>
5:13 pm - Friday April 20, 2068

“የጀግኖቻችን፣ የእሸቴዎችን አደራ በፍፁም አንረሳም!!!”፦ ( ዶ/ር ይልቃል ከፋለ  የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር)

የጀግኖቻችን፣ የእሸቴዎችን አደራ በፍፁም አንረሳም!!!”
 ዶ/ር ይልቃል ከፋለ 
የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር
 
*…. የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር ይልቃል ከፋለ “የጀግኖቻችን፣ የእሸቴዎችን አደራ በፍፁም አንረሳም” ሲሉ እሸቴ ሞገስ ከበኩር ልጁ ይታገስ እሸቴ ጋር ሆኖ ለሕዝቡና ለአገሩ የከፈለው መስዋዕትነት የክልሉ መንግስት እንደማይረሳው አስታወቁ። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር ይልቃል ከፋለ ያስተላለፉት መልእክት ሙሉ ቃል እንደሚከተው ይቀርባል፦
 
የእሸቴዎችን አደራ ተቀብለናል!
የአሸባሪው ህወሓት ኃይል ክልላችንን ሲወር ክልላችን መቀበሪያው እንዲሆን ያደረጉት ጀግኖች እልፍ አእላፍ ናቸው። በርካታ ጀግኖቻችን ከጠላት ጋር ተናንቀው ጀብዱ ሰርተዋል። ውድና ክብር መስዋዕትነት ከፍለዋል።
ከእነዚህ አንዱ ለሕዝብና ለአገር ክብር ሲል ሞትን ንቆ ፊት ለፊት ገጥሞ ከእነ ልጁ በጀግንነት የክብር መስዋዕትነት የከፈለው የሸዋው እሸቴ ሞገስ አንዱ ነው።
እሸቴ ሞገስ ከበኩር ልጁ ይታገስ እሸቴ ጋር ሆኖ ለሕዝቡና ለአገሩ የከፈለው መስዋዕትነት፣ የሰራው ጀብዱ ብዙ ያስተምረናል። እሸቴ ሞገስ አልሸሽም ብሎ ከልጁ ጋር በርካታ ጠላትን ጥሎ በጀግንነት አልፏል።
እሸቴ ሞገስ በጀግንነት ሲዋጋ የወደቀው ልጁ አስከሬን ጥግ ሆኖ ሲዋጋ እሱም በክብር እንደሚሰዋ እርግጠኛ ሆኖ፣ እያለቀሰ ሳይሆን ለወገን የአርበኝነት ስንቅ በሚሆን አልበገርባይነት ነው።
እሸቴ ሞገስ በጀግንነት ሲፋለም መስዋዕት እንደሚሆን እርግጠኛ ሆኖ ለመንግስት ቤተሰቦቸን አደራ ብሏል። በርካቶች እንደ እሸቴ ሞገስ የክብር መስዋዕትነት ከፍለዋል። በየአካባቢው አስገራሚ አርበኝነት የፈፀሙ በርካታ እሸቴዎች እንዳሉን እሙን ነው። ወደፊትም ይኖራሉ።
እኛም የጀግኖቻችን፣ የእሸቴዎችን አደራ በፍፁም አንረሳም። የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በዚህ የሕልውና ዘመቻ እንደ እሸቴ ሞገስ ለህልውናቸው፣ ለሕዝብና ለአገራቸው ክብር መስዋዕትነት የከፈሉ ጀግኖችን ቤተሰቦች በመንከባከብና በማገዝ አደራውን ይቀበላል።
ለጀግናው እሸቴ ሞገስ ቤተሰቦች ስለ መፅናናት አንነግራቸውም! ሌሎችም በክብር ሲወድቁ ስለመፅናናት አናነሳም።
እነ እሸቴ ሞገስ የልጅን ትኩስ አስከሬን ጥግ ሆኖ በሀዘን ሳይሆን በጀግንነት መፋለምን አስተምረውናል! ሲወርድ ሲዋረድ ስንዘክረው የኖርነውን የአባቶቻችን አርበኝነት በዘመናችን አሳይተውናል።
ለሕዝባችንና ለአገራችን እስከመጨረሻው መስዋዕትነት እንድንፋለም የሰጡንን አደራ ተቀብለን ለሕልውናችን እስከመጨረሻው መስዋዕትነት እንታገላለን።
ክብር በመስዋዕትነታቸው ሕዝብና አገራቸውን ለጠበቁ ጀግኖች ይሁን!
Filed in: Amharic