>

ተቆርጦ የቀረው ....!!! (በእውቀቱ ስዩም)

ተቆርጦ የቀረው ….!!!

(በእውቀቱ ስዩም)

በየነ  ባልንጀራየ ነው፤ ጦርነቱ ሲጀመር “በዩማ ቲዩብ “ የሚል የዩቲዩብ አካውንት ከፍቶ መሸቀል ጀመረ፤ አንዳንዴ የድል ዜና ሲጠርርበት ሰለ አድዋ ወይም ስለዶጋሊ ድል በመተረክ ፕሮግራሙን  ይሞላዋል፤ አንዳንዴ  የኔን ግጥም ሳይቀር  ከፌስቡኬ ላይ ወስዶ ይዶልበታል፤ ሳንቲም ማካፈሉ ይቅር ፤  ክሬዲት እንኳ  ሊሰጠኝ አልፈለገም::
አንድ ቀን ንድድ ብሎኝ ፤
“ለምንድነው ግጥሜን አንብበህ ስሜን የዘለልከው? ”ብየ ጠየኩት::
 “  ለደህነነትህ ስለማስብ ነው”  አለኝ ኮሰተር ብሎ::
“ስለፍቅር በጻፍኩት ግጥም  ምን አይነት የደህንነት ችግር ሊገጥመኝ ይችላል?
“ህዝብ በየግንባሩ   እየተዋደቀ  ስለፎንቃ መፈላሰፍህ ያናደደው አንዱ ደብድቦ ሊገልህ ይችላል! ጊዜውን መምሰል ያልቻለ እድሜው ያጥራል”
“ ጊዜውን መምሰል ያልቻለ እድሜው ያጥራል “ የሚለው የማን ጥቅስ ነው ?”  አልኩት፤
“ የኔው ነው!  የተልባ ማሻው ሚካኤል ነው ያቀበለኝ”
ትናንት በየነ ቤቱ ምሳ ጋበዘኝ፤ በጨዋታችን መሀል  አማርኛው   እንዴት እንደ ተለወጠ ታዘብሁ::
ስንበላ “  ባይሆን ከጎረድጎረዱ ቅመስ ! ይሄ አደገኛ ትርክት የመሰለ ፊትህ የማይወዛው ስጋ ስለማትበላ ነው “  አለኝ፤
 በየጉርሻው  ጣልቃ  “  ብላ እንጂ ፤ ሆድና ግንባር አይሸሸግም” እያለ ይጎተጉተኛል፤
“ ቆይ! ግንባር የሚል ቃል ሳትጨምር ማውራት  አትችልም?” አልሁት ::
“ በገዛ ቤቴ የፈለገኝን ማውራት መብቴ መሰለኝ  ፤  ሁለተኛ ልታርመኝ ብትሞክር  በዚህ ጠርሙስ ነው  ግንባርህን የምተረክከው  ! ግንብአራም !”
ማእዱ ከተነሳ በሁዋላ፤
“ከእምብርቴ በታች  ውጥረት ነግሷል  “ ብሎ ወደ መጸጃ ቤት ሄደ::
ከተመለሰ በሁዋላ ብዙ ተቀምጦ አልቆየም::
“አሁንም ሽንት ቤት ልቴድ ባልሆነ” አልሁት፤
“ አዎ! ተቆርጦ የቀረውን አራግፌ እመለሳለሁ”
Filed in: Amharic