>

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ጋዜጣዊ መግለጫ

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ጋዜጣዊ መግለጫ

ሐምሌ 19 ቀን 2014 ዓ.ም

የፌዴራል እና የሁለቱ ክልሎች መንግሥታት በአፋጣኝ በመረጃና በምዝገባ ሥርዓት የታገዘ፣ አሳታፊ የሆነ፣ የተጠያቂነት ሥርዓት የተዘረጋለት እንዲሁም ከፍላጎት ጋር የተመጣጠነ ምላሽ ማቅረብ እና ክትትል ማድረግ፣ እንዲሁም በትምህርት፣ በጤና ግልጋሎት እና በመጠለያ መብቶች ረገድ ያለውን ክፍተት በመለየት መብቶቹን ለማሟላት ተገቢውን እርምጃ በአፋጣኝ መውሰድ እና በመንግሥትና በአጋር ድርጅቶች ለድርቁ የሚሰጡ ምላሾች ለሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ተጋላጭ የሆኑ የማኅበረሰብ ክፍሎችን ልዩ ፍላጎቶች ከግምት ውስጥ ያስገቡ እንዲሆኑ ማድረግ ይኖርባቸዋል

.

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በኦሮሚያ እና በሶማሌ ክልሎች የተከሰተውን ድርቅ እና ያደረሰውን ጉዳት ተከትሎ ከየካቲት 14 እስከ 29 ቀን 2014 ዓ.ም. ድረስ በድርቁ በከፍተኛ ደረጃ ጉዳት ደርሶባቸዋል ተብለው በተለያዩ አካላት በይፋ እውቅና የተሰጣቸው አካባቢዎች በመዘዋወር የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ክትትል በማድረግ ያዘጋጀውን ባለ 50 ገጽ ሪፖርት ዛሬ ይፋ አድርጓል። በዚህም መሰረት በኦሮሚያ ክልል፣ ቦረና ዞን፣ በያቤሎ፣ ተልተሌ፣ ድቡሉቅ፣ ድሬ እና ሞያሌ ወረዳዎች በሚገኙ 11 ቀበሌዎች፤ እንዲሁም በሶማሌ ክልል፣ ሸበሌ፣ ጀረር እና ፋፈን ዞኖች፣ በጎዴ እና አዳድሌ፣ ደጋሃቡር እና ቢርቆድ እና ቀብሪ በያህ ወረዳዎች በሚገኙ 6 ቀበሌዎች በመዘዋወር፣ ተጎጂዎችን፣ የመንግሥት አካላትን፣ የጤና ተቋማት ኃላፊዎችን እንዲሁም የተለያዩ ድጋፎችን የሚያቀርቡ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን አነጋግሯል፣ አካላዊ ምልከታ አድርጓል።

ኮሚሽኑ በክትትሉ በኦሮሚያ ክልል 68 ቁልፍ መረጃ ሰጪ ግለሰቦች ጋር ቃለ-መጠይቆችን እና 15 የቡድን ውይይቶችን እንዲሁም በሶማሌ ክልል 14 ቁልፍ መረጃ ሰጪ ግለሰቦች ጋር ቃለ መጠይቆችን እንዲሁም 24 የቡድን ውይይቶችን በአጠቃላይ 82 ቃለ-መጠይቆችን እና 39 የቡድን ውይይቶችን በማድረግ መረጃዎች እና ማስረጃዎች ሰብስቧል፡፡ በተቻለ መጠን የጾታ እና የተጋላጭ ሕብረተሰብ ተሳትፎ፣ ውክልና እና ስብጥር ከግምት ውስጥ አስገብቷል።

በተጨማሪም ብሔራዊ የሰብአዊ መብቶች ተቋማት ይህን መሰል ከፍተኛ ቁጥር ባለው የማኅበረሰብ ክፍሎች ላይ ጉዳት በሚያደርሱ የተፈጥሮ አደጋዎች ወቅት የሚያደርጓቸው የክትትል እና ምርመራ ሥራዎች በአደጋዎቹ ወቅት የተሰጡትን ምላሾች በመገምገም እና ምክረ ሃሳብ በማቅረብ ረገድ አስተዋጽዖ እንደሚያደርጉ ያስረዳው ኢሰመኮ፣ ይህም ክትትል በዚሁ ዓለም አቀፍ አሠራር እና ኮሚሽኑ በተሰጠው ስልጣንና ኃላፊነት መሰረት የተከናወነ መሆኑን በሪፖርቱ አብራርቷል። ስለሆነም ይህንን ለተቋሙ በዓይነቱ የመጀመሪያው የሆነውን የማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መብቶች ዘርፍ ሪፖርት ሲያቀርብ ክትትሉ በድርቁ ምክንያት የደረሱ ጉዳቶች እና እየተከናወኑ ያሉ የምላሽ ሥራዎችን እንዲሁም መልሶ ለማቋቋም እየተወሰዱ ያሉ እርምጃዎችን አግባብነት ካላቸው ዓለም አቀፍ፣ አህጉራዊ እና ብሔራዊ የሰብአዊ መብቶች መርሆችና ድንጋጌዎች አንጻር በመገምገም ምክረሃሳቦችን የሚሰጥ መሆኑን ገልጿል።

