>

ሐሳቤን በመግለጼ የለወጥኩት…? (በፍቃዱ ኃይሉ)

BefeQadu Z. Hailu“ለምን ትጽፋለህ?” በይፋ “በብዕር ታጋይ” ከሆንኩ ወዲህ በተደጋጋሚ የሚገጥመኝ ጥያቄ ነው። አንዳንዶች፣ ዓላማዬን ለማወቅ፤ ሌሎች፣ መራር ጦሱን እንዳልጎነጭ ለማሳሰብ ነው ይህን መጠየቃቸው። እኔም ለገዛ ራሴ ተመሳሳይ ጥያቄ፣ በተደጋጋሚ ማቅረቤ አልቀረም። የምጽፈው ለውጥ ለማምጣት ነው። ‘ምን ዓይነት ለውጥ አመጣ[ለ]ሁ?’ የሚለውን ወረድ ብለን መልስ እናገኝለታለን።ከዚያ በፊት ግን ከእስር ቤት አሾልኬ ከኔ በፊት ካወጣኋቸው ቁዘማዎቼ በአንዱ ላይ «ለምን እጽፋለሁ?» በሚል ንዑስ ርዕስ ያሰፈርኩትን በድጋሚ ላካፍላችሁ፦

“ጆርጅ ኦርዌል «ገንዘብ ለማግኘት» ከሚደረግ ጥረት ውጪ ጸሐፍት የሚጽፉባቸውን «አራት ትላልቅ መግፍኤዎችን» እንደዘረዘረ አንድ መጽሐፍ ላይ አነበብኩ፡፡ እነዚህ መግፍኤዎች ከተራ ጉራ (‘sheer Egoism’ ማለትም ጎበዝ መስሎ ለመታየት፣ ስለራስ እንዲወራ፣ ወይም ከሞት በኋላ ለመታወስ ለመሳሰሉት) ከመጻፍ ጀምሮ እስከ ፖለቲካዊ ዒላማ (Political purpose ወይም ዓለምን ወደ ሚፈልጉት አቅጣጫ የመግፋት ዕቅድ) ድረስ ሊዘልቁ ይችላሉ። ሌሎቹ መግፍኤዎች ለጥበባዊ ግብ (aesthetic enthusiasm ማለትም ዋጋ የሚሰጡትንና ሰዎች እንዲሰሙት የሚፈልጉትን ነገር በጥበባዊ አቀራረብ የማጋራት ጉጉት)፤ ለታሪካዊ ጥቅም (historical impulse ወይም ስለታሪክ እውነቱን የመለየትና ለወደፊቱ የማስቀመጥ ግብ) የሚደረጉ የምኞት መጻፎች ናቸው፡፡

“የእኔም የመጻፍ አባዜ (ልበለው?) ከእነዚህ የኦርዌል መግፍኤዎች አንዱ ወይም ከፊሉ ወይም ሁሉም ወይም ማንኛውም ሊሆን ይችላሉ፡፡ ወይም ደሞ ነብይ መኮንን በግጥም እንዳለው «ስለሚያመኝና መጻፍ ስለሚያክመኝ» ይሆናል፡፡ እንድ ነገር ግን አምናለሁ፡፡ የቮልቴርን አፍ ተውሼ እምነቴን ልናገር፦ «we can, by speech and pen, make men more enlightened and better» (በንግግር እና ብዕር ሰዎች የነቁና የተሻሉ እንዲሆኑ ማድረግ እንችላለን፡፡)”

‘ጽሑፍ ለለውጥ’(?)

