>

የወንጀል ሥርዓቱ ‹‹የአገርና የሕዝብ ደኅንነት ተቋም›› (ከይኄይስ እውነቱ)

የወንጀል ሥርዓቱ ‹‹የአገርና የሕዝብ ደኅንነት ተቋም››

ከይኄይስ እውነቱ


ኢትዮጵያ አገራችን ላለፉት ሃምሳ ዓመታት የተለያየ ስያሜ ቢሰጠውም በስም ካልሆነ በስተቀር በተግባር የአገርና የሕዝብ ደኅንነት ተቋም አልነበራትም፤ አሁንም የላትም፡፡ ይልቁንም ይህ ተቋም ከደርግ አገዛዝ ዘመን ጀምሮ ለተተከለው የወንጀል/ወሮበሎች ሥርዓት ዋስና ጠበቃ፣ ጠባቂና መከታ፣ ቋሚ ለጓሚና ደንገጡር ሆኖ ሲያገለግል የነበረና አሁንም ያለ የወንጀል ሥርዓቱ ዓይነተኛ መገለጫ የሆነ የማጅራት መቺዎች (criminal gangsters/thugs) ስብስብ ነው፡፡ ባገርና በሕዝብ ደኅንነት ሽፋን የዜጎችን ሕይወት ሲዖል ያደረገ የጭራቆች ቡድን ነው፡፡ መላ ኢትዮጵያን ወኅኒ ቤት ያደረገ፣ ላገርና ለሕዝብ ደኅንነት ሥጋት በሆኑ ኃይሎች ሳይሆን በራሱ ዜጎች ላይ የስቃይን ጥግ የሚፈጽም የሽብርተኞች መንጋ ነው፡፡ 

ዛሬ በኢትዮጵያ መንበረ መንግሥት ላይ በጉልበታቸው ተሰይመው አገርና ሕዝብን ለማጥፋት መንግሥታዊ ሽብር እየፈጸሙ ያሉ ግለሰቦችና ቡድኖች የዚሁ ማጅራት መቺ ቡድን አባላት የነበሩ ናቸው፡፡ ሥልጣንና በሥልጣን የሚገኘውን ጉልበትና ሀብት ሁሉ ተጠቅመው በራሳቸው ክፋትና ለታሪካዊ የውጭ ጠላቶች በቅጥረኝነት በማደር በሙሉ ኃይላቸው ኢትዮጵያን የምታህል ጥንታዊት፣ ታሪካዊትና ነፃ አገር እንዲሁም ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለውን ኩሩ፣ የታፈረና አገር ወዳድ ሕዝብ በነገድ/ጐሣ አጥፊ ሥርዓት ከፋፍለው የማጥፋትና የማዋረዱን እኩይ ተግባር ከጀመሩ እነሆ 31 ዓመት ተቈጠረ፡፡ ባለፉት ሠላሳ አንድ ዓመታት በአገር መከላከያና በፖሊስ ሠራዊት ስም ያለው ተቋም ወደድንም ጠላንም የዚህ ማጅራት መቺ ቡድን ዓላማና ተግባር ተጋሪና ቅጥያ ነው፡፡ ባጭሩ በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ የአገርን ሉዐላዊነት እና ዳር ድንበርን የሚያስጠብቅ ብሔራዊ የመከላከያ ኃይል እንዲሁም የሕዝብን ሰላማዊ ኑሮና ደኅንነት የሚያስጠብቅ የፖሊስ ሠራዊት የላትም፡፡ በተቃራኒው እነዚህ ኃይሎች ለአገርና ለሕዝብ ደኅንነት ከፍተኛ ሥጋት ደቅነው ይገኛሉ፡፡ በተለይም ወያኔና ወራሾቹ አማራ ብለው በሰየሙት የአገራችን ክፍልና  በመዲናችን በአዲስ አበባ፡፡ እነዚህ ተረኞች ከወያኔ ትግሬ የሚለዩት ገርባዎች/ገበሮዎች መሆናቸው፤ ፈሪዎችና ጨካኞች መሆናቸው፤ሁሉም የኛ የሚል ገሪባነታቸው፤ ጣራ የነካ ንቀታቸውና ዕድሜአቸውን ለማሳጠር የሚጣደፉበት ጅልነታቸው ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በዓላማ ረገድ አንዳች ልዩነት የላቸውም፡፡ በተለይም ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን እና የነዚህ ዋነኛ መገለጫ ነው ብለው የሚያስቡት የአማራው ሕዝብ ላይ ያላቸውን ጥላቻ በሚመለከት የኋለኞቹ እጅግ ቢብሱ እንጂ ልዩነት የላቸውም፡፡ 

ከደርግ ጀምሮ በትግሬ ወያኔና በኦሕዴድ/ኦነግ ባገራችን ኢትዮጵያ ላይ በጉልበት የሠለጠኑት ነውረኛ ሥርዓቶች የወንጀል ሥርዓቶች መሆናቸው ላይ መተማመን ካለ፤ በነዚህ የወሮበሎች ሥርዓት ስለ ሕግና የሕግ የበላይነት፣ ስለ ‹መንግሥታዊ› አሠራር ግልጽነትና ተጠያቂነት ማውራት ተራ ቧልት/ፌዝ ይሆናል፡፡

