>

የአፋር ህዝብና የፀረ ኮሎኒያሊዝም ተጋድሎ....!!! "" (እጩ ዶ/ር ሀቢብ መሀመድ እንደጻፈው)፦

የአፋር ህዝብና የፀረ ኮሎኒያሊዝም ተጋድሎ….!!!

“”

(እጩ ዶ/ር ሀቢብ መሀመድ እንደጻፈው)፦

ጥንቅር ሰለሞን ብርሃኑ፦

“”

ግብፅ ኢጣልያ ፈረንሳይ በአፋር በኩል በተደጋጋሚ ሞክረው

አልተሳካላቸውም። በአፋር በኩል ኢትዮጵያን ለማጥቃት የሞከሩ ሁሉ አንዳቸውም አልተሳካላቸውም። በአገራቸው ለመጣ ምንም

አይነት ድርድር አላደረጉም፤ መሸንገያዎችን አልተቀበሉም። ሁሉም ለኪሳራ ተዳርገዋል።

የአፋር ህዝብ የቅኝ ግዛት ገና ከመነሻው እየተቃወመ እየተከላከለ ና እየተጋደለ ለመኖሩ የተፃፈ መዛብቶችን እያገላበጡ፤ እየጠቀሱ

የሚነግሩን አቶ ሃቢብ መሀመድ እንደሚሉት ይህ ደማቅ የፀረ ኮሎኒያሊዚም ተጋድሎ ታሪክ የተደበቀ መሆኑን እያወሱ ነባራዊ ሁኔታውን ከአፋር ተፈጥሯዊ መልከዓ ምድራዊ ገጽታ ጋር

እያነፃፀሩ አብራርተዋል። በ1869 የስዊዝ ካናል መከፈትን ተከትሎ ቅኝ ገዢዎች የአፋር አካባቢዎችን ና ወደቦችን በዕይታቸው ውስጥ እንዲገባ ሆኗል በዚሁም ምክንያት አውሮፓውያን አፋርን ለማሳመን የተለያዩ ምክንያቶችን ይዘው መቅረብ የዘወትር ስራቸው ማድረግ ጀመሩ። እንደሚታወቀው ቅኝ ገዥዎች የተለያዩ የማሳመኛና መደለያ ዘዴዎችን ቢያቀርቡም የአፋር ህዝብ በማንኛውም ጊዜና ሁኔታ ለእነዚህ አካላት የተበገረም፤ የገበረም አልነበረ። ዛሬ እንደ አፋር ግዛት ወይም ምድር የማትቆጠረው ዘይላ ፈረንሳይ ስትገባ በ1875 ውሎችን በመፈራረም እንደሆነ ውሎቹም በሁለት ቋንቋዎች በአረብኛና በፈረንሳይኛ የተዘጋጁ እንደነበሩ አስታውሰው

በዝርዝር አብራርተዋል። በ1869 ኢጣሊያ የከሰል ማንደጃ ቦታ በኪራይ ለአንድ የግል ካንፓኒ ማከራየቱን የገለጡት የታሪክ ምሁሩ በጊዜ ሂደት ይህ ካምፓኒ በመንግስት ይዞታነት ሲቀየር መጀመሪያ ሰፍረውበት ከነበሩት ቦታ ቀስ በቀስ እያስፋፋ እዚያ ያሉ ቦታዎችን መቆጣጠር ቢፈለጉም ኢጣሊያ የአፋርን መሬት መያዝ ዓላማ እንደሌላቸው መግለጣቸውን እያጣቀሱ ይገልጣሉ፤ በ1885 በጊዜው ለነበረው ለቀይ ባህር አዛዡ እንደ ቀኝ ግዛት እንዳይቆጠሩ ማሳሰባቸውን ተናግረዋል።

ይህ የቅኝ ገዡዎች የማባበያ ስሌት የተለመደ መሆኑ አውስተው ከሱልጣን መሀመድ ሃንፈሬ ጋር የተደረገውን ውል በተመለከተ በዘመኑ ገናና የነበረው የአፋር ባለቅኔ ቶላ ሀንፍሬ እንዲህ ብሎ መናገሩን አስታውሰዋል፡፡ ለውጭ ሃገር ሰዎች ራስህን ማሳወቁ ጥሩ አይደለም ማንነትህን ካወቁ ሊያጠቁህ ይችላሉ ….እንዲህ እያለ ምክሩን የለገሰው ቶላ ሃንፈሬ እስካሁን ድረስ የቅኝ ገዢዎችን እሳቤ ቀድሞ ያወቀ ነበር ማለት ይቻላል።