ጸሐፊነት – በተለይ የትችት ጸሐፊነት በሁለት በኩል በተሳለ ቢላዋ እንደመጠቀም ነው። ሌሎችን በሚተቹበት መሥፈርት መልሶ መተቸት ይመጣል። ይህ የጸሐፊነት መንታ ስለት ደግሞ በማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ የበረታ ነው።

በማኅበራዊ ሚዲያ ዘመን ‘ጸሐፊነት’ ቀላል ነው። ነገር ግን እንደሕትመት ሚዲያ የአንድ ወገን የሐሳብ ፍሰት የሚስተናገድበት አይደለም። በማኅበራዊ ሚዲያ አንድ ሰው ለጻፈው አንድ አከራካሪ ሐሳብ እልፍ ምላሽ ይቀበላል። ሌላው ቀርቶ፣ ዛሬ ዛሬ መደበኛው ሚዲያ ላይ ለተስተናገደ አንድ ሐሳብ በማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ (እንደሐሳቡ ሸንቋጭነት) ብዙ ምላሾችን ማንበብ የተለመደ ነው። ይህ ትክክለኛው የሕዝባዊ ተዋስኦ (discourse) ባሕሪ ነው። ከተቻለ – እውነት፣ ካልተቻለ – ስምምነት በዚህ ዓይነቱ የሐሳቦች ፍጭት ነው የሚወለደው።

ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ መጻፍ ስጀምር ያሰፈርኳቸውን በርካታ ሐሳቦችን አሁን ሌላ ሰው ጽፏቸው ባይ በተቃራኒው የምሟገታቸው ዓይነት ሁነዋል። ይህ የምኮራበት ተራማጅነት ነው። በዓመታት የጦማሪነት ሒደት ውስጥ በእጅጉ የለወጥኩት የመጀመሪያው ሰው እኔን – ራሴን ነው።

በፊት፣ በፊት በሐሳቤ የመጣውን ነገር ሁሉ እንደወረደ ነበር የምጽፈው። ነገር ግን በወቅቱ እርግጠኛ የሆንኩባቸው ሐሳቦች በቀላል መከራከሪያ ፉርሽ ሲደ:ረጉብኝ፣ ሁሌም ለምጽፈው ጉዳይ ተቃራኒ ሞጋች ሐሳቦች ሊኖሩ እንደሚችሉ ሳልወድ በግዴ ማገናዘብ ጀመርኩ። ከመጻፌ በፊት ስለምጽፈው ነገር የማውቀው ምን እንደሆነ? የምቃወመው/የምደግፈው [ለ]ምን እንደሆነ? ራሴን መጠየቅ፣ በቅርብ የማገኘውን መረጃ ማገላበጥ እና ሙሉ እርግጠኛ ላልሆንኩባቸው ሐሳቦች አንባቢ እንዲሞላልኝ ክፍተት መተው ጀመርኩ። ይህ ሒደት የትኛውም ዩንቨርስቲ በቀላሉ የማያስተምረኝ ራስን ደግሞ፣ ደጋግሞ የመቅረፅ ሒደት ነው። ሐሳቤን በመግለጼ ያገኘሁት ትልቁ ትሩፋቴ ይኸው ነው።

‘ጽሑፍ ለነውጥ’(?)

የኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሚዲያ በሃይማኖት፣ ብሔር እና ፖለቲካ ጉዳዮች “የጥላቻ መድረክ” እንደሆነ ብዙዎች ይገምታሉ። ነገር ግን እውነታው ተቃራኒውን እንደሆነ ነው አንድ ጥናት የሚጠቁመን። በኦክስፎርድ እና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ባለሙያዎች ከ2007 ጀምሮ ለሁለት ዓመታት የተደረገ ጥናት እንደሚጠቁመው “የጥላቻ” ወይም “አደገኛ” ንግግሮች አንድ በመቶ እንኳ አይሞሉም። ይልቁንም ከአጥኚዎቹ አንዱ የሆኑት Iginio Gagliardone እንደሚገልጹት፣ በማኅበራዊ ሚዲያ ትልቁ ችግር ‘ለቅራኔ መሔድ’ (going against) ነው።