የወንጀል ሥርዓት የሆነው የኦሕዴድ/ኦነግ አገዛዝ በቅርቡ ‹‹የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት›› ብሎ የሰየመውን የማጅራት መቺዎች ስብስብ የተቋቋመበት ‹ሕግ› ማሻሻያ ብሎ የጥፋት ተግባሩን የበለጠ የሚያጠናክርበት ሥልጣን ጨምሮለታል፡፡ ለዚህም ጽሑፍ መነሻ የሆነኝ ይኸው ‹የማሻሻያ ረቂቅ› ነው፡፡ ወደ ይዘቱ ለመግባት የዚህ ጽሑፍ ዓላማም ፍላጎትም አይደለም፡፡ የዓዋጁ ረቂቅ ማሻሻያ ማብራሪያ ተብሎ በተዘጋጀው 5 ገጽ ጽሑፍ ውስጥ ኢትዮጵያ የሚለውን ቃል ተጸይፈው እንደ ሟቹ የወያኔ አለቃ ‹አገሪቱ› በማለት ደጋግመው መጠቀማቸው የወሮበሎቹን አገዛዝም ሆነ ለራሱ ማስጠበቂያ የፈጠረውን የማጅራት መቺዎች ‹ተቋም› ማንነት አንድ ማሳያ መሆኑን ታዝቤአለሁ፡፡ 

መልእክቴ ባጭሩ በወንጀል ሥርዓት ውስጥ ስለ ጥሩና መጥፎ፣ አፋኝና ‹ሕገ ወጥ› ሕግ ማውራቱ ፋይዳ የለውም ለማለት ነው፡፡ በወንጀል ሥርዓት ውስጥ ሕግ የጥፋት መሣሪያ ሆኖ ከማገልገል የዘለለ ሚና አይኖረውም፡፡ ዛሬ ዜጎች በነገድ ማንነታቸው ብቻ እንደ አውሬ እየታደኑ በፈጠራ ክስ የሚንገላቱበትና ያለ ፍርድ ወደ ወኅኒ የሚወረወሩበት፣ የሚደበደቡበትና ደብዛቸው ጠፍቶ የሚሰወሩበት ጊዜ ላይ ነው የምንገኝ፡፡  እነዚህ ማጅራት መቺዎች በወያኔም ሆነ በወራሹ የኦሕዴድ አገዛዝ በአማራው ሕዝብ ላይ ዕለት ዕለት የዘር ማጥፋት ወንጀል ሲፈጽሙ፣ የዘር ማጽዳት ተግባር ሲፈጽሙ፣ የጦር ወንጀል ሲፈጽሙ፣ በግፍ ገድለው ለቀብሩ ኩርማን መሬት ሲነፍጉት/እንደ ቆሻሻ ዝቀው ባንድ ጉድጓድ ሲጨምሩት፣ ባጠቃላይ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ሲፈጽሙ፣ በገፍ ሲያፈናቅሉት፣ በቀጠና ሲያሰቃዩት፣ ባቀናው አገሩ ባይተዋር ሲያደርጉት የእነሱ (የወያኔ/ኦነጎች) ‹ሕገ አራዊት› እንኳን የሚፈቅድ ሆኖ አልነበረም፡፡ እንደዚህ ዓይነቱን የነውረኞች ሥርዓት ዳግም እንዳያቆጠቁጥ ከሥሩ ነቅለን ማስወገድ ይኖርብናል፡፡

የአማራው ማኅበረሰብ ብቻ ሳይሆን አገሩን የሚወድ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በእነዚህ የጥፋት ኃይሎች ላይ ፋኖ ሆኖ መሠማራት ይኖርበታል፡፡ ጊዜው የዘገየ ቢመስልም ሁሉም ከነቃበት ሰዓት ጀምሮ ላገሩና ለወገኑ ፋኖ ሆኖ ይነሣ፡፡ ደጋግሜ ሳይታክተኝ የምጮኸው የአማራው ማኅበረሰብ በተለይ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ባጠቃላይ የቅድሚያ ጠላት ወያኔ ትግሬ ወይም ኦሕዴድ/ኦነግ ሳይሆን የነዚህ ነውረኞች ዘላለማዊ አሽከር የሆነው፣ አማራን ብሎም ኢትዮጵያን ለማጥፋት ወያኔ የፈጠረው ብአዴን የሚባለው የቁም ምውታኖች ስብስብ ነው፡፡ በየትኛውም ኃላፊነት ደረጃ ከወረዳ/ቀበሌ እስከ መጨረሻው ዕርከን ያሉ አመራሮችን (ዝምድናና ጎጥ ሳይቆጥሩ) ያለ ምሕረት ማስወገድ የቅድሚያ ተግባራችን ሊሆን ይገባል፡፡ እሱን ካስወገድን የወያኔና የተረኞቹ ጉዳይ ዕዳው ‹ገብስ› ነው፡፡ ከባድ ጥፋት እያደረሱ መሆኑን ባውቅም ድምጥማጣቸው መጥፋቱ አይቀርም፡፡ ተራ የብአዴን አባል ነኝ የሚለው ነውረኛ፣ ከምድረ ገጽ እንዲጠፋ እያስጨፈጨፈ ባለው ሕዝብ እንዲታመን ከፈለገ (ዕድል ይሰጣቸው የሚሉ ወገኖች ስላሉ እንጂ እኔ በግሌ በነዚህ ጉዶች ላይ አንዳች እምነት የለኝም) ከአባልነቱ በይፋ ወጥቶ ትግሉን ሲቀላቀልና ይቅርታ የሌለው ወንጀል የፈጸመበትን ሕዝብ ለመካሥ ከተነሣ ብቻ ነው፡፡ 