የተፈራው አልቀረም ሂደቱ ቀስ በቀስ እየፈካ መጋረጃው እየተገለጠ ሲመጣ ገና ከመነሻው ነገሩ ያላማራቸው የአፋር ባላባቶች የቅኝ ገዢዎች ሴራ በማጋለጥ በይፋ መቃወማቸውን ጀመሩ፡፡

እንደ ምሳሌ ለማንሳት ያህል በገጠራማው የኤርትራ አካባቢ ኗሪዎች ላይ ቀረጥ መጣል ሲጀመር የራኸይታ ሱልጣን በግልጽ ተቃወመ፤ ይህን ተከትሎ ጦርነት መቀስቀሱ ፤ በዚህም

ምክንያት ሱልጣኑን ጨምሮ ጎሳ መሪዎች ቀረጥ እንደማይከፍሉ ለጣሊያኖች ነገሯቸው፡፡

የኋላውን የአፋር የተጋድሎ ታሪክ መረዳት ያልፈለገው ቅኝ ገዢው ኢጣሊያ ለማስገበር የሃይል አማራጭን መንገዱ አድርጎ መረጠ፤

በአፀፋው በይፋ የተቃወሙት አፋሮች እስከ ቤተሰባዊ ሃረግ ድረስ ያሉት ተከላክለውት መልሰውታል፡፡ ወደ አፋር ምድር ፊታቸውን ያዞሩት ሁሉ አልተሳካላቸው። ከቅኝ ገዢው ኢጣሊያ ቀድመው የመጡት ቱርክና ግብጽ ኪሳራ አጋጥሟቸዋል፡፡ ሙዚንገር የተባለው የጦር መሪ ከቱርክ ልምድ ወስዶ ቀረጥ ከማስከፈል ና ወደቦችን ከመገንባት ሊቆጠብ ችሏል ፤የአፋር ህዝብና አካባቢው የነፃ ግዛት ባህሪይ እንዳለው ነው ማረጋገጥ የቻለው፡፡በዚህም መሰረት ግብጽ ቀረጥ ማስገበር

ውስጥ መግባት አልቻለችም በራሷ ወደብ ዳርቻ ላይ ብቻ ነው ተገትራ የቀረችው፡፡

አጤ ሚኒሊክ በሁለት ቋንቋ ውል ማድረጋቸው ውሎ አድሮም ችግር መፍጠሩን ያስታወሱት አቶ ሃቢብ በአፋር ምድርም ሌላኛዋን ቅኝ ገዢ ፈረንሳይም በፈረንሳይኛና በአፋረኛ (በነገራችን ላይ ያኔ አፋረኛ ቋንቋ አረብኛ ፊደል ስክሪፕት ) ነበር የሚጠቀመው። የተፃፈው ውል የሚጋጩ ነበሩ፤ ልዩነት ነበረው፤ በዚህም

መሰረት የራኸይቶ ሱልጣን የተደረገው ስምምነት የወዳጅነት እንጂ መሬት የመሸጥ አይደለም ብሎ አፍርሶታል፡፡

በ1890 ፈረንሳይ ተመሳሳይ አቋም በመውሰድ በኢትዩጽያ ድንበር ኡቡክ ነው የገባችው የሰፈረችው፤ በዚህም እጅግ የተቆጡት አፋሮች ከመሃል ተጠራርተው ተነስተው ተመሙ፤ ወደ ባህር ዳርቻ እንድትጠጋ አደረጓት፤ ይህም የሆነው አፋሮች አልገብርም አልገዛም በማለታቸው መቀመጫዎቿን እንድትቀይር አስገድደዋታል፡፡

የአፋሮችን ባንድ ላይ መነሳት እጅግ ያስቆጣት ፈረንሳይ አሊ ሁመድን እና ልጆችን ጭምር በማገት ወደ ማዳጋስካር እስር ቤት በማጋዝና ሌሎችንም በርካታ ሙከራዎችን ብታደርግም

