>

ለውጥ ሳይኖር ተቀለበሰ ማለት የለውጥን ትርጉም አለማወቅ ነው! (አገሬ አዲስ)

ለውጥ ሳይኖር ተቀለበሰ ማለት የለውጥን ትርጉም አለማወቅ ነው!

                                                  

አገሬ አዲስ


ለውጥ ማለት የአንድ ቁሳዊ አካል በጊዜ ሂደት በውስጣዊና ውጫዊ ጫና ምክንያት በመልክና በይዘቱ ወይም በጸባዩ ላይ ከቀድሞው የተለዬ ሆኖ ሲገኝ ነው።ለውጥ በቁሳዊ አካል ብቻ ሳይሆን በማህበረሰብ  ላይም  የዕውቀት(ንቃተሕሊና) እድገት ደረጃ  ምክንያት አመለካከቱና የኑሮ ዘይቤው ይለወጣል። ያንን እድገት ተከትሎ፣በጥቅሉ የማህበረሰብ ግንኙነት፣የኤኮኖሚውና የፖለቲካው አቅጣጫና ጉዞ የመለውጥ ግዴታ ውስጥ ይገባል። የማህበረሰብ ግንኙነት፣ የሥራ ባህሉና ያኗኗር ዘይቤው፣በአገር  ደረጃ የሚከሰተው ለውጥ የእድገቱ ነጸብራቅ ነው።ለውጥ አንድ ቦታ ላይ ብቻ ተወስኖና ተቸክሎ  ወይም በግማሽ መንገድ ላይ የሚቆም ሳይሆን፣ በሂደት የሚናጥ አሮጌው በአዲሱ እዬተተካ የሚጓዝበት  ተፈጥሯዊ ሕግ የሚከተል ሂደት ና ውጤት ነው። በሁሉም አቅጣጫ ከነበረው የተለዬ ሲሆን ለውጥ መጣ ይባላል።ለውጥ ሙሉነት  እንጂ ግማሽነት የለውም።የሰው ልጅ ሰው የሚባለው ከጽንስ እስከውልደት ድረስ ያለውን የተፈጥሮ ጉዞ ወይም ሂደት ሲያጠናቅቅና ሕጻን ሆኖ ሲወለድ ነው።እንቁላልም  ውስጣዊ እንቅስቃሴውን  ተከትሎ በጊዜ ሂደት ጫጩት ከዚያም ዶሮ ሲሆን እምርታዊ ወይም መሠረታዊ ለውጥ አመጣ ተብሎ ይቆጠራል።ለውጥ ሥር ነቀል ነው የሚባለውም ከነበረበት ደረጃ፣ከነበረው መልክና ይዘት የተለዬ ሆኖ በመገኘቱ ነው።  

የለውጥን ሂደትና ምንነት በማህበረሰብ ወይም በአገር ደረጃ ብናዬው የሚከተለውን ይመስላል።

በአገራዊ ፖለቲካ ወይም የማህበረሰብ ኑሮ በኩልም ለውጥ ብዙ መልኮች አሉት።ከአንዱ የሕብረተሰብ ደረጃ ወደ ሌላው ለመሻገር የሚያስችለውን ሁኔታ ካሟላ ወደተለዬ ማህበረሰባዊ ኑሮና አመለካከት ይሸጋገራል። ለዚያ ደግሞ የህብረተሰቡ ዕውቀት ደረጃ ወይም ንቃተ -ሕሊና ወሳኝ ይሆናል።የነቃ ሕዝብ ለተሻለ ኑሮ ይታገላል እንጂ በነበረው እረክቶ ለመቀመጥ ሕሊናው አይፈቅድለትም።ለዚያም ነው ሕይወት የተከተረ ውሃ አይደለም የሚባለው።ምን ጊዜም ቢሆን ለአዲስ ግኝትና ውጤት ጉጉት አለበት።የሕዝብ ቁጥር በጨመረ ቁጥር ፍላጎቱ እዬጨመረ ይሄዳል።ፍላጎቱ በጨመረ ቁጥር ደግሞ የሚሟላበትን መንገድ ይሻል።የሕዝቡን ጥያቄና ፍላጎት የማያሟላ የኤኮኖሚ እድገት ከሌለ፣ያንንም የሚመራና መልክ የሚያሲዝ መመሪያ  (ፖሊሲ) የሚቀርጽ ብቃት ያለው  የፖለቲካ ሃይል ማለትም መንግሥት ከሌለ ህብረተሰቡ ሌላ ስርዓት እንዲመጣ ትግል ውስጥ ለመግባት ይገደዳል። በትግሉ የሥርዓት ለውጥ መጥቶ የሚሻውን ካላገኘ፣ በግለሰቦች መለዋወጥ ብቻ ከተወሰነ  ለውጥ መጣ ተብሎ ሊቆጠር አይገባም። የመጣው ለውጥ ሳይሆን ተመሳሳይ የፖለቲካ አስተሳሰብ ያላቸው  ፖለቲከኞች፣የሹም ሽረት ወይም የወንበር ክፍፍል ያደረጉበት ሂደት  ሆኖ ይቀራል። ይህንን እንደ አጠቃላይ ግንዛቤ ወስደን ወደ አገራችን ወደ ኢትዮጵያ ስንመለስ:- 

