>

ሂስ ዘ መጽሐፍ “ፍኖተ ዐማራ፡ በፕ/ር ግርማ ብርሃኑ 2015 ዓ/ም” (በዳመና ዝናቡ ጎርፉ)

ሂስ ዘ መጽሐፍ “ፍኖተ ዐማራ፡ በፕ/ር ግርማ ብርሃኑ 2015 ዓ/ም”

በዳመና ዝናቡ ጎርፉ 

ሂስ ስጽፍ አቃቂረኛ፥ አላጋጭ እና አሽሙረኛ ነኝ። እና አንድን ጽሑፍ አንብቤ ስጨርስ አቃቂር ለማውጣት የማይመቸኝ ከሆነ ወይም የማላግጥበት ይዘት ከሌለው ሂስ (ግምገማ) አልጽፍበትም። የሚያቆለጳጵስ ወይም ማመስገኛ ሂስ ጽፌ አላውቅም። በጽሑፍ ግምገማ ላይ አድናቆትና ምስጋና መግለጽ ብፈልግ እንኳ ቃላት የሚገጣጠሙልኝ አይመስለኝም። ይህን መጽሐፍ ካነበብኩ በኋላ ግን በለመድኩት መንገድ ሂስ ማዘጋጀትም አልቻልኩም፤ ሂሱን አለመጻፍም አልቻልኩም። እና አዲስ ሙከራዬ ስለሆነ ይህን ጽሑፍ ካነበባችሁ በኋላ ለእኔም ሂስ ጻፉልኝ። 

ፕ/ር ግርማ የሀገር ፍቅር ለህዝብ ክብር ያላቸው፡ በኢትዮጵያ ላይ የተጋረጠው የመፍረስ አደጋ የሚያንገበግባቸው ምሁር ናቸው። የስራ ዘመናቸውን በሙሉ በአውሮፓ የኖሩ ቢሆንም፡ ሀገራቸው ለአፍታም ከአእምሯቸው ጠፍታ እንደማታውቅ በየወቅቱ የሚታተሙት ስራዎቻቸው ያመለክታሉ። መቼም አንድ ጽሑፍ ተዘጋጅቶ ለህትመት እስኪበቃ ድረስ ይዘቶቹ በጸሐፊው አዕምሮ ምን ያህል እንደሚብላሉ መገመት አይከብድም። የሙሉ ሰአት ስራው የሆነ ሰው ቢሆን እንኳ እርሳቸው እንደሚያደርጉት ለእያንዳንዱ ጥናታዊ ጽሑፍ ማጣቀሻ የሚሆኑ በርካታ ጥናታዊ ስራዎችን አንብቦ፡ ጠጣር ጭብጥ ያለው አንድ ጽሑፍ አጠናቅሮ ለህትመት ለማብቃት፡ ወራት ሊፈጅበት ይችላል። እርሳቸው ግን በወር ውስጥ ብዙ ጽሑፎች አሳትመው፥ በሚዲያ ለረጅም ሰአታት ማብራሪያ ሰጥተው፥ ለተለያዩ ወገኖች እርዳታ አድርገው . . . ነው ዋናውን የምርምርና የማስተማር ስራቸውን ደግሞ የሚሰሩት። ይህ ድካም በቀላሉ የሚታይ መስዋእትነት አይደለም። ያለጥልቅ የሀገር ፍቅርና ተቆርቋሪነትም ይህ መስዋእትነት ሊከፈል አይችልም። እንደርሶም ያለ የለ ፕ/ሮ! በውነት የመጨረሻው ፕ/ሮ ማክስ ነዎ! ጥርት ያለ እይታ ትልቅ ሚሞሪ ያለው ስለሆነ ገዝቸዋለሁ ሀሳብዎን። 

