>

ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ያደረጉት ቆይታ

dr-negaso-gidadaዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ – የመካከለኛው ኢትዮጵያ ታሪክ, የአዲስ አበባ የባለቤትነት ጥያቄና ህገ-መንግስታዊ ልዩ ጥቅም ላይ ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ የሰጡት ምላሽ

1) በመካከለኛው ኢትዮጵያ የነበረው የህዝቦች ታሪክ ምን ይመስላል?

እኔ ልናገረው የምችለው ከአፄ አምደፅዮን ጀምሮ ያሉትን በተለይ ከአለቃ ታዬ መፅሐፍ ያነበብኩትን ነገር ነው፡፡ አፄ አምደፅዮን ከ1314 እስከ 1344 ነበር የነገሡት፡፡ በእሳቸው የንግስና ዘመን ፍልስፍናው ክርስትና ነበር፡፡ በዚህ ክርስትናን የማስፋፋት ዘመቻ “ጋላ” ወንዝ የሚባለውን ተሻግረው እንደነበር ይጠቀሳል፡፡ ይሄ ወንዝ የዛሬው አዋሽ ይሁን ጉራጌና ኦሮሚያ መካከል ያለው ዋቤ ይሁን አይታወቅም፡፡ ይሄን ወንዝ ተሻግረው ዘመቻ ሲያካሂዱ እንደነበር ካገኘኋቸው የታሪክ መዛግብት መረዳት ችያለሁ። በምስራቅ አካባቢም እስከ ቀይ ባህር ድረስ አፋርና ሶማሌ፣ ሐረር አካባቢ ሲንቀሳቀሱ እንደነበር ተዘግቧል፡፡ የሰሜን ኢትዮጵያ የሚባለው እስከ ደብረ ብርሃን ድረስ የነበረው ነው፡፡ የነገስታቱ ማዕከላቸው ደግሞ በየጊዜው ተለዋዋጭ ነበር፡፡ አፄ አምደፅዮን መጫዎችን (ኦሮሞዎች ይሁኑ አይሁኑ አላውቅም) ጎጃም ወስደው እንዳሰፈሯቸው የሚናገሩ መረጃዎች አሉ፡፡ እንደገና ከአፄ ይስሃቅ ዘመነ መንግስት እስከ አፄ ልብነ ድንግል ድረስ ለ200 ዓመታት ኢትዮጵያ በሚባለው አካባቢ ኦሮሞዎች እንደነበሩ አለቃ ታዬ ፅፈዋል፡፡ ኦሮሞዎች የመካከለኛውን ኢትዮጵያ ክፍል ተቆጣጥረው እንደነበረ አስረጂ ከሆኑት መካከል አምቦ አካባቢ አንድ ማዕከል ነበራቸው፤

በ1314 እ.ኤ.አ ማለት ነው፡፡ በሰሜን ሸዋ ከተታ የሚባል አካባቢም የኦሮሞዎች ማዕከል እንደነበረ ተዘግቧል፡፡ (አሁን “ላሎ ምድር” ከሚባለው አካባቢ ጋር ግንኙነት ይኑረው አይኑረው አላውቅም) ነገር ግን በአካባቢው ላሎ የሚባል ሀብታም የአፄ አምደፅዮንን ከብት ጠባቂዎች ወግቶ ወደ ደዋሮ ሸሽቶ፣ የኦሮሞ ታላላቅ አባቶችን እንደወለደም ታሪክ ይነግረናል፡፡ ከልጆቹ መካከል ወሎ፣ ቱለማ፣ መጫ፣ ኢቱ፣ አርሲ፣ ቦረና የመሳሰሉት ልጆች ይገኙበታል። እነዚህ ልጆች ለ200 ዓመት ተባዝተው ዛሬ የሀገር ስም እስከመሆን ደርሰዋል፡፡ በአዋሽ አካባቢም ሸዋ ውስጥ ደዋሮ የሚባል አለ፡፡ ይህ ቦታ ግን የአሁኑ ዳውሮ አይደለም፡፡

በአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት በሚገኘው የረር አካባቢ ዛሬም ድረስ የገዳ ስርአት የሚፈፀምበት “ኦዳነቤ” አለ፡፡ ከተለያዩ አካባቢዎች ኦሮሞዎች ወደ ኦዳነቤ እየመጡ ዳኝነት ያገኙ እንደነበር ተዘግቧል፡፡ እነዚህን የታሪክ ማስረጃዎች ስንመለከት፣በአጠቃላይ ኦሮሞዎች በደቡብ አዋሽን ይዞ በሰሜን እስከ አባይ ድረስ እንደነበሩ መረዳት ይቻላል፡፡ “ጋፋት” የሚባል ህዝብ አባይ አካባቢ ይኖር እንደነበር፣ ጉራጌዎች ደግሞ ጊቤ አካባቢ አሁንም ያሉበት ቦታ እንደነበሩ፣ ጊቤ ማዶ ደግሞ ዳሞት የሚባል ህዝብ እንደነበረ (እነዚህ ሰዎች ጎጃም፣ ወላይታ፣ ወለጋ አካባቢዎች አሉ) የእኔም ቅድመ ዘሮች ዳሞታዎች ናቸው። “ሙጭጮ” የሚባሉ ህዝቦችም በምዕራብ ሸዋ አካባቢ እንደነበሩ ታሪክ ያስረዳናል፡፡ ወደ ወለጋ አካባቢ፡- ገበቶ፣ አጋዲ፣ ታዛ፣ ወረጎ፣ ጋንቃ፣ ማኦ ቡሣሴ የሚባሉ ህዝቦች እስከ 16ኛ መቶ ክ/ዘመን ድረስ እንደነበሩ በታሪክ ይጠቀሳል፡፡ አዋሽ አካባቢ ከኦሮሞዎች ጋር ሃድያዎች ነበሩ፡፡ አዋሽ ሸለቆ ውስጥ ደግሞ አፋር፣ ወርጂ፣ አርጎባ፣ ራያ ነበሩ፡፡ ቀይ ባህር ድረስ ኦሮሞዎች እንደነበሩ በታሪክ ተጠቅሷል፡፡

የኦሮሞ ህዝብ በተለይ ከብት አርቢ ስለነበረ ከብቶች ሲበዙ፣ የቤቱ ታናሽ ልጅ ሰዎችን አስከትሎ ወደ ሌላ አካባቢ ይሄዳል፡፡ ኦሮሞዎች ዘላን አልነበሩም፡፡ ሽማግሌዎች አንድ ቦታ እየተቀመጡ ልጆች ከብቶቻቸውን ሩቅ ቦታ ወስደው ካስጋጡ በኋላ ወደነበሩበት ይመለሱ ነበር፡፡ በዚህ ዓይነት ብዙ ቦታ ደርሰው ሊሆን ይችላል፡፡  እስከ 19ኛ መ.ክ.ዘ ኢትዮጵያ የሚባለው ሀገር እስከ ደብረ ብርሃን የነበረው ነው፤ ከሱ በስተደቡብ የነበረው በኢትዮጵያ ነገስታት ስር አልነበረም፡፡ በዘመነ መሳፍንት ዘመን ደግሞ ሸዋ፣ ወሎ፣ ትግራይ፣ ጎንደር፣ ጎጃም በየራሳቸው መሳፍንቶች የሚመሩ ነበሩ፡፡ እነዚህን ግዛቶች በአንድ ማዕከል ለመጠቅለል ብዙ የደከሙት አፄ ቴዎድሮስ ናቸው፡፡ እሳቸው ሙሉ ለሙሉ ባያሳኩም አፄ ምኒልክም አፄ ዮሐንስ ያማከሉትን ወርሰው ኢትዮጵያን ሲያስተዳድሩ ነበር፡፡