አጥኚው እንደሚሉት “Statements that go against are statements attacking another speaker or a specific group by belittling, provoking, teasing them maliciously, or explicitly threatening them.” («‘ለቅራኔ መሔድ’ የሚለው ምደባ ውስጥ የሚገቡ ንግግሮች ሌላኛውን ተናጋሪ ወይም ቡድን የሚያንኳስሱ፣ በነገር የሚሸነቁጡ፣ በሐሰት የሚወነጅሉ፣ ወይም ደግሞ በዛቻ የሚያስፈራሩ ናቸው።») የሐሳብ ነጻነትን የሚያፍነው መንግሥት ብቻ አይደለም። ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተሰበሰበው ማኅበረሰብ ሐሳብን የመግለጽ ነጻነትን የሚያፍንበት መንገድ ይህ ‘ለቅራኔ የመሔድ’ ልንለው የምንችለው ባሕል ነው።

ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ‘ለቅራኔ መሔድ’ የሚያጠፋው ሁለት ነው፤ ፩ – ራሱን ለቅራኔ ሒያጁን ከሌሎች ጋር ቅራኔ ውስጥ እንዲገባ እንጂ ለተዋስኦ የሚበጅ ሐሳብ እንዳያበረክት ያደርገዋል፣ ፪ – ለቅራኔ የተሔደበትን ጸሐፊ በውይይቱ እንዲቀጥል ወይም ከውይይቱ እንዲማር ተጨማሪ ዕድል አይሰጠውም። ለቅራኔ መሔድ የመጨረሻ ግቡ የተለየ ሐሳብ ያለውን ማባረር እና ተመሳሳይ ሐሳብ የሚያራምዱ እርስ በርስ የማይዳረሱ (mutually exclusive) ብዙ ክበቦችን መፍጠር ነው።

እያንዳንዱ ችግር መፍትሔ ያስተምራል። ከላይ የጠቀስኩትን ‘ለቅራኔ መሔድ’ አጉል ልመድ በአጭሩ ለመክላት ‘በጨዋነት በመጻፍ፣ ከሰዎች እና ቡድኖች ይልቅ ሐሳቦች ላይ በማተኮር፣ ትችቶች ሲጻፉ የሚተ:ቸውን አካል ሳይቀር ለመልስ እና ለውይይት ተሳታፊ የሚሆንበትን ዘለፋ አልባ አጻጻፍ ስልት መከተል’ ይቻላል።

‘ጽሑፍ ለእስር’(?)

ሁለት ግዜ ታስሬያለሁ — መጀመሪያ ለ18 ወራት ዞን ዘጠኝ ጦማር ላይ በጻፍኩት “በሽብር ተጠርጥሬ”፣ ቀጥሎ የአሜሪካ ድምፅ ራዲዮ ላይ ባወራሁት “የአስቸኳይ ግዜ አዋጁን አጥላልተሃል” ተብዬ። ሁለቱንም የታሰርኩት ሐሳቤን በነጻነት በመግለጼ ነው። እነዚህ ክስተቶች መጻፍ እንደዋዛ ስጀምር ወደ አላሰብኩት አቅጣጫ ሕይወቴን ቀይሰውታል። ነገር ግን እስሬ የመጣው ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብቴን ጥቅም ሳላውቅ ወይም በቅጡ ሳላጣምም ቢሆን ኖሮ ዝም ልል እችል ነበር። ነገር ግን ከላይ እንደገለጽኩት የጽሑፎቼ የመጀመሪያ ተጠቃሚ እኔው ራሴ ነኝ። በራሴ መጨከን አልችልም።

ሐሳብን በነጻነት መግለጽ ማለት ለኔ መተንፈስ እንደማለት ነው። ግለሰቦች፣ ማኅበረሰቦች፣ ዓለም በጥቅሉ በተፈጥሮ ላይ የምትሠለጥነው ሐሳብን በነጻነት መግለጽ ሲቻል ብቻ ነው። ሐሳብ በነጻነት የማይገልጹበት ፀጥታ እንጂ ሠላም የለም፤ ኩርፊያ እንጂ እርቅ የለም፤ ድንቁርና እንጂ ዕውቀት የለም።

ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ ነጻነት ለዘላለም ይኑር!

Filed in: Amharic