>

የፋኖን ባህሪ፣ ሂደትና እድገት አስመልክቶ (አንዱ ዓለም ተፈራ)

የፋኖን ባህሪ፣ ሂደትና እድገት አስመልክቶ

አንዱ ዓለም ተፈራ

 

የፋኖን አፈጣጠርና ምንነት ብዙዎች ስለዘረዘሩት እዚህ መደረት አልፈልግም። እኔ ማቅረብ የፈለግሁት፤ እኛ በውጪ አገራት የምንገኝ ኢትዮጵያዊያን፤ አሁን በተጨባጭ ያለውን የፋኖ ባህሪ፣ ሂደትና ዕድገት አስመልክቶ ስለአለን ግንዛቤ ነው።

ፋኖ፤ አገር ወዳዱና ወገን አፍቃሪው ሁሉ፤ በያለበት አካባቢም ሆነ ባገር አቀፍ ደረጃ፤ መንደሩን ሆነ አገሩን የሚያሰጋ ሁኔታ ሲፈጠር፤ ይሄን ለመቋቋም በአንድነት ነፍጥ አንግቶ የሚነሳበት ክስተት ነው። በአብዛኛው ` የአንድ ጎጥ ወይንም የአንድ አካባቢ ጉዳይ ሆኖ አብሮን ኖሯል። አሁን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተከሰተው፤ የፋሽስት ጣሊያን ወራሪ ጦር ወደ አገራችን በገባ ጊዜ የተፈጠረው ዓይነት ሁኔታ ነው። ቀደም ሲል፤ መይሳው ካሣ፣ በላይ ዘለቀ፣ አቡነ ጴጥሮስ፣ ገበየሁና ባልቻ፣ ኃይለማርያም ማሞ፣ ታከለ ወልደ ሐዋሪያት፣ አበበ አረጋይ፣ አብዲሳ አጋ፣ ዘርዓይ ድረሰ፣ አብረሃ ደቦጭና ሞገስ አስገዶም፣ አብቹና አበራ ካሣ፣ ገሪማ ታፈረ በፋኖነት ታሪካዊ ግዴታቸውን ተወጥተዋል። ዛሬም ይሄ ታሪካዊ ዕሴታችን ደምቆ እየቀጠለ ነው።

የፋሽስቱ ወራሪ ጦር ኤርትራን ጠቅጥቆ፣ ትግራይን ዘልቆ ወደ ቀሪው ደቡብ ክፍል ሲያመራ፤ አገር ወዳዱ ፋኖ እየተደራጀ፤ በያለበት አገሩን መከላከል ያዘ። በየክፍለ አገሩና መንደሩ፤ የፋኖ ስብስቦች፤ ነፍጥ አንግበው፤ “ወደኛ መንደር ሰላቶ አይገባም!” በማለት የየቡድኖቻቸው አለቆች መድበው አገር መከላከል ያዙ። አኒህ መሪዎች፤ የየቡድኖቻቸው አለቆች በመሆን ታወቁ። ቀስ አያለ አገር አቀፍ እየሆነ ሄደ። ቀዶ ከሠራው የመኪና መንገድ በስተቀር፤ ወራሪው የፋሽስት ኃይል ወደ ገጠሩ መግባት አልቻለም። በጎንደር ቢትወደድ አዳነ መኮነን እና አሞራው ውብነህ፣ በጎጃም አነ በላይ ዘለቀ፣ በሸዋ እነ ኃይለማርያም ማሞና ሌሎችም አካባቢያቸውን ተቆጣጥረው መደማመጥ ያዙ። የወራሪውን ፋሽስት ጦር፤ በየቦታው ፋኖዎች የየአካባቢያቸውን መሬት እሳት ሆነው ባለማስነካት፤ መቀመጫ ነሱት። ደጃዝማች ታከለ ወልደ ሐዋሪያት ወደ ጎጃም፣ ወደ ጎንደር፣ ወደ ጅግጅጋና ወደ ኬንያ ሁሉ በመዘዋወር አስተባብረዋል። ራስ አበበ አረጋይና ሌሎችም በሚችሉት ሁሉ እንዲሁ አድርገዋአል። ይህ የትናንቶቹ የፋኖዎች ታሪክ ነው። ወራሪውን የፋሽስት ጦር ካገር ያስወጡት፤ እኒህ በየቦታው ተበታትነው የነበሩ ፋኖዎች፤ አንድ አገር አቀፍ ራዕይ ይዘው አገራችን ኢትዮጵያ፣ ስንደቃችን አረንጓዴ ብጫ ቀይ፣ አንድነታችን ኢትዮጵያዊነታችን ብለው ነበር። አንድ ሕዝብ፣ አንድ አገር፣ አንድ ሰንደቅ ዓላማ፤ ምንግዜም ነፃነት! ብለው ነበር። ይህ በሂደት ያደገ ሕዝባዊ አንድነት፤ የብዙዎችን ጥረትና ትብብር ተንተርሶ ነበር።

