>

“የሕዝብ ሰው/Public Figure” መሆን አንዳንዴ ሳያሰክር ይቀራል? (ብሥራት ደረሰ)

“የሕዝብ ሰው/Public Figure” መሆን አንዳንዴ ሳያሰክር ይቀራል?

ብሥራት ደረሰ


በስንቱ ተናድጄ እንደምዘልቀው አላውቅም፡፡ ዛሬ ሌሊት ነው፡፡ እንደልማዴ የዩቲዩብ ቻናሎችን ስዳስስ አንዱ ቀበጥ አርቲስት ሚስት ሊያገባ ከአርባ በላይ ሽማግሌዎችን ወደእጮኛው ቤት መላኩን በኩራት የሚገልጽ አንድ የዩቲብ ገጽ ላይ ዐይኔ ዐረፈ፤ ቀልቤንም ሳበውና እከታተለው ጀመር፡፡ ግን አልጨረስኩትም፡፡ የሰዎችን ሥራ ፈትነት ከተገነዘብኩበት በቂ ነው ብዬ ወደ ሌላ አንገብጋቢ ዝግጅት አመራሁ፡፡ የሀገራችን ሁለንተናዊ ዕድገት መቼም የሚያስቀና ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ ይህ አብሻቂ ክስተትም የሚያሳየን ይህንኑ ነው፡፡

በርግጥም ይሄ በሰዎች ዘንድ የመታወቅ ጣጣ ሳያጃጅልና ሳያሰክር አልቀረም፡፡ አሁን ማን ይሙት አንድ ታዋቂም ሆነ አል-ታዋቂ ሰው ሚስት አገባ አላገባ ምን ያህል ሀገራዊና ሕዝባዊ ቁም ነገር ኖሮት ነው እንዲህ ያለ መጃጃል ውስጥ የተገባው? በውነት በዝግጅቱና በአርቲስቱ አፍሬያለሁ፡፡ ነገሩ ባጭሩ “ሳይቸግር ጤፍ ብድር” እንዲሉ ነው፡፡ በሽምግልናው የተካተቱ ሰዎችም ሥራ ፈትነታቸው አሳዝኖኛል፡፡ የቀረ እኮ የለም! ከጳጳስ እስከ ዲያቆን፣ ከሰባኪ እስከ ዘማሪ፣ ከሴት አርቲስት እስከወንድ የቦተሊካ አናሊስት … ምን አለፋችሁ በሽምግልናው ያልታደመና ያልተካተተ አንድም የበቃና የነቃ ብፁዕ ዜጋ የለም – ከፓትርያርኩና ከጠ/ሚው እንዲሁም እስልምናንና ካቶሊክን ከመሰሉ አንዳንድ የሃይማኖት መሪዎች በስተቀር ሁሉም ተካቷል ማለት ይቻላል – ሲያሳዝኑ!! መጋቢ ሀዲስ እሸቱ ራሳቸው አሉበት፡፡ ያልገባኝ ግን ዓላማው ነው፡፡ በዛሬ ጊዜ ባል ተገኝቶ እምቢ ሊባሉ ኖሯል? ሥራ ያጣች መነኩሴ አሉ …

ሀገራችን ጭንቅ ላይ ናት፡፡ ጦርነቱ፣ ርሀቡ፣ ስደትና መፈናቀሉ፤፣ ዘረኝነቱ፣ የኑሮ ውድነቱ፣ እስር እንግልቱ፣ አፈናውና እገታው …. ይህና ሌላው ችግር ወጥሮን ቀኑ በመከራ ነግቶ በመከራ እየመሸ እንዲህ ዓይነት ቅብጠትና የአርቲስቶች መሞላቀቅ በፍጹም ሊገባኝ አልቻለም፡፡ ለካንስ ዜጎች በተለያዬ ምህዋር ውስጥ ነው የምንገኘው!! ለካንስ ተለያይተናል፡፡ ደግሞም አንድኛህ አንባቢ ወይ አድማጭ  “ቀንተህ ነው” በለኝና አስቀኝ አሉ፡፡ ምኑ ነው የሚስያቀናው? የአርቲስቱ ዘግይቶም ቢሆን ማግባት? ለአንዲት “ኮረዳ” ከአርባ በላይ ዕውቅ ዜጎችን ለሽምግልና ልኮ ሥራ ማስፈታት? ይህ ድርጊት ያሳፍራል እንጂ በጭራሽ አያስቀናም፡፡ አእምሮን በትክክል ያለመጠቀም ውጤት ሊያስቀና አይችልም፡፡