ባለፉት ሃምሳ ዓመታት የኢትዮጵያ ሕዝብ ከደረሰበት የንቃት አኳያ  ባደረገው ትግል ሦስት ሥርዓቶች እንዲቀያዬሩ አድርጓል።የሚፈልገውን ስላላገኘ፣የተሻለ ሥርዓትም ስላልሰፈነ የለውጥ ባለቤት ሊሆን አልቻለም።ለውጥም አልነበረም።ሆኖም ግን ምንም እንኳን የሚፈልገውን ባያገኝም፣ኑሮው ከእሳት ወደ እረመጡ ቢሆንበትም በፖለቲካው መስክ የተለያዩ ሃይሎችን ለማስተናገድ ችሏል። 

ዘውዳዊ ሥርዓቱን ጥሎ የሚፈልገውን ለውጥ ሳያገኝ ትግሉን ተቀምቶ በምትኩ ወታደራዊ አምባገነን መንግሥት ለ17 ዓመታት ተተክሎበታል።ወታደራዊ አምባ ገነኑን ሲታገል ኖሮ  የሚፈልገውን ሳያገኝ ትግሉ ተጠልፎ ላለፉት 30 ዓመታት  የጎሰኞች ስብስብ የሆነ ቡድን የሚቆጣጠረው ስርዓት ተዘርግቶበታል።እነዚህ  ሶስት ስርዓቶች ለሕዝቡ መሠረታዊ ወይም ሥር ነቀል ለውጦች ያመጡ ሳይሆኑ የገዥዎች መለዋወጥ የተከናወነባቸው ናቸው።ስማቸው ቢለያይም ግብራቸው ተመሳሳይ ነው።የሕዝቡ ኑሮ አልተሻሻለም፣ሰብአዊ መብቱ አልተከበረም፣የሚጠይቀው የዴሞክራሲ ጥያቄዎቹ አልተመለሱም፣በሕዝቡ ፍላጎትና ምርጫ ሥልጣኑን የተረከቡ ሳይሆኑ በጉልበት የተጫኑበት አምባ ገነኖች ናቸው።ስለሆነም  ለውጥ አልነበረም ማለት ይቻላል።

የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሚፈልገው ለውጥ ያላሰለሰ ትግል በማድረግ ብዙ መስዋእትነት ከፍሏል፤አሁንም እዬከፈለ ነው።ሥርዓቶች የሕዝብ ጥያቄ መመለስ ሲያቅታቸውና ጉልበታቸው ሲደክም፤አለያም የሕዝቡ ትግል ሲያስጨንቃቸውና ለመውደቅ ሲቃረቡ በውስጣቸው ሽኩቻና ብጥብጥ ይፈጠራል።ያ ብጥብጥና ሽኩቻ እያደገ ሲሄድ ዕድለኞች ከሆኑ አንዱ ሌላውን በማሶገድ የሕዝቡን ስነ ልቦና በመስለብ ደጋፊ በመፍጠር ጊዜያዊ እረፍት ያገኛሉ።አገራችንም ውስጥ ከአራት ዓመት በፊት የሆነው ይኸው ነው።

የወያኔ ጭካኔ፣ሌብነት፣ዘረኝነት፣ጸረ አንድነት፣ጸረ ኢትዮጵያ የሆነ አቋም ያስመረረው ሕዝብ ከዳር እስከዳር ተነስቶ መንበረ ሥልጣኑን በነቀነቀበት ወቅት የዚያው ሥርዓት አካልና አባል ፣የወንጀሉ ሁሉ ተጠያቂዎች የሆኑ ጮሌዎች የሕዝቡን ጩኸት ቀምተው የለውጥ ሃዋርያ ነን ብለው ብቅ አሉ።