አሁን ያለውን የፋኖ ባህሪ፣ ሂደትና ዕድገት ስንመለከት፤ ተመሳሳይ ሁኔታዎችን እንገነዘባለን። ፋኖዎች በያሉበት አካባቢያቸውን ለመጠበቅ ነፍጥ አንግበው ተነሱ። በያሉበትም ያካባቢያቸው መሪዎች አበጁ። መሰባሰብና ማደግ ያዙ። ይሄ የሆነው በሂደት ነው። ቀጥሎ ገዢው ቡድን በከባድ መሳሪያ፣ የብልፅግና መዋቅር፣ እና መንግሥታዊ ጉልበቱንም ተጠቅሞ፤ ከባድ ጉዳት ማድረስና ማጥቃት ያዘ። እናም ፋኖዎች ከትንንሽ የመንደር ቡድኖች ወደ ቀጠና መሰባሰብ ያዙ። የፋኖዎች መገናኛ መንገድ አስቸጋሪ የሆነበትና፤ የስልክ ልውውጡ ጠላት በሚዘውረው የቴሌኮሚኒኬሽን መስሪያ ቤት በኩል መሆኑ፤ እንቅፋቶች ፈጠረባቸው። መጠቂያም ሆነባቸው። ሲፈልግ የሚዘጋውና ሲፈልግ የሚከፍተው የበይነመረብ ሥርጭት፤ አስተማማኝ በሆነ መንገድ መጠቀም አልተቻለም። እናም በፍጥነት ወደ አንድ መጥተው፤ አንድ ራዕይ ይዘው፣ አንድ ግብ አጽድቀው እንዲታገሉ አልረዳቸውም። ሆኖም ይሄ አላቋረጠም። አሁንም እየተቀራረቡ ናቸው። ፈረንጅ፤ “Growing pain” ይላል። የግድ መታለፍ ያለበት አስቸጋሪ ሂደት! በዚህ ወቅት ጥሩ አጋጣሚዎች ሊያመልጡ፣ ቶሎ መታረም ያለባቸው እንዲቆዩ ሊደረጉ፣ አላስፈላጊ መስዋዕትነት ሊደርስ ይችላል። የማያመልጡት ዕዳ ነው!

ይሄ ሂደት በቅርብ ሊገኝ የሚችለውን ድል ሊያዘገይ ይችላል። ድል ግን አይቀሬ ነው። ድል የሚመጣው፤ እየደረሰ ያለው ግፍ ከባድ በመሆኑ፣ የተያዘው ትግል ትክክለኛ በመሆኑና፤ ሕዝቡ የትግሉ ባለቤት ስለሆነ ነው። የአደረጃጀቱ ሁኔታ ድሉን ሊያዘገይ ይችላል እንጂ፤ አይቀሬነቱን አይቀይረውም። በመጀመሪያ እስክንድር ነጋ፣ ቀጥሎ ምሬ ወዳጆና የተወሰኑ የፋኖ መሪዎች፣ ቀጥሎ በጎንደር የፋኖ ለህልውና ለፍትህ እና ለዴሞክራሲ ንቅናቄ፣ ተከትሎ ደግሞ ዘመነ ካሤ በበኩሉ፤ በያሉበት ተደራጅተው የተለያዩ ግንባሮችን መሥርተዋል። አስፈላጊም ተገቢም ናቸው። የሚያስደንቅ አይደለም። ችግር የለበትም። መከተል ያለበት፤ እኒህ ሁሉ፤ ጠላታቸው አንድ፣ ግባቸው አንድ፣ ድልና ጉዳታቸውም አንድ ስለሆነ፤ ወደ አንድ የመሰባሰባቸው ሂደት ነው። ይሄ በሂደት ይከተላል። በዘመነ ካሤ ጥይት፣ በምሬ ወዳጆ ጥይት፣ በውባንተ ጥይት፣ የሚቆስለው የአብይና የብርሃኑ ጁላ ወታደር ነው። በዚህ በኩል የሚቆስለው የአማራ ልጅ ነው። አማራ የሚታገለው ለእኩልነት፣ ለነፃነት፣ ለኢትዮጵያዊነት ስለሆነ፤ ትግሉ የኢትዮጵያዊያን በሙሉ ነው። ፋኖ የአማራ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ልጅ ነው። እናም አገር አቀፍ የሆነ አደረጃጀትና የትግል ሂደት መከተል አለበት። 