በነገራችን ላይ ለአማራው ማኅበረሰብ ከብአዴን የማይተናነሱ ጠላቶች በስሙ የተደራጁና ከርሳሞች የተሰባሰቡባቸው ድርጅቶች ጭምር ናቸው፡፡ በዋናነት አብን የሚባል ነውረኛ ድርጅት፡፡ አንዳንድ ደኅና ግለሰቦች ውስጡ አሉ በማለት የሚናገሩ እንዳሉ ዐውቃለሁ፡፡ ካሉ ይህን ቆሻሻ ድርጅት ጥለው ይውጡና ፋኖን ይቀላቀሉ፤ በአደረጃጀት ያግዙት፡፡ ሊቋቋም ዳር ዳር ሲል ጀምሮ በዚህ ድርጅት ላይ የነበረኝ አቋም ትክክል መሆኑን ከፍሬው ለማረጋገጥ ችዬአለሁ፡፡ 

አሁን ራሱን ኢዜማ ብሎ የሚጠራው ‹ግንቦት 7› ላይ በመጠኑ ተስፋ አድርጌ ነበር፡፡ ወደ አገር ውስጥ ሳይገባ ኢትዮጵያን ለማፍረስ ከሚሠሩ የጥፋት ኃይሎች ጋር ኅብረት ሲፈጥርና ወደ አገር ውስጥ ከገባም በኋላ አሁን በሥልጣን ላይ ካለው አሸባሪ ቡድን ጋር አንድ አካል አንድ አምሳል ሆኖ ሲሠራና በአማራው ሕዝብ ላይ በወንጀል ሥርዓቱ ለሚፈጸመው ግፍ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ተባባሪ ሆኖ ሳገኘው፣ ይህ ድርጅት ከነ አመራር አባላቱ የኦሕዴድ አሽከርነቱን ያስመሰከረ የሆዳም አድርባዮችና ነውረኞች ስብስብ መሆኑን በሚገባ ተረድቼአለሁ፡፡

ወደ ቀደመ ነገሬ ልመለስና፣ በሕይወት ለመኖር የሚደረግ ትንቅንቅ ላይ ስለ ‹ሰላማዊ ትግል› የሚያወራ ግብዝ ካለ ጆሮ የሚሰጠው የለም፡፡ እዬዬም ሲደላ ነው ይባላል፡፡ ከፍ ብዬ እንደጠቀስሁት አንዳች የመንግሥትነት ባሕርይ የሌለው የወሮበሎች ሥርዓት በአገርና ሕዝብ ደኅንነት፣ በአገር መከላከያና ፖሊስ ሽፋን ሽብርተኞችን እያሰማራ ቀዬው ድረስ መጥቶ የሚገለውን፣ እየጎተተ የሚያስረውንና የሚሰውረውን፣ ከቤት ንብረቱ የሚያፈናቅለውንና የሚያንገላተውን የጥፋት ኃይል ዝም ብሎ ይመልከት የሚል ግለሰብም ሆነ ቡድን ካለ እሱ ከጠላት ወገን ነው፡፡ የወንጀል ሥርዓትን እንኳን ደጃፋችን መጥቶ ያለበት ድረስ ሄደን የገባበት ገብተን ማስወገድ ያገርና የሕዝብን ህልውና ለመታደግ የምናስብ ኢትዮጵያውያን ሁሉ የዜግነት ግዴታችን ነው የሚል ጽኑ እምነት አለኝ፡፡  

በመጨረሻም በውጩ ዓለም የምትገኙ አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን፣ ሕዝባዊው ኃይል/ፋኖ ወያኔና ወራሾቹ ባጠሩለት የጐሣ አጥር ሳይወሰን መላ ኢትዮጵያን እንዲታደግ የምትሹ ከሆነ በስንቅ፣ በትጥቅና ቤተሰቦቹን በመደገፍ አለኝታነታችሁን የምታስመሰክሩበት ጊዜ ዘግይቷል ካልተባለ አሁን ነው፡፡ ከሰላማዊ ሰልፍ የዘለለ ‹ፋኖነታችሁን› ለወገናችሁ በተግባር አሳዩት፡፡

Filed in: Amharic