ለመጀመሪያ ጊዜ ፕ/ር ግርማን ያወቅኳቸው “Black intellectual genocide” በሚል ጽሑፋቸው ነው። ጽሑፉ የምርምር ስራ ዉጤት ሲሆን በ”education review: a journal of book reviews” እ.አ.አ በ2007 የታተመ ነው። ጽሑፉ ሪቻርድ ሊን እና ታቱ ቫንሃነን “IQ AND THE WEALTH OF NATIONS” በሚል ርዕስ ያሳተሙትን ጥናታዊ ስራ የሚሞግት ነው። ፈረንጆቹ የኢትዮጵያውያንን የማሰብ አቅም በተዛባ ስልትና አለካክ እጅግ ዝቅጠኛ አድርገው በማቅረባቸው የደረሱበትን አሉታዊ ማጠቃለያ በመቃወም ነባራዊ ሁኔታውን በተገቢው ልኬት እንዴት ማቅረብ እንደሚገባ በሙያዊ ቋንቋቸው ይገስጻሉ። ኢትዮጵያዊያንን ዝቅ አድርጎ የሚያየውን ጥናት ሲሞግቱ ታዲያ ከሳይንሳዊ ጽሑፍነቱ ባሻገር “ዘራፍ!” የሚያስብለው የኢትዮጵያዊ ወኔ ቀስቅሶ ጥናቱን እንዳስጀመራቸው አልጠራጠርም።  ስለሀገር ፍቅራቸውና ለህዝብ ያላቸውን ክብርም በዚህ ጽሑፍ የመጀመሪያ መስመር ላይ ያሰፈርኩት፡ ጥናቱን ለማድረግ ያነሳሳቸውን ቁጭት ተገንዝቤ ነው። ከዚያ በኋላ ጽሁፎቻቸውን ተከታትዬ ማንበብ ጀመርኩ። 

በአማራ ህዝብ የህልውና አደጋዎች ላይ የሚጽፏቸውን ትንታኔዎች በ borkena.com, Eurasia Review, Ethiopian Insight, Zehabesha.com ላይ ሲታተሙ አነባለሁ። አሁን ደግሞ “ፍኖተ ዐማራ” በሚል ርዕስ ያሳተሙትን መጽሐፍ አንብቤ ጨረስኩ። መጽሐፉ በርካታ መረጃና ማስረጃዎች እንዲሁም ምልከታና ጥቆማዎች ቀርበውበታል። ነባራዊ ሁኔታዎችን መረዳት በሚገባን ልክ በመተንተን ከድርጊቶች ታሪካዊ መነሻ እስከ ወደፊት እርምጃዎች ተብራርተዋል። 

በመጀመሪያው ምዕራፍ ጸረ-አማራ የሀሰት ትርክቶች አመሰራረታቸውንና ኢላማ ያደረጓቸውን እሴቶች፡ በተለይ በአማርኛ ቋንቋ እና በአጼ ምኒልክ ላይ በርካታ ዋቢዎችን በማመሳከር በሰፊው አትተዋል። እንደሚታወቀው ምእራባውያን ከቅኝ ግዛት ሙከራዎች በኋላ በደረሰባቸው ሽንፈት ትልልቅ የበቀል ሴራዎችን ጎንጉነው ኢትዮጵያን በክፋት ጎብኝተዋታል። ከአድዋ ድል በኋላ አርባ ዓመታትን ቆይተው ጣሊያኖች ወረራ ቢያደርጉም ሊሳካላቸው ባለመቻሉ፤ በመቸውም ዘመን በሞከሩበት መንገድ ኢትዮጵያን ማንበርከክ እንደማይቻል ተገንዝበውታል። ከዚያ በኋላ አመጣጣቸውን በቀጥተኛ ወረራ ወይም በጦርነት ሳይሆን የሀገሪቱን ህዝቦች እርስ በእርስ በሚያጣሉ፥ በሚከፋፍሉና የጋራ ኃይላቸውን ማድከም በሚቻልበት የረጅም ጊዜ ሴራ መሆን እንዳለበት ተረድተዋል። ይህም የሀገሪቱን ጥንካሬ በመለየትና ለቅኝ ገዥዎች የማይሸነፍ ህዝብ ያደረጋቸውን ተቋማትና እሴቶች በመለየት በተናጠል የሚጠቁበትን ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች በመንደፍ እንደነበር ያስረዳሉ። 