ሽምግልና ምን ማለት ነው? እኔ እንደሚገባኝ ሽምግልና ማለት ዓይነቱ ብዙ ቢሆንም ሠርግና ጋብቻን በተመለከተ ግን ወንዱ ለሴቷ ቤተሰቦች ሦስት ሽማግሌዎችን ልኮ “ልጃችሁን ለልጃችን” በሚል ባህላዊ ሥርዓት የቤተሰብን ፈቃድ የሚጠይቅበት ወግ ልማድ ነው፡፡ ሦስት ሰዎች መሆናቸውም ሥላሤዎችን እንደሚወክል ስለሦስት ቁጥር ታሪክ ከተጻፉ መልእክቶች መረዳት አይከብድም፡፡ ገና ለገና ታዋቂ ነኝ ተብሎ፣ ገና ለገና “አገር ምድሩ ስለሚያውቀኝ ታዋቂ ሰዎችን በብዛት ልኬ ታሪክ እሠራለሁ” ከሚል የሞኝ አስተሳሰብ ተነስቶ እስከዚህ መውረድ የጤንነት አይደለም፡፡ ለዚህ ለዚህማ አገር በመከራ ዶፍ እየተመታች በአሁኑ ሰዓት በሌለን ገንዘብ በ50 ቢሊዮን ብር ቤተ መንግሥት ሊሠራ የሚጃጃለው ጠ/ሚኒስትራችን ምን አጠፋ!! በሀገራችን የጋብቻ ታሪክም አርባና ሃምሳ ሽማግሌዎችን ልኮ ቤተሰብን ያስፈቀደ አልሰማሁም፤ የዚህ ችግር ምንጭ የመታወቅና ያለመታወቅ ብቻ ሳይሆን ባህሉን በውል ያለመረዳትም ጭምር ይመስለኛል፡፡ እንጂ እኮ መቶ ሽማግሌም መላክ የሚችሉ ከዚህ አርቲስት የበለጡ ሀብታሞችና ዝነኞች አሉ፡፡ “ኧረ ይሄ ነገር ያስቅብናል፤ ‹አወቅሽ፣አወቅሽ› ቢሏት ‹የባሏን መጽሐፍ አጠበች› ተብሎም ይተረትብናልና ግዴለህም በቅጡ እናድርገው!” የሚል አማካሪስ እንዴት ይጠፋል? እንዴት ሁሉም ተያይዞ የሕጻናት ዕቃቃ ጨዋታ ውስጥ ይገባል? የደላው ሙቅ ያኝካል ነው የሆነብኝ፡፡ ሌላው የገረመኝ ደግሞ ለሽምግልና የተመረጠው ታዳሚ ሁሉ ወግና ልማዱን ዘንግቶ ተግተልትሎ መሄዱ፡፡ አርቲሰቱን ማፍቀር ሌላ፣ ከባህልና ከወግ መጣረስ ሌላ፡፡ ምን ፈረደብን ጎበዝ፡፡ አንድ ሰው እንኳን “ኧረ ይሄ ነገር ከባህላችንና ከትውፊታችን ውጪ ነው” ብሎ እንዴት አልተቃወመም? “እኔ እንዲህ ነኝ፤ ዕወቁኝ” ለማለት ካልሆነ በስተቀር በዚህ የሽምግልና ሂደት አንዳችም ትምህርት አልተላለፈም – ከጉራ በስተቀር፤ “ጉራ ብቻ” አለ ቴዲ አፍሮ – እውነቱን ነው፡፡ ከዚህ ዓይነት ጅልነት ለወደፊቱ ታዋቂ ሰዎቻችን ቢጠነቀቁ ከትዝብት ይድናሉና ይህችን ማስታወሻ ሳያገባኝ እንዲሁ ከተብኩ፡፡ ታዋቂነት ከብልኅነት ጋር ይደመር፤ አለዚያ ትርፉ ኪሣራ ነው፡፡ “በማን ላይ ቆመሽ” እንዲሉ ነውና ሕዝባችሁን አስቡት፡፡ እንደዚህ ዓይነቱ እዩኝ እዩኝ በተለይ በዚህን የመከራ ወቅት ተገቢነት የለውም፡፡ 