በመጀመሪያም አማራ በሙሉ አንድ ድርጅት፣ አንድ ግብ፣ አንድ ሰንደቅ፣ አንግቦ መስለፍ አለበት። ወደዚያ እየሄደ ነው። አንዳንዶቻችን ቶሎ ለምን አልሆነም በሚል የምንበሳጭ አለን። የፍላጎት ጉዳይና የተጨባጭ እውነታ ጉዳይ፤ የተለያዩ ናቸው። ዛሬ የተወለደን ሕፃን ለምን አይሮጥም ብንል፤ የግንዛቤው ጉድለት ከኛ ነው። ፋኖ የአገር ጉዳይ አሳስቦት ወደ አስፈላጊው ድርጅት መሄድ ከጀመረ ወራቶች አላስቆጠረም። ይልቁን በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ ያስመዘገባቸው ድሎች፤ ሊያስደንቁን ይገባል። እናም የፋኖዎች ወደ አንድ መሰባሰብ እንደሚሳካ በትልቅ ተስፋ እንጠብቅ። የምናደርገው እርዳታ ይጨምር። በያለንበት ይሄ እንዲሳካ እንግፋ። ወይዘሮ የኔዓለም ደስታ ምድሩ ይቅለላትና፤ “ሱሪ ባንገት!” ትል ነበር ስጣድፍ ተመልክታ። ሌሎች ሕይወታቸውን እየገበሩ የሚገፉት ትግል፤ የራሱ የሆነ ሂደትና እድገት አለው። እኛ በቀደድንለት በኩል ለምን አልገባም ብለን አናስብ። ሁሉም ይሆናል! አይቀሬው ድል ይሳካል።

በየመቀመጫዎቻችን ተኮፍሰን፤ ትግሉን መሪ ሆነን፤ ዛሬ ይሄ ለምን አይሆንም! ነገ እንዲህ መሆን አለበት! ከነገ ወዲያ አዲስ አበባ መገባት አለበት! ማለታችን መጥፎ አይደለም። ተቆርቋሪነታችን ያሳያል። ነገር ግን፤ ሌሎችም በያሉበት የየራሳቸውን እያቀዱና እየዶለቱ መሆኑን አንርሳ! ወሳኙ ደግሞ፤ በቦታው ሆነው፣ ሁኔታውን እየተገነዘቡ፣ አስፈላጊና በነሱ ግንዛቤ ትክክለኛ የሚሉትን እያደረጉ፤ ከፍተኛ መስዋዕት በመክፈል ያሉ ፋኖዎች ናቸው። እኛ ልናደርግ የሚገባን ከፍተኛ ጉዳይ፤ ድጋፍ ማድረጉ ላይ ነው። በተለያዩ ፋኖዎች የተወከላችሁ የውጭ አስተባባሪዎች ደግሞ፤ በዚሁ ተቀራርባችሁ ለነሱ መዋሃድ አስፈላጊውን ድጋፍና ግፊት እንድታደርጉ ነው የምማጸናችሁ! እያደረጋችሁ መሆኑን እገምታለሁ፤ ሆኖም በተቻለ መጠን ይፍጠን።

Filed in: Amharic