ከነዚህ የሀገሪቱ ጥንካሬ መሰረቶች ውስጥ የተለዩት ዋና ዋናዎቹ ህዝብ የሚያምነውና ለህዝቡ የሚታመነው ዘውዳዊ ስርአተ-መንግስት፥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን፥ የመንግስትና የህዝብ አንድነት መገለጫና የሉአላዊነት አርማ የሆነው ሰንደቅ አላማ፥ የሀገሪቷ ህዝቦች የጋራ መግባቢያ በመሆን ያገለገለው አማርኛ ቋንቋ እና ለተደጋጋሚ ሽንፈት የዳረጋቸው ሀገር ወዳድ የአማራ ህዝብ ነው። እነዚህን ተቋማትና እሴቶች ማፍረስ ሲቻል ሀገሪቱ ደካማ ስለምትሆን ለቅኝ ግዛትም ሆነ ለበቀል ጥቃት የምትመች እንደምትሆን ምእራባውያኑ ቅድመ ስምምነት አድርገውበታል። በዚህ መሰረት ጠንካራ ተቋሞቹን መበተን የሚቻልባቸውን ዘዴዎች ነድፈው ፕሮጀክቶች ቀርጸው ወደ ሀገሪቱ በማስገባት ላለፉት መቶ አመታት ስራቸውን ሲሰሩ ኑረዋል። 

የመጀመሪያው ፕሮጀክታቸው በካቶሊክ ሚሲዮናውያን ስም በርካታ ፖለቲከኞቻቸውን በማስገባት በተለይም በወለጋ አካባቢ አማራ ጠልነትን “ነፍጠኛ” በሚል መለያ ኮድ እንዲስፋፋ፥ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ – የነፍጠኛ ባንዲራ በማለት እንዲጠላ የማድረግና ኦሮሞውን ከኢትዮጵያዊ ስነልቦናው መለየት፥ ዘውዳዊ ስርአቱን ጨቋኝና ገዳይ እንደሆነ መስበክና ኦርቶዶክስ ተዋህዶን የአማራ ብቻ ሐይማኖት በማስመሰል የሀሰት ትርክቶቹን ለዘመናት በህዝቡ የማስረጽ ስራ ሰሩ። በዘመናዊ ትምህርት ሰበብም ወደ ሚሲዮኖቹ ሀገር ወስደው ዘውዳዊ ስርአቱን መገልበጥና ማጥፋት የሚችሉ ተማሪዎችን አፈሩ። የመጀመሪያው የምእራባውያኑ ጸረ-ኢትዮጵያ እንቅስቃሴ ስኬትም የተለካው የሀገሪቱን ስርአተ መንግስት በራሷ ልጆች ማውደም መቻላቸው ነበር። 

ዘውዳዊ መንግስቱ የራሱ ችግሮች ቢኖሩበትና ለዜጎቹ ምቹ ያልነበረ ቢሆንም እንዲጠፋ የተደረገበት መንገድ ግን በውጮች ሴራ እንጅ በሀገር ውስጥ ኃይሎች የእድገት ሂደት በመጣ ጥያቄና ትግል ስላልነበረ ከዘውዳዊ መንግስቱ መፍረስ ማግስት ሊተካ የሚችል የተሻ አስተዳደራዊ ስርአት አልተገኘም። የተሻለ ስርአተ መንግስት እንዳይፈጠርም ሌትና ቀን ተግተው የሚሰሩት እነዚሁ ለዘውዳዊው ስርአት መፍረስ ምክንያት የሆኑ የሀሰት ትርክት ፋብሪካ ሚሲዮናውያን ናቸው። ምክንያቱም ምንጊዜም ፍላጎትና ተልእኳቸው ሀገሪቱን ማቆርቆዝ እንጅ የተሻለ ስርአት እንዲፈጠርላት አልነበረም። የብሔር ፖለቲካ ወደ ሀገራችን እንዲገባ የተደረገው በድንገት ሳይሆን የህዝብ ለህዝብ መቃቃሩን ወደ መገዳደል ለማሳደግ፡ የፖለቲካ አይዲዮሎጅ እንዲመራው ለማድረግ ታቅዶና ታምኖበት ነበር። የተለያዬ ቋንቋ ተናጋሪውን ማህበረሰብ የተጨቋኝ ስነልቦና እንዲኖረው በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ስኬት ካስመዘገቡ በኋላ የእራስ ገዝና ነጻ አውጭ ፓርቲዎች እንዲፈጠሩና ተጠናክረው የፖለቲካውን መሀል ሜዳ እንዲይዙ ለማድረግ ያላፈሰሱት ሙዋለ ንዋይ የለም። የፓርቲ ማቋቋሚያ የተደረጉ፥ የህዝብ ታሪክ ተደርገው መወሰድ የቻሉ በርካታ ስሁት ትርክቶች ባልተጠበቀ ፍጥነት የሀሳብ ገበያውን ተቆጣተሩት። መከፋፈል፥ ጥላቻ፥ መንጋነት እና ጽንፈኝነት ጦዘ። 