የሕዝቡ አለመደራጀትና መሪ አልባ መሆን ለነዚህ አጭበርባሪ ጎሰኞች የተረኛነት ዕድሉን ሰጣቸው።በነበረው ሕገ መንግሥት፣በወያኔ የጎሰኝነት አስተሳሰብ፣በተዘረጋው አገራዊ የክልል አወቃቀር—ወዘተ እዬተመሩና እዬመሩ ምንም አይነት ለውጥ ሳይኖር የለውጥ ሃይል ነን ማለት ጀመሩ፤ሕዝቡም የለውጥ ሃይሎች ፣መሪውንም  ሙሴ እያለ  አጨብጭቦ ተቀበላቸው።እስከ አሁንም ድረስ አብዛኛው ለውጥ እንደነበረ አሁን ግን ለውጡ እዬተቀለበሰ ነው የሚል የጅል ጩዃትና አቤቱታ እያሰማ ይገኛል።የፖለቲካ ፓርቲም ነን የሚሉት ሳይቀሩ ለውጡ ተቀለበሰ እያሉ ሙሾ በማውረድ ላይ ናቸው። ለመሆኑ ምን አይነት ለውጥ መጣ?ምንስ ተቀዬረ?በወያኔ ኢሕአዴግና በኦነግ መራሹ በኦሕዴድ ብልጽግና መካከል ያለው ልዩነትና  ለውጥ ምንድን ነው?በድርጅትና በመሪ መለዋወጥ ሕዝቡ የሚፈልገው መሰረታዊ ለውጥ መጣ ማለት  ነወይ?ለነዚህ ወሳኝ ጥያቄዎች ግን አጥጋቢ መልስ የሚሰጥ አልተገኘም።ሁሉም ለውጡ ተቀለበሰ በሚለው መዝሙር የደነቆረ ይመስላል።ወይም የለውጥ ትርጉሙ የገባው አይመስልም። ለውጥ ነበር ግን ተቀለበሰ ብሎ የሚያምነው አድርባይነት ወይም ንቃተ ሕሊናው የለውጥን ትርጉም ለማወቅ አልፈቀደለትም ብቻ  ነው።በእኔ በኩል ገና ከጅምሩ ሽር ጉዱን ስከታተል፣የመፈነጋገሉን ሂደት ሳጤን፣ ለውጥ የለም፣የግለሰቦች መቀያዬር፣የጎሳ መተካካት ነው በማለት አቋሜን ገልጫለሁ።ከምቀርባቸውም ሰዎች ጋር ተፋጭቻለሁ።ከጊዜ በዃላ ግን ሲገለጽላቸው ይቅርታ የጠዬቁኝም አልጠፉም።  ከሦስት ዓመት በፊት የኢትዮጵያ ክፍላተሃገር ህብረትን ወክዬ አዲስ አበባ በየስብሰባው አዳራሽ ሳልፈራ ይህንኑ  በግልጽ ስናገር ነበር።በአገር አቀፍ ደረጃ የተደራጁትንም ከሃያ የማያንሱ የፖለቲካ ድርጅቶች በራስ ሆቴል አዳራሽ  ሰብስቤ ይህንኑ በመግለጽ አገራችን አሁን ላለችበት አደጋ ሳትጋለጥ መፍትሔ በሕብረት  ፈልጉለት፣አለበለዚያ የጎሰኞቹ ቡድን ሁሉንም ተቆጣጥሮ  አገራችንና ሕዝቡ እናንንተም ጭምር  ለመከራና ለችግር ይዳርጋችዃል በማለት ፤አስተባብሪ ኮሚቴም ተቋቁሞ ነበር፤ ግን ሥራውን ሳይጀምረው ተበተነ። ብዙ ጊዜም በተለያዩ ጽሑፎች ስገልጽ ነበር አሁንም  ለውጥ እንደሌለ ፣ያልነበረ ለውጥም እንዳልተቀለበሰ ሽንጤን ገትሬ ተናግሬአለሁ፣አሁንም እናገራለሁ ግን ምን ይደረጋል አልሰምቶም! ሆነ እንጂ። አሁን ላይ አንዳንድ የፖለቲካ ድርጅቶችም ዓይናቸውን በመግለጽ ወይም የሕዝቡን ቁጣና ጩኸት በመፍራት የለውጥ ሃይል ነው ብለው ሲደግፉት በቆዩት ድርጅት ላይ ጣታቸውን ቀስረው ፣”ለውጡ ተቀልብሷል!” በማለት ላይ ናቸው። 