በ19ኛ ክ.ዘመን መጨረሻ ላይ ከሸዋ በኩል ንጉስ ሣህለስላሴ፤ ከሸዋ አካባቢ ወደ ደቡብና ምዕራብ የመስፋፋት ሂደት ነበር፡፡ ታሪክ ፀሐፊዎች እንደሚገልጹት፤ ከእንጦጦ በስተሰሜን አድርገው እስከ ጉራጌ ሀገር ድረስ ወረራዎችን ሲያካሂዱ ነበር፡፡ ወረራ ሲያካሂዱ ቋሚ አገዛዝ አልፈጠሩም፤ዘርፈው ነበር የሚመለሱት፡፡ የዚህ ዓይነት እንቅስቃሴ ነበር በአካባቢው የነበረው፡፡ ወረራዎች ሲካሄዱ ቤቶች ይቃጠሉ እንደነበር፣ ሽማግሌዎችም ህፃናትም እንደሚገደሉ በታሪክ ተመዝግቧል፡፡ የሸዋ ነገስታት በዚህ መንገድ ለመስፋፋት ሲሞክሩ የአውሮፓ ኢምፔሪያሊስቶችም በአካባቢው ቦታ ተሰጥቷቸው ቆንፅላዎቻቸውን ከፍተዋል፡፡

በመካከለኛው ኢትዮጵያ በርካታ የራሳቸው ማንነት ያላቸው ህዝቦች እንደነበሩ ገልጸዋል፡፡  እነዚህ ህዝቦች ዛሬ የት ገቡ? በተለይ ከ16ኛው ክ/ዘመን ጀምሮ ከግራኝ አህመድ ወረራ በኋላ ባለው 50 ዓመት ጊዜ ውስጥ የኦሮሞዎች መስፋፋት ነበረ፡፡ ከምስራቅ የሚስፋፉትን ሱልጣኔቶችና ከሰሜን የሚስፋፉትን ክርስቲያኖች ለመከላከል ነበር የተስፋፉት፡፡ ከጎጃምና ከሸዋ በኩል ወደ ምዕራብ የመስፋፋት ሁኔታ ነበር፡፡ ይሄን ነገር ብዙ ኦሮሞዎች ይክዳሉ፤ በኔ በኩል ግን ተቀባይነት የለውም፡፡ ኦሮሞዎች ሲስፋፉ በ“ጉዲፈቻ”፣ በ“ሚዲቻ” እና በጋብቻ ሥርአት የደረሱባቸውን ህዝቦች ኦሮሞ ያደርጉ ነበር። ለምሳሉ ዳሞታና ሙጭጮ የተባሉ ህዝቦችን ካስገበሩ በኋላ በሚዲቻና በጉዲፈቻ ስርአት ኦሮሞ አድርገዋቸዋል፡፡ “ሚዲቻ” በሚባለው ስርአት አንድ ክፍለ ህዝብን እንደ ወንድም በመቀበል እንደ ሌላው ኦሮሞ መብት ይጎናፀፋል፡፡ በጋብቻ ስርአትም ኦሮሞ የሆኑ አሉ፡፡ ኦሮሞዎች ዘመድ አያገቡም፡፡ እስከ 12 ትውልድ ቆጥረው ነው የሚጋቡት በዚህ የጋብቻ ስርአት ከሌላ ህዝብም ይጋቡ ነበር፡፡ በዚህ መንገድ በጊዜ ሂደት ያላምዷቸውና ቋንቋና ባህሉን እንዲቀበሉ ይሆናሉ፡፡ ብዙዎቹ የተዘረዘሩት ህዝቦች በዚህ ዓይነት ኦሮሞዎች ሆነዋል፡፡ ከደጋው አካባቢ ሸሽተው ወደ ሸለቆዎች ገብተው ዛሬም ድረስ ማንነታቸው ሳይቀየር የቆዩ ህዝቦች አሉ፡፡ አብዛኞቹ ግን ኦሮሞዎች ሆነዋል፡፡ እነዚህ ከኦሮሞ የተዋኃዱ ህዝቦች ዛሬም ድረስ የሚኖሩበት ቦታ በስማቸው ይጠራል፡፡ ይሄ ማስታወሻ ይሆናቸዋል፡፡

2) አዲስ አበባ እና ኦሮሞዎች በታሪክ ያላቸው ግንኙነት መቼ ነው የሚጀምረው?