በዚህም መሰረት ክትትል የተደረገባቸው ቦታዎች በተደጋጋሚ ጊዜያት በድርቅ የሚጠቁ አካባቢዎች ቢሆኑም በዚህ ሪፖርት የተሸፈነው ወቅት የተከሰተው ድርቅ ከዚህ በፊት ከነበሩት አደጋዎች በተለየ መልኩ የተራዘመ ማለትም ከ 2 እስከ 4 የዝናብ ወቅቶች ያልዘነበበት እንዲሁም ሰፊ ቦታዎችን ያካለለ እንደሆነ የክትትሉ ግኝት ያሳያል፡፡ በመሆኑም ማኅበረሰቡ እንደ ከዚህ ቀደሙ ወደ ተሻሉ ቦታዎች ተዘዋውሮ ከድርቁ ተጽዕኖ ለማምለጥ አልቻለም፡፡

በድርቁ ጉዳት ሳቢያ በተለይ በቂ ውኃና ምግብ ባለመኖሩ ሰዎች ለተለያዩ የጤና እክሎች ተዳርገዋል፡፡ በምግብ እጥረት ምክንያት ሰውነታቸው የከሳ፣ ሆዳቸውና እግራቸው ያበጠ በዚህም ታመው የተኙ ሰዎች አሉ፡፡ የጤና ግልጋሎት መስጫ ተቋማት በአካልም በኢኮኖሚም ተደራሽ አለመሆናቸውንም ክትትሉ አሳይቷል፡፡ የጤና ግልጋሎቶችን ለራሳቸው ማግኘት ለማይችሉ የድርቁ ተጎጂዎች የጤና ግልጋሎቶችን ተደራሽ በማድረግ ረገድ የተሠሩ ሥራዎች ውስን ናቸው፡፡ በዚህ ምክንያት ተጋላጭ የሕብረተሰቡ ክፍሎች በተለይም አረጋውያን እና ሕፃናት ሕይወታቸው አደጋ ላይ ወድቋል። በድርቅ ምክንያት ተፈናቅለው በተፈናቃይ ካምፖች ውስጥ ለሚገኙ ሰዎች የሕዝብ ጤና አጠባበቅ ተግባራት አለመከናወኑ እና የተፈናቃዮችን ጤና አደጋ ውስጥ ሊከት የሚችል እንደ ወረርሽኝ የመሰለ በሽታ ተጋላጭነት ነበር፡፡ ይህም የድርቅ ተጎጂዎችን የጤና መብት ከማረጋገጥ አንጻር ክፍተት እንዳለ ያመላክታል፡፡

የክትትል ሪፖርቱ በሁለቱም ክልሎች ድርቁ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ድርቁ ስለተከሰተበት አውድ እና አጀማመር፣ ለድርቅ ስጋት፣ ቅነሳ፣ ቅድመ ማስጠንቀቂያ እና ዝግጁነት የተሰጠውን ትኩረት እንዲሁም ድርቁ ያስከተላቸው ጉዳቶች እና የተሰጡ ምላሾች ከሰብአዊ መብቶች አንጻር ዳስሷል። ለምሳሌ በኦሮሚያም ሆነ በሶማሌ ክልል በቅድመ ማስጠንቀቅ እና በዝግጁነት ረገድ የተሰበሰቡት መረጃዎች አግባብነት ባላቸው የብሔራዊ የአደጋ ክስተት ስጋት ሥራ አመራር ፖሊሲና ስትራቴጂ እና በአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ማቋቋሚያ ደንብ ቁጥር 363/2008 ድንጋጌዎች መሰረት የድርቁን አደጋ ቅነሳ፣ ቅድመ-ማስጠንቀቂያና ዝግጅት እንዲሁም የማሳወቅ ሥራዎች በይፋ አለመሠራታቸው ለድርቁ አደጋ ምላሽ የዘገየ እንዲሆን ምክንያት መሆኑን ከክትትል ሪፖርቱ መረዳት ተችሏል፡፡