 ከልባቸው ከሆነ ቢዘገይም እዚህ ላይ መድረሳቸው መልካም ነው።አይተነው ጊዜ ወደሚያዋጣው ከሚል ጅዋጅዌ ጨዋታ የራቀ ከሆነም  በርቱ ሊባሉ ይገባል።ለመሠረታዊ ለውጥ እንዲታገሉና እንዲያታግሉ ድፍረትና ቆራጥነት አይለያችሁ እላቸዋለሁ። አነሳሳቸው ለይስሙላ ሆይ ሆይ ብሎ ለመቆም ከሆነ ለትዝብት ይዳርጋቸዋል።እያታለሉ የሚኖሩበት ጊዜ አለመሆኑን ሊያውቁት ይገባል። 

መታወቅ ያለበት ችግሩ በአንድ ነጠላ ድርጅት ወይም ቡድን የሚፈታ ስላልሆነ ለውጥ ፈላጊው ሃይል በጋራ ተሰባስቦ የጋራ አመራር ፈጥሮ መታገል ይኖርበታል።ያለፈውም የውድቀታችን ታሪክ የሚያስተምረን ይህንኑ ነው።

ብልጽግና ተብዬው የወያኔ ምልምል ድርጅት ከመለመለው የወያኔ ቡድን ጋር በሚያስማማው ጸረ ኢትዮጵያ አቋሙ በመነሳት ተደራድሮ የጎሳ ሥርዓቱን ለማስቀጠል በመነጋገር ላይ  ባለበት ወቅት ሰለባ የሆነው ሕዝባዊ ጎራ ለምን መቀራረብ እንዳልቻለ፣በተደጋጋሚ ከሚገባበት የእርስ በርስ ንትርክ፣ መጠላለፍ፣ብሎም አለመተማመን፣መናናቅና  እራስ ወዳድነት አዘቅት ለመውጣት ለምን እንደማይፈልግ ሲያስቡት እንቆቅልሽ ነው። በመካከሉ ያለውን ጥቃቅን ችግር መፍታት ያልቻለ ፣በጥቅም የሚገዛ እርምጥምጥ የፖለቲካ ድርጅት ግዙፉን አገራዊ ችግር ይፈታል ብሎ መጠበቅ የዋህነት ነው።ስለሆነም የሕዝቡን ድጋፍና እምነት ለማግኘት ለድልም ለመብቃት ያለው አንዱና ዋናው መንገድ ድክመቱን አሶግዶ ፣ተባብሮ የጋራ አመራር ፈጥሮ መታገል ነው።አለበለዚያ ግን  በያዙት የጎሰኞች ስርዓት ውስጥ በሚነሳ ውዝግብ ለውጥ ይመጣል ብሎ ማሰብና መጠበቅ  ጨቋኝ ጥሎ ጨቋኝ መሸከም፣ከጭፍን ጎሰኛ አምባ ገነን ሥርዓት ወደ ጭፍን ጎሰኛ  አምባ ገነን ሥርዓት ሲገላበጡ መኖር ይሆናል።ለውጥ ሳይመጣና የሚፈልጉትን ሳያገኙ ሲዳክሩ መኖር ማለት ነው።

ያለፉትን ሥርዓቶች መተካካት በተመለከተ በዶር ቴድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ግጥም ጽሑፌን ልደምድም

ባስራ ሁለት መርፌ የተሰፋች ቁምጣ፣

አዲስ ንጉሥ እንጂ ለውጥ መቼ መጣ።

አዎ ለውጥ አልመጣም፤ሃቻምናም፣አምናም ሆነ ዘንድሮ ያው በገሌ ነው።በአምባ ገነኖች ክርን ሲደቆሱ መኖር ነው።ያለፈውን አራት ዓመት የከፋ የሚያደርገው ደግሞ የጭፍን ኦነጋውያን ሥርዓት መሆኑ ነው።ከሳት ወደ እረመጥ ይሏል ይህ ነው።

ለውጡ ተቀለበሰ የሚሉ ሰዎች ለውጥ ማለት ምንድን ነው?ከመቀያየርስ በምን ይለያል?በእንግሊዝኛው what is the difference between  Change and Transform የሚለውን አንስተው እንዲመረምሩት በአክብሮት ልጠይቃቸው እወዳለሁ።

ለእውነተኛ ሥር ነቀል ለውጥ እንነሳ፤የምናጣው  ነገር ቢኖር የታሰርንበትን የጎሰኞች ሰንሰለትና አገር አልባ መሆንን ነው።   

 

Filed in: Amharic