አስቀድሜ እንዳልኩት ንጉሥ ሣህለ ሥላሴ ተደጋጋሚ የመስፋፋት ወረራ ያደርጉ ነበር። የእሣቸው ልጅ ኃይመለኮትም ብዙም ባይሆን እንቅስቃሴ ያደርጉ ነበር፡፡ በኋላ የኃይለመለኮት ልጅ አፄ ምኒልክ ወደ ደቡብ ወረራቸውን ከአካሄዱ በኋላ ማዕከላቸውን ከደብረ ብርሃን አካባቢ ወደ እንጦጦ ያዘዋውራሉ፡፡ ዋና ከተማቸውን እንጦጦ ላይ ያደርጋሉ፡፡ በአካባቢው ያሉት ኦሮሞዎች ነበሩ፤እነሡን ገባር ያደርጋሉ፡፡ በሌላ በኩል የውጭ ዲፕሎማቶች መምጣት ጀምረው ነበር፡፡ ለነዚህ ዲፕሎማቶች ከእንጦጦ በታች ቦታ መርጠው ይመጣሉ። አሁን የአሜሪካ፣ ጀርመን፣ እንግሊዝ፣ ሩሲያ ኤምባሲ ቦታዎች በዚህ መንገድ የተሠጡ ናቸው፡፡  6 ኪሎ፣ 4 ኪሎ፣ ፒያሣ፣ ካዛንቺስ፣ መስቀል አደባባይ ድረስ ያሉት ቦታዎች ከነዚህ ሂደቶች በኋላ ነበር የተያዙት፡፡ ኦሮሞዎች ፊኒፊኔ ይሉ የነበረው ፍልውሃ ስለነበር ነው፡፡ በፍልውሃ አካባቢ የገዳ ስርአትና የኢሬቻ ስርአት የሚያካሂዱበት ጨፌ ነበረ። በተለይ አሁን የምኒልክ ቤተ መንግስት የምንለው፣ አሁን ጠ/ሚኒስትሩ ያሉበት አካባቢ ‹‹ዳሊቲ›› ይባል ነበር፡፡ እዚያ ቦታ ላይ የገዳ እና ኢሬቻ ሥርዓት ይደረግ ነበር፡፡ አፄ ምኒልክ ቤተ-መንግስታቸውን አሁን ወዳለበት ያመጡት ለፍልውሃ ቅርብ ለመሆን ነው፤ እንጂ ቦታው ላይ ኦሮሞዎች ከ16ኛው ክ/ዘመን ጀምሮ ይኖሩበት ነበር።

3) ከዚያ በፊት የነበሩት ህዝቦችስ የትኞቹ ናቸው?

“የላሎ” ታሪክ የነበረው በዚሁ አካባቢ ነው። ሰሜን ሸዋ አሁን ላሎ ምድር ተብሎ የሚጠራው አካባበቢ ለአዲስ አበባ በእጅጉ ቅርብ ነው፤ ስለዚህ አዲስ አበባ አካባቢ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ኦሮሞዎች እንደነበሩ የሚታወቅ ነው ማለት ነው፡፡ ቦታውን ምኒልክ ሲይዙት ብዙ የጎሣ መሪዎች ተገድለዋል። የጎሣ መሪዎቹ ተገድለው መሬታቸው ለቤተ-መንግስት ሰዎች፣ ለውጭ ሀገር ዲፕሎማቶች ነው የተከፋፈለው፡፡ በህይወት የተረፉት ሸሽተዋል፡፡ ሆን ተብሎ በማፈናቀልም ወደ አርሲ፣ ባሌ አካባቢ እንዲሰፍሩ የተደረጉ አሉ፡፡ ባህሉና ቋንቋውም በክርስትና መስፋፋት ጠፍቷል፡፡