ድርቁ እና ለድርቁ ምላሽ በመስጠት ሂደት በሰብአዊ መብቶች አፈጻጸም ላይ የተከሰተውን አሉታዊ ተጽዕኖ እና ጥሰትን በተመለከተ ሪፖርቱ በተለይም በሕይወት፣ በምዝገባ፣ መረጃ፣ ተሳትፎ እና ተጠያቂነት፣ በመጠጥና በንጽሕና መጠበቂያ ውኃ መብት እና በምግብ መብት፣ በንብረትና መተዳደሪያ መብት፣ እንዲሁም በትምህርት፣ በጤና እና በባህል መብቶች ላይ ላይ ትኩረት አድርጓል። እንዲሁም የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን ጨምሮ ድርቁ ለመብቶች ጥሰት ተጋላጭ በሆኑ የማኅበረሰብ ክፍሎች ላይ ያደረሰውን ጉዳትም ዳስሷል። ለምሳሌም የውኃ መብትን በተመለከተ ለክትትሉ በተመረጡ ቦታዎች የድርቁ ተጽዕኖ መሰማት የጀመረው የመጠጥና የንጽሕና ውኃ ምንጮች መቀነስ እና መድረቅን ባስከተለ የውኃ እጥረት የተነሳ መሆኑን እና ለዚህ ሁኔታ የሚሰጠው ምላሽ እንደየአካባቢው የተለያየ ሲሆን የመጨረሻው አማራጭ ግን ውኃን በተሽከርካሪ ማከፋፈል አስታውሶ፣ ክትትሉ በተደረገበት ወቅት ድርቁ በተከሰተባቸው አካባቢዎች በመሰረተ ልማት አለመኖር፣ በነዳጅ እጥረት፣ በውኃ ዋጋ መናር ወይም በውኃ አቅርቦት ውስንነት ምክንያት ውኃ ተደራሽ የማይሆንላቸው በርከት ያሉ ሰዎች እንደነበሩ ያሳያል፡፡

ኢሰመኮ በአፋጣኝ እና በሂደት ወይም በመካከለኛ ጊዜ ውስጥ ሊተገበሩ ይገባል በማለት በመከፋፈል የተለያዩ ምክረ ሃሳቦችን ያቀረበ ሲሆን፣ በተለይም የፌዴራል እና የኦሮሚያ እና የሶማሌ ክልሎች መንግሥታት በአፋጣኝ ሊተገብሯቸው ይገባል ካላቸው መካከል አንዱ በመረጃና በምዝገባ ሥርዓት የታገዘ፣ አሳታፊ የሆነ፣ የተጠያቂነት ሥርዓት የተዘረጋለት እንዲሁም ከፍላጎት ጋር የተመጣጠነ ምላሽ ማቅረብ፣ ማሰራጨት እና ክትትል ማድረግ የሚለው ነው። በተጨማሪም ኮሚሽኑ መንግሥት ከአጋር ድርጅቶች ጋር በመሆን በድርቁ ሳቢያ ለተፈናቀሉ ድጋፍ ፈላጊዎች ባሉበት ቦታ እርዳታ እንዲያገኙ እንዲያደርግ፣ እርዳታ የሚገኝበትን ቦታ እና ሁኔታ እንዲያሳውቅ እና ያለ በቂ መረጃ. ለሚፈናቀሉ ሰዎች አፋጣኝ እርዳታ ለማድረግ የሚያስችል የመጠባበቂያ እርዳታ ዝግጁ እንዲያደርግ ጠይቋል።

ይህንኑ አስመልክተው የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ፣ መንግሥት በተለይም የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ሕጉ በሚያዘው መሰረት የድርቁን አደጋ በይፋ በማሳወቅ በአደጋ ክስተት ስጋት ሥራ አመራር ሥራ እገዛ ከሚያደርጉ ሀገራዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች እና ሀገሮች ጋር ሀገሪቱ ያጸደቀቻቸው ዓለም አቀፍ እና አህጉራዊ ስምምነቶችን መሰረት ያደረገ ዓለም አቀፍ ትብብር እንዲኖር የማድረግ ግዴታ እንዳለበት አስታውሰዋል። በተጨማሪም “እስካሁን በመንግሥት እና መንግሥታዊ ባልሆኑ አካላት በድርቁ ለተጎዱ ሰዎች እና አካባቢዎች የተሰጡ ምላሾች አበረታች ቢሆኑም፣ ተጎጂዎች አሁንም በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ እና ድርቁም ከሁለቱ ክልሎች በተጨማሪ ወደሌሎች አካባቢዎች እየተስፋፋ ነው፤ እንዲሁም በተለያዩ ግዜያት በሁለቱ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች በሚያገረሹ ግጭቶች ምክንያት በድርቁ ሳቢያ የተፈናቀሉ ሰዎችን ለተደራራቢ ጉዳት እየዳረገ ነው። ስለሆነም በድርቁ ለተጎዱና አዋሳኝ አካባቢዎች የሚሰጠው ትኩረት ሊቀንስ አይገባም” በማለት ዶ/ር ዳንኤል ጥሪ አቅርበዋል።

Filed in: Amharic