ይህ ጡዘት ዛሬ ጸረ-ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን እንቅስቃሴ፥ የነጻነት አባታቸው የሆነውን የምንጊዜም ባለውለታ ንጉስ ምኒልክን ጭራቅ አድርጎ መሳልና የድልና የነጻነት አርማዋን አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ሰንደቅ አላማ “ጨርቁ” ብሎ ከመጥራት እስከ አናሰቅልም ማለት ድረስ መጥላትና የራሳቸው ወንድምና እህት የሆነውን የአማራን ህዝብ የዘር ማጽዳት ግድያ መፈጸም አደረሳቸው። አሁን እነዚህን ሰዎች “ያመናችሁት የሀሰት ታሪክ ነው፤ አማራ ጠላታችሁ አይደለም” ብሎ ማስረዳት አይቻልም። ተወልደው አድገውበታልና ሌላ ታሪክ አያውቁም። በምናብ የተፈጠሩ ክስተቶችን ሰበብ በማድረግ  እውን እርምጃ ወደ መውሰድ ያደረሱት የስሁት ትርክቶቹ ደራስያን ጠላቶች ናቸው። ሜንጫና ቆንጨራ ይዞ አማራን እየገደለ ላለው ወጣት መንስኤዎቹ ከአያቶቹ ጀምሮ ሲሰርጽበት የቆየው ጸረ-አማራ ጥላቻ ነው። የዚህ አረመኔያዊ ድርጊት ፈጻሚዎች ጥፋተኛ አይደሉም ማለት ግን አይደለም። 

በመሆኑም ዛሬ በአማራ ህዝብ ላይ የሚደርስበት ጅምላ ግድያ፥ መፈናቀልና መገለል የሀሰት ትርክቶቹ ጥቅል ውጤት ነው ማለት ይቻላል። ለዚህ ህዝብ በደል ፍትህ መጠየቅና የህልውና አደጋውን የሚቀለብስበትን አቅጣጫ መጠቆም ፍጹም ሰብአዊነትና ለነፍስ ጽድቅ የሚሰራ እንጅ ዘውጋዊ ወገንተኝነት አድርጌ አልረዳውም። ለዚህም ነው ፕ/ር ግርማን በዚህ መጽሐፋቸው ይዘት ላይ በተለየ መልኩ ሂስ እንዳቀርብላቸው የገፋፋኝ። 

አማራ ከተጋረጠበት የህልውና አደጋ እንዲወጣ በእውቀት፥ በሞራል፥ በገንዘብ፥ በማቴሪያል ወዘተ ድጋፍ ማድረግ የአማራ ብሔር ተወላጅ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያን አንድነትና እንደ ሀገር መቀጠል የሚፈልግ ሰው ሁሉ ሚና ነው መሆን ያለበት። የአማራ መድከም፡ የኢትዮጵያ መፍረስን ይቀድማል። የአማራ መጠንከር የኢትዮጵያ ትንሳኤ መሰረት ነው። እኔ ተንትኜ ያቀረብኩት ሳይሆን የኢትዮጵያ ቋሚ ጠላቶች ድምዳሜ ነው። የኢትዮጵያ ጠላቶች ደግሞ በሀገሪቱ ውስጥ ካሉ ማህበረሰቦች ውስጥ መርጠው ዘመድ የሚያደርጉት ጎሳ እንደሌለ ማወቅ ተገቢ ነው። አንዱን በአንዱ አስገድሎ ብቻውን የቀረውን አስሮ መግረፍ ቀላል እንደሚሆንላቸው አስበው የሚያደርጉትን ሴራ መረዳት ይገባል። 