የህዝቦች በታሪክ ሂደት መዋዋጥ ጋር ተያይዞ “እዚህ ቦታ ላይ እኔ ነኝ ቀደምት” የሚለው ሙግት ምን ያህል ያዋጣል? በቅርብ ጊዜ የሚታወስ ከሆነ፣ በተለይ ህዝቦች ማንነታቸው ሳይበረዝ (ሣይዋሃድ) ከተቀመጠ እንዲሁም ቦታው መቼ እንደተወሰደበት ከታወቀ ዕውቅና መስጠቱ ጠቃሚ ነው፡፡ የታሪክ አሻራዎች የሚታወሱ ከሆነ ለዚያ ማስታወሻ ማኖር ይጠቅማል እንጂ አይጎዳም፡፡ ለምሣሌ የቦታ ስም ወደነበረበት ይመለስ ሲባል የቦታውን ባለቤት እውቅና ለመስጠት እንጂ ለታሪክ ቁርሾ መሆን የለበት። በዚያ ቦታ የሰፈረውንም ተነስ ማለት አይቻልም፤ ዋናው ነገር ቦታው ላይ ለቀደምቶቹ እውቅና መስጠቱ ነው፡፡ ሃውልት መትከል፣ ስም መመለስ የሚባለው ለማስታወስ ያህል ነው የሚሆነው። እዚህ ጋ የሮዴሽያና የደቡብ አፍሪካን ምሣሌ መጥቀስ ይቻላል፡፡ ነጮች ወደ አካባቢዎቹ ሄደው፣ ከነባሮቹ ቦታዎቹን ነጥቀው፣ ብዙ አስከፊ ሁኔታ ፈጥረው ነበር፡፡ አሁን ግን በፍትሃዊነት አብረው ይኖራሉ፡፡ ከመሬቱም አብረው ይጠቀማሉ፡፡ ይሄ ነው መሆን ያለበት፡፡

ህገ መንግሥቱን በማርቀቅ ሂደት እርስዎም ተሳትፈዋል፡፡ በአንቀፅ 49(5) ላይ የኦሮሚያ ልዩ ጥቅም በአዲስ አበባ ላይ እንዴት ነው የተካተተው?  እንደሚታወቀው ከ1983 እስከ 1987 ዓ.ም ድረስ የሽግግር መንግስት ወቅት ነበር፡፡ በነዚህ ጊዜያት ውስጥ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ነበሩ፡፡ ከግንቦት 20 ቀን 1983 እስከ ሰኔ 24 ቀን 1983 ድረስ ለአንድ ወር ያህል ጊዜያዊ መንግስት ተቋቋመ፡፡ ይህ ጊዜያዊ መንግስት ከሰኔ 24-28 የተካሄደውን የሠላም ኮንፈረንስ ሲጠራ በርካታ ታጣቂዎች ተሳትፈው የነበረ ሲሆን ያልተሳተፉት ኢህአፓ፣ መኢሶን እና ኢሰፓ ነበሩ፡፡ ሌሎች በሙሉ ተሳትፈዋል። ግለሰቦች፣ ምሁራንና የሃይማኖት መሪዎችም ነበሩ። በዚህ ኮንፈረንስ ቻርተር ተዘጋጅቶ ተፈረመ። የሽግግር መንግስቱ ነሐሴ 1983 ተመሰረተ፡፡ በ1984 በሽግግር መንግስቱ አዋጅ ቁጥር 7/1984፣ በነጋሪት ጋዜጣም ጥር 5 ቀን 1984 ዓ.ም ነው ታትሞ የወጣው፡፡  በዚህ አዋጅ አንቀፅ 8 ላይ የክልሎች ማቋቋምን የተመለከተ አለ፡፡ በዚህ አዋጅ ላይ ብዙ ጊዜ የምትጠቀስ አንቀፅ አለች፡፡ አንቀፅ 3 ንኡስ አንቀፅ 2 ሀ(4) ላይ በክልል 13 (ሀረር) እና 14 (አዲስ አበባ) ላይ የኦሮሞ ብሄራዊ ጥቅምና ፖለቲካዊ መብት የተጠበቀ ይሆናል ይላል፡፡ ዋናው መነሻ ይህቺ አንቀፅ ነች፡፡

4) ይሄ ጥያቄ መጀመሪያ የተነሳው በማን ነበር?

እንግዲህ በሰላም ኮንፈረንሱ ተሳታፊ የነበሩት ነፃ አውጪ ድርጅቶች ስለነበሩ የተለያዩ ሃሳቦች ይንፀባረቁ ነበር፡፡ በተለይ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) እና የኢስላሚክ ኦሮሞ ነፃነት ግንባር እንዲሁም “ቶክቹማ” የሚባል ባሌ፣ አርሲና ሐረር አካባቢ የሚንቀሳቀስ ድርጅት ነበር፡፡ ሌሎችም የነፃነት ድርጅቶች ነበሩ በሂደቱ፡፡ በታሪክ የተዛቡ ሁኔታዎች እንዲስተካከሉ ለማድረግ፣ የተገፈፈ መብት እንደገና እንዲመለስ የሚሉ ጥያቄዎች ነበሩ። ይሄ ሁሉ ባለበት ርዕሰ ከተማ የት ይሁን ሲባል፣ አዲስ አበባ ትሁን የሚል ስምምነት ላይ ተደረሰ። ድሬደዋ ደግሞ የንግድ ከተማ ስለሆነች ለፌደራል መንግስት ታስፈልጋለች ተብሎ እንዳለ እንድትቀጥል ስምምነት ተደረሰ፡፡  በተለይ “ኦነግ” በሸዋ ነገስታት መስፋፋት የኛ ህዝብ መብት ተገፍፏል፤ ስለዚህ መብታችን ይመለስ፤ቢያንስ በፖለቲካና በኢኮኖሚ ረገድ ኦሮሞ በፊንፊኔ ላይ መብቱ ይጠበቅ እንዲሁም ሃረርም በኦሮሚያ መካከል ስለሆነች በተመሳሳይ የኦሮሞ መብት ይጠበቅ የሚል ጥያቄ አንስቶ ነበር፡፡ እስካሁን ድረስ በሐረር አስተዳደር የኦህዴድ ተሳትፎ አለ፡፡  የሐረር ጉዳይ ግን በህገ መንግስቱ ላይ የለም… አዎ! በኋላ ለምን እንደቀረ ባላውቅም ቀርቷል፡፡  በኋላስ የአዲስ አበባ ጉዳይ እንዴት ህገ መንግስቱ ላይ ተደነገገ? እንደሚታወቀው የህገ መንግስት አርቃቂ ኮሚሽን አቋቋምን፡፡ በዚህ ኮሚሽን ውስጥ 15 የተለያዩ ህዝባዊ ድርጅቶች ማለትም ማህበራት ነበሩ፡፡ ከሽግግር መንግስቱ ተወካዮች ም/ቤት ደግሞ 7 ሰዎች ነበሩ፡፡ ከነዚህ 7 ሰዎች ደግሞ ሁለት ብቻ ነበርን ፤የኢህአዴግ ሰዎች፡፡ እኔ እና ከኢህዴን አቶ ዳዊት ዮሐንስ ነበርን በዚህ ኮሚሽን ውስጥ ህውሓት ተወካይ አልነበረውም፡፡ ሌሎች 7 ግለሰቦች ደግሞ ከም/ቤቱ ውጪ ባሉ የፖለቲካ ድርጅቶች የተወከሉ ነበሩ፡፡ በጠቅላላው 27 ሰዎች ነበርን በኮሚሽኑ ውስጥ፡፡

መጀመሪያ ያደረግነው 75 የተለያዩ ጥያቄዎችን አዘጋጅተን በኢትዮጵያ ውስጥ ላሉ 23 ቀበሌዎች ለህዝብ በተንን፡፡ ከጥያቄዎቹ ውስጥ ለምሳሌ “የፌደራል ስርአት ነው ወይስ አሃዳዊ ስርአት የምትፈልጉት?” የሚል ለህዝቡ ይነበባል፡፡ እጅ ያነሳሉ፤ ይቆጠራል፤ አብላጫው ቁጥር ይያዛል፡፡ በዚህ ሂደት ነበር የተጠናቀረ መረጃ የተሰባሰበው። ያ መረጃ በኮሚሽኑ ከታየ በኋላ ኤክስፐርቶች ይገመግሙታል፡፡ ከዚያ እንደገና ሃያ ሰባታችን እንከራከርበታለን፡፡ በዚህ ሂደት እንደማስታውሰው፤ በሁለት ጉዳዮች መስማማት አልቻልንም ነበር። እነዚህም አንቀፅ 39 እና የመሬት ጉዳይ ናቸው። በነዚህ ሁለቱ ላይ እስከ መጨረሻውም አልተስማማንም ነበር፡