>
5:13 pm - Wednesday April 20, 8687

የፌዴሬሽን ምክር ቤት የኦህዴድ ትርፍ አንጀት ምክር ቤት...! (ግርማ ካሳ)

የፌዴሬሽን ምክር ቤት የኦህዴድ ትርፍ አንጀት ምክር ቤት…!

ግርማ ካሳ

 


የፌዴሬሽን ምክር ቤት የሚባለው 153 አባላት ያሉት ነው፡፡ እያንዳንዲ ብሄር ብሄረሰብ የሚባለው አንዳንድ ተወካይ አለው፡፡ ጉሙዝ፣ ሃመር፣ ሽናሻ፣ አርጎባ ..ሁሉም፡፡ ወደ 76 ናችው፡፡ ከአማራ ክልል አገው አዊ፣ አገር ዋግ፣ አርጎባና አማራ 4 ተወካዮች አሉ፡፡ ከደቡብ ወደ 53 ተወካዮች አሉ፡፡ ከኦሮሞ አንድ ተወካይ፡፡ በቤኔሻንጉል፣ ለማኦ፣ ኮሞ፣ ሸናሽ፣ ጉሙሽና በርታ 5 ተወካዮች፡፡ እንዲህ እያለ 76 ተወካይች ይደርሳሉ፡፡

ከ153ቱ 77ቱ በሕዝብ ነው የሚወሰነው፡፡ አንድ ሚሊዮን ተጨማሪ ያለው አንድ ተጭዕማሪ ተወካይ ይሰጠዋል፡፡ ኦፌሴላዊ በሆነው፣ እንደ ፈረንጂ አቆጣጠር በ2007 በተደረገው የሕዝብ ቆጠራ መሰረት፣ ለአማራ ብሄረሰብ ተጨማሪ 25 ተወካይ ይሰጠዋል፡፡  ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ቅርበት ያላቸው እንደነገሩኝ ቀመሩ ኦፊሲላዊ በሆነው ቆጠራ ሳይሆን የስታቲስቲካል ኤጂነሲ በቅር የስጠውን ግምት ( estimate) ተመርኩዞ ነው፡፡  ሆኖም ኝ የስታቲስቲካል ኤጂነሴው በዘር ወይንም ብሄረሰብ ያለው ግምታ ያካተተበት ሰነድ ይፋ አላደረገም፡፡

እንግዲህ ይህ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ኢፍትሃዊና ኢዴሞክራሲያዊ ነው ፣ የአዲስ አበባ፣ የዴራዳዋ ህዝብ ፣ ለምሳሌ በኦሮሞ ክልል ያሉ ኦሮሞ ያልሆኑ ማህበረሰባት አልተወከሉም የምለው ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ አማራዉን ወክለው የፌዴሬሽን ምክር ቤት አባላትን የሚመርጠው የአማራ ክልል ምክር ቤት ነው፡፡ የአማራ ክልል ምክር ቤት አዲስ አበባ፣ ድሬዳዋ፣ ሃረር፣ ናዝሬት፣ ጂማ፣ መተከል፣ አሶሳ፣ አርሲ …ያሉት አማራዎች የመረጡት አይደለም፡፡ አምስት ሳንቲምም ከአማራ ክልል ውጭ ስላሉ አማራዎች ሲከራክር፣ ሲሞግት፣ ለነርሱ መብት ሲሰራ አላየንም፡፡ ታዲያ እንዴት ነው ከጎጃምና ከጎንደር የመጡ የአዲስ አበባ ፣ ሆነ የነ ሃረር ድሬዳዋን ነዋሪዎች ጥቅምና ፍላጎት አንስተው ሊከራከሩና ሊሞግቱ የሚችሉት ? ይሄ አንዱ ነጥብ ነው፡፡

 

ሌላው በፌዴሬሽን ምክር ቤት ከ153ቱ  አባላት ነን የሚሉት አማራ ነን የሚሉት 20  ቢሆኑ ነው፡፡ 13%  ብቻ፡፡ ስለዚህ በወልቃይት ጉዳይ ላይ አብይ አህመድና ኦህዴዶች የፌዴራል መንግስት የተቆጣጠሩ እንደመሆናቸው ከአማራ ክልል ውጭ ያሉ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አባላት ኪሳቸው ውስጥ ነው ያሉት፡፡ አሁን እርስቱ ይርዳውና የደቡብ ክልል ሰዎች፣ እነ አሻድሊ ሁሴን …ከኦህዴዶች ፍቃድ ውጭ ይሂዳሉ ???

በመሆኑም በፌዴሬሽን ምክር ቤት የሚወሰነው ውሳኔ ኦህዴዶች የፈለጉት ውሳኔ ነው፡፡ አብይ አህመድ ይሄንን ያውቃል፡፡ ለማወናበድ ሲል ነው አገኘው ተሻገርን የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዬ ያደረገው፡፡ ልክ ደመቀ መኮንን ከህወሃት ጋር በሚደረገው ውይይት የኮሚቴ ሰብሳቢ እንዳደረገው፡፡ “እኔ አይደለሁም፣ አማራ ተበድሏል የምትሉ ከሆነ አማራዉን አገኘውን ጠይቁት፣ አማራዉን ደመቀ ጠይቁት” ብሎ ፣ ከነርሱ ጀርባ ሆኖ እነርሱ አጋፍጦ ለማምለጥ፡፡ ሰውዬው ልማዱ ነው እርሱን ጻድቅ አድርጎ ሌላው መክስ፡፡

Filed in: Amharic