>

"በዚህ ሰው ላይ በሀሰት የመሰከራችሁ - ህሊና ባይኖራችሁ እንኳን ፀፀቱ እድሜ ዘመናችሁን ይከተላችኋል…!!!" (ጌታቸው ሽፈራው)

“በዚህ ሰው ላይ በሀሰት የመሰከራችሁ – ህሊና ባይኖራችሁ እንኳን ፀፀቱ እድሜ ዘመናችሁን ይከተላችኋል…!!!”
ጌታቸው ሽፈራው

እስክንድር ነጋ ላይ በሀሰት የመሰከሩ ሰዎች እድሜ ዘመናቸውን ሲሸማቀቁ ይኖራሉ። ምንም ሕሊና ቢስ ቢሆኑ እስክንድር ላይ በሀሰት መመስከር ግን እረፍት አይሰጣቸውም። ከዚህ ቀደም በሀሰት የመሰከሩበትም እንደተሸማቀቁ ናቸው!
እስክንድር ነጋ ማንም ለሚያጨማልቀው የኢትዮጵያ ፖለቲካ የማይገባ ሰው ነው። እስክንድር ጨካኙ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ መገኘት የሌለበት እውነተኛ ሰው ነው። እስክንድር ሰብአዊ ሰው ነው። ከልክ በላይ የመርህ ሰው ነው። ሲበዛ ኃይማኖተኛ ነው። ታናሾቹን እንደ ታላቅ የሚያከብር ገራሚ ሰው ነው። እስክንድር ከሰላማዊ መንገድ ውጭ ሌላ የማይታየው የሰላማዊ ትግል ቄስ ነው። እስክንድር ሕዝብን የሚያከብር ለራሱ የተለየ ክብር የማይፈልግ ሰው ነው።
 እስክንድርን የሚወዱትና የሚያከብሩት ሰዎች ይኖራሉ። ግን እስክንድር ስለታሰረ፣ ስለሚቃወም ብቻ ጀግና ተብሎ የሚወደድ ሰው አይደለም። የእስክንድር ሰብአዊነቱ፣ መርሁ፣ እምነቱ ከፍ ያለ ነው። በርቀት የሚወደው፣ የሚያከብረው ሰው በቅርበት ቢያየው የበለጠ ይገረምበታል።
እስክንድር ለጠላቶቹ ሳይቀር የሚራራ የእግዜር ሰው ነው። እስክንድር መንገድ ላይ ሲያልፍ ሲታይ እንኳን ለአልፎ ሂያጅ ክብር የሚሰጥ፣ መንገደኛን እንደሚያውቀው ሰው ቆሞ በክብር አሳልፎ፣ የሚሄድ በቀናነቱ የሚቀናበት ሰው ነው።  እስክንድር በስክነቱ የሚያስቀና ሰው ነው። እስክንድር በትህትናውና በመርሁ እንደሱ በሆንኩ የሚያስብል ሰው ነው።  በዚህ ሰላማዊ፣ ቀናኢ፣ ሰብአዊ ሰው ላይ በሀሰት የመሰከሩ እድሜ ዘመናቸውን እረፍት አያገኙም።
እስክንድር በሀሰት መሰከሩበት፣ አሰሩት የማይረበሽ፣ ሰላማዊነቱ እረፍት የሚሰጠው ሰው ነው።
የሀሰት መስካሪዎቹ ብቻ ሳይሆኑ እስክንድርን የሚያክል ቀናኢ፣ ሰብአዊ፣ እጅግ ሰው አክባሪ፣ የእግዚያብሔር ሰው ወደ ፖለቲካ የገባባት ኢትዮጵያም ታሳዝነኛለች። ሰው ሁሉ ሲሸሽ፣ ሰው ሲጠፋ ለዚህ ክፉ ፖለቲካ የማይሆነው፣ ጭቃ መራጨት ለበዛበት፣ የክፉዎች መነሃሪያ ውስጥ እስክንድር መገኘት አልነበረበትም። ሕሊናው ዝም ማለትን ስለማይፈቅድለት ብቻ ገባ። ለእሱ ሞራል ልዕልና የማይመጥን ፖለቲካ ውስጥ መግባቱ ራሱ አሳዛኝ ነው። ይህ አልበቃ ብሎ በሀሰት ምስክር ክፋታቸውን አበዙበት! እሱ ግን አይጠላቸውም “እግዜር ይቅር ይበላችሁ” ይላቸዋል። የእምነት አባቶች  ነን ከሚሉት መካከል እንደ እስክንድር ቢበደሉ እንደዚህ የእግዜር ሰውነታቸው ተገልጦ አይታይም። ሊበሳጩም፣ ሊራገሙም ወዘተ ይችሉ ነበር። እስክንድር ግን ልዩ ነው!
በእስክንድር ላይ በሀሰት የመሰከራችሁ መከራችሁ!  ህሊና ባይኖራችሁ እንኳን ፀፀቱ እድሜ ዘመናችሁን ይከተላችኋል። ይፀፅታችኋል። በዚህ ንፁህ ሰው ላይ በሀሰት መመስከር ለዘላለሙ ያሰቃያችኋል።
Filed in: Amharic