በመጽሐፉ ሶስተኛና አራተኛ ምዕራፎች ላይ በጥልቀት እንደተመላከተው ላለፉት ሰላሳ ዓመታት ስልጣን ላይ የቆየው የብሔር ነጻ አውጭ ፖለቲካ ያደራጀውን የፖለቲካ ባህል ወርሶ አሁንም እየገዛ ያለው አስተዳደር ከጥፋት መንገዱ ሊመልሰው የሚችል መካሪ እልተገኘለትም። ይልቁንም ከፖለቲካው መረን የለሽነት አልፎ የባህል ስሪቶችንና ማንነቶችን ደምስሶ የራስን ማንነት ማላበስ የሚፈል ግልጽ ዘር ጭፍጨፋ የሚፈጽም ኃይል እየጎነ መጥቷል። በተለይ አማራዎች ላይ ያነጣጠረ የዘር ማጽዳት ግድያ በኦሮሞ ኃይሎች አሁንም እየተፈጸመ ነው። የራሱ የአማራ ህዝብ አመራር ተብየዎችም ለመጣ ለሄደው የማእከላዊ መንግስት ገዥ ታዛዥና ተላላኪ ከመሆን ያለፈ የሚመሩትን ህዝብ መሰረታዊ ጥያቄዎች መመለስ በሚችል ፍላጎትና አቅም እንዲሁም ስነልቦና እና ሞራል የተገነቡ እንዳልሆነ በተጨባጭ ተብራርቷል። 

ስለዚህ ተወደደም ተጠላም የአማራ ህዝብ ከእልቂት የሚተርፍበትን ውስጣዊ አደረጃጀት ፈጥሮ በራሱ አቅም ህልውናውን ለማስቀጠል መታገሉ አይቀርም። ለእልቂቱ ምንጭ ወደሆነው ውጫዊ አለማቀፍ ማህበረሰብ መቼም ድረሱልኝ፥ አድኑኝ የሚለው አይኖርም። ፍኖተ ዐማራ ይህንን የህልውና ትግል በፋኖ አደረጃጀት መጀመርና ሁለንተናዊ ህዝባዊ እንቅስቃሴ በማድረግ አስተዳደራዊ ስርአትን ብቻ ሳይሆን መሰረታዊ የባህል አብዮት ማድረግ እንደሚገባም ይመክራል። ይህ ህዝባዊ አብዮት በድንገተኛ ስልጣን አዳኝ ቡድኖች ተነጥቆ እንዳይኮላሽም በአዋቂዎች የሚመራ አዲስ የስርአት ስሪት መሰረት የሚጥል እንዲሁም በየደረጃዎቹ በቁጥርና በልኬት መገምገም የሚችሉ ውጤቶችን ማምጣት በሚቻልባቸው መርሀግብሮች ማቀድ እንደሚቻል ተገልጿል። በዚህ ረገድ ምሁራን ከተጽእኖ ነጻ ሁነው በየእውቀታቸው የዚህን ህዝብ ህልውና መታደግና አኗኗሩን ማሻሻል የሚችሉ ሀሳቦችን አስተዋጽኦ በማድረግና ህዝባዊ መሪ በመሆንም የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ አጽንኦት በመስጠት ይጠቃለላል።   

መጽሐፉን ወድጄዋለሁ። አስተምሮኛል። ሁሉም ሰው ቢያነበው እመክራለሁ። ነገር ግን ለመሳቅ ወይም ለመዝናናት የሚነበብ መጽሐፍ አይደለም። ይልቁንም በሚያሳዝኑ፥ በሚያበሳጩ፥ በሚያስቆጩ ጭብጦች እና እውነቶች የተሞላ ብዙ ነገሮችን በሽፋናቸው ከምናውቀው የተለዬ ይዘታቸውን ግልጥልጥ አድርጎ የሚያሳይ የጥናታዊ ስራዎች ጥንቅር ነው።

Filed in: Amharic