አፋሮችን ከመታገል ያገዳቸው አልነበረም፡፡የአፋሮችን ለቅኝ ገዢዎች የማይንበረከኩ መሆኑን የተረዳችው ፈረንሳይ አፋርን ከነባር መሬቱ ማፈናቀልን ስራዩ ብላ ተያያዛቸው፡፡

በቅድሚያ ዜይላ አካባቢ የነበረውን ነባር ህዝብ ተገፍቶ ወደ ጅቡቲ ገጠራማ አካባቢ እንዲሰፍሩ ከዚያም በመቀጠል የጅቡቲን ከተማ መሆን ተከትሎ ደግሞ ከነባር ግዛታቸው ተነስው በገጠር አካባቢዎች ብቻ ተወስነው እንዲኖሩ አድርጓዋቸዋል፡፡

ታዲያ በእነዚህ ጊዚያት ውስጥ ልክ በሌሎች የአፍሪካ ሃገራት ሁሉ ቅኝ ገዢዎች እንደሚያደርገት ባንዳና ሰራተኛ ሊሆናቸው የሚችሉ ሰዎችን ከሌላ አካባቢዎች በገፍ በማምጣት ማስፈራቸው የየዕለት ተግባራቸው ነበርና፤ ከሌላ አካባቢ በመጡ በሰራተኝነት ና

በወታደርነት ላገለገሏቸው ምንደኞች ባዕዳን፤ ከተማዋን እንዲቆጣጠሩ አደረጉ፡፡

ቅኝ ገዥዋ ፈረንሳይ አፋርን ከታሪካዊ ስፍራ ና ከተሞች ካፈናቀሉት በኋላ ከኢኮኖሚያዊ፣ ከፖለቲካዊ ና ማህበራዊ ጉዳዩች ወደኋላ

እንዲቀሩና ባይተዋር ሊያደርጉት ችለዋል፡፡

ለኢትዮጵያ የተከፈለ መስዋዕትነት በዚህም ውሰጥ እንኳ አፋር ከራሱ አልፎ ወደ ኢትዮጵያ ሲገባ በመከላከሉ ያልከፈለው መስዋዕትነት የለም፤ ተከላክሏል፤ ተዋግቷል፡፡ በ1875 የግብፁ ሙዘንገር በአውሳ በኩል ሊገባ ሲሞክር የተከፈለው መስዋዕትነት፣ ጦርነት ዝም ብሎ አይደለም፤ ጊፉ በተባለው ስፍራ የተካሔደው ጦርነት በደፈናው እንደሚገለፀው ሳይሆን ብዙ ዲፕሎማሲ የተደረገበት መሆኑን እያብራሩ ሲገልፁ በዚያን ጊዜ የኢትዮጵያ ገዢዎች ንጉሶች አንዱ አንዱን ለመጣል ከቅኝ ገዢዎች ጋር የሚስማሙበት ጊዜያት እንደነበረ አስታውሰው አፋር ግን ይህን እምቢ ብሎ በታሪካዊዋ ጊፉ ላይ ተዋግቶ ወራሪ

ሃይሉን ደምስሶታል፡፡

የግብፁ ሙዚንገር በአፋር በኩል ማለፍ ግድ ይለው ነበርና ለመስማማት ከካዲቪ ኢስማኤል የተፃፈ ደብዳቤ ይዞ ነው የመጣው፡፡ እኛ ሚኒሊክ ጋር ተስማምተናል ዮሃንስ ጠላትህ ነው፤ ሙስሊሞችን ጨፍጭፏል፤ ስለዚህ አንዋጋ አሳልፈን የሚል

ደብዳቤ ይዞ መጥቶ ከነመልዕክተኞቹ ጊፉ ላይ ተደምስሰዋል፡፡ ይህ ኢትዩጵያን ከውጭ ወራሪ ለመታደግ የተደረገ ጦርነት ነው ፤ያኔ ይህንን እንደ ቅድመ ሁኔታ ተቀብሎ ቢያሳልፋቸው ኖሮ አገራችን በቀላሉ መፈረካከስ ትችል ነበር፡፡ በአፋር በኩል ገብቶ ኢትዩጵያን ያጠቃ አንድም ሃይል የለም፡፡ በጦርነት ከተሳተፈው አንዱ በ1875 ሁሉም የአፋር ጦር መክቷቸዋል ሲል መፃፉን አንዱ የታሪክ ፀሃፊውን ዋቢ በማድረግ ጠቅሷል፡፡

Filed in: Amharic