ከታዋቂ ሰዎች አንዱ እንግዲህ ወፈፌው ጠ/ሚኒስትራችን መሆኑም አይደል? አዎ፣ ሀገር በችጋርና በችግር እየተጠበሰች የደላው አቢይ የግድግዳ ቀለም በማስቀየር ላይ ነው፡፡ የዕብድ ገላጋዩም በዛና አዲስ አበባ ውስጣዊ ክርፋቷን በግድግዳ ቀለም የደበቁ የሚመስላቸው ኦሮሙማዎች ሌት ተቀን ግድግዳ እየፋቁ ግራጫ ቀለም በመቀባት ላይ ናቸው፡፡ ማወቅ ያለባቸው ግን በውጫዊ የቀለም ለውጥ የውስጥ ግማትንና ቁናስን መከላከል የማይቻል መሆኑን ነው፡፡ ይቺ ሌላ ያቺ ሌላ ብለዋል አለቃ ገ/ሃና፡፡ ወይ ዘመን ሲያረጅ!! የዘመን ጅጅትና አይግጠማችሁ፡፡ ይሄ ዘመንማ አለቅጥ ጃጀ፡፡ እጅግ አስጠሊታም ሆነ፡፡

እንዲህ እንዲህ እያልን እንግዲህ 2015 ዓ.ምን ልንቀበል የዛሬዋን ሰኔ ስድስትን ጨምሮ ልክ ሦስት ወራት ብቻ ቀሩን፡፡ ያኔ ከፍ ሲል ከጠቃቀስኳቸው የግልና የቡድን ጅልነቶችና ማኅበረሰብኣዊ ስካር ዕብደቶች ተገላግለን በጤናማ ሁኔታ እንደምንገናኝ ተስፋ አለኝ፡፡ ያኔ ብዙዎቻችን ወደ አቅላችን ተመልሰን እንደሰው ማሰብ እንደምንጀምር ትልቅ ተስፋ አለኝ፡፡ ያኔ ቁጥራችን ከአሁኑ ሲነጻጸር ዝቅተኛ መሆኑ ቢገመትም ለዚያ ዘመን የምንበቃ ዜጎች እርስ በርስ እየተያየን አንዳችን ለአንዳችን መተሳሰብና መተዛዘን የምንጀምርበት ወቅት እንደሚብት እገምታለሁ፡፡ ያኔ አሁን መቀመቅ የከተተን ዘረኝነትና ጎጠኝነት ተወግዶ በሀገራዊ የጋራ ስሜት እንደምንተሳሰር ተስፋ አለኝ፡፡ ያኔ አሁን የሚያመነቃቅሩን የዲያቢሎስ ልጆች ጥጋቸውን ይዘው በዕውቀትና በጥበብ በሚመሩ መልካም እረኞችና ለነፍሳቸው በሚያድሩ ደጋግ አባቶች እጅ እንደምንገባ አምናለሁ፡፡ ለአርቲስቶቻችንም ልቦና ይስጥልን፤ ከሚያጥበረብርና ልብን ከሚያሳባጥ ዕብሪትም ይሠውርልን፡፡ ፈጣሪ ሀገራችንን በቶሎ ይጎብኝ፡፡ ….

Filed in: Amharic