሳላስቆጥር  ግዛቴን ደርድሬ
እራት አስቋጥሬ  በዶላር ታጥሬ
ቄጤማም ገብሬ በገዳ አሰጨፍሬ
ከወንበር ሰፍሬ  በጌታም አድሬ
በፀሎት ወጥሬ  በአላህም ኖሬ
በዱዐ ዘይሬ  በጀዝቦች ታጥሬ

ሕዝቡ ሚጮህብኝ  እኔን የማይገባኝ
ከሰው አስበልጬ  በራሴ ተውጬ
ስልጣኔን መርጬ ኮርቻም ፈርጥጬ
አባ ጅፋር ትቼ   ከሸገር ገብቼ

ፓርኮች ባሳመርኩኝ
ዛፎች በተከልኩኝ
መንገድ ባፀዳሁኝ
የህልሜን በኖርኩኝ

ቁመና አሳምሬ  ምክር ቤት ፎግሬ
በነገስኩ ባገሬ  በፖርክ ተሽከርክሬ
ዙሪያውን አጥሬ  ፒኮኳን ገትሬ
በገዛ ድምሬ  ሆኜ  በመንበሬ
በስንዴ እርሻ ልማት  ዞሬ ተሽከርክሬ

መብቴን አስከብሬ  አለቁ አትበሉኝ
ሽምጥ  በጋለብኩኝ  ፈረሴን ቼ  ባልኩኝ
እኔም ቀን ወጥቶልኝ   ወንበር በጨበጥኩኝ

ዜጎች ተጎዱብን   ልጆች ወሰዱብን
ቤት ተቃጠለብን   ሰዎች ታረዱብን
ሀብትም ወደመብን  ይኽ ሁላ ለምኔ
በአገዛዝ ዘመኔ  እያለሁ በውኔ

እስኪ ለቀቅ አርጉኝ  ለዙፉኔ ልቀኝ
እነከሌ ሞቱ   ከቤት እደወጡ
እኔ ምንአገባኝ   ባገር አልነበርኩኝ
ልመና በሄድኩኝ   ፓርኮች  ባዋቀርኩኝ
በስልጣኔ ልናኝ  ምናለ ብትተውኝ

በተለመነ  ብር  በተሻረ ብድር
ባሳተምኩትም ብር  ባቆሙኩት መደብር
በለጋሶች ግብር    እያላችሁ እርር

ድርሽ እንዳትሉ ወዲያ ተገለሉ
ከእኔ አትታገሉ  እርስበርስ ተባሉ

ብፈልግ አስሬ   ካልሆነም አሳስሬ
ጉድጓድም ቆፍሬ  ግፋም ቢል ቀብሬ
መንበሬን አኑሬ   እራሴን ቀብርሬ

እናንተን በምርጫ   በሀሰት ፍጥጫ
ባይሆን በሀሳብ መስጫ  ከሆነልኝ መቅጫ
አዳሜ ቢንጫጫ በሸኔ ቁንጥጫ
አሳጥቼ መውጫ  መግቢያና መሄጃ

ሁልሽን ማሳጫ   ሕግን አስተርጉሜ
ለሀገር ሁላ አዳሜ   በፍፁም ገግሜ
ስልጣኔን አርዝሜ

ዘወትር እንድወደስ  እንድባልም ንጉሥ
ሰባተኛው ፈረስ   አባ ሻንቆን ትቼ
አባዳምጠው ትቼ   አባ ጠቅል  ትቼ
አባ በዝብዝ ትቼ   አባ ታጠቅ ትቼ
አባ ዳኘው ትቼ
ይኸው ሰጠሗችሁ   ብልፅግና አምጥቼ
ቼ በሉ ፈረሴን ቼ!

Filed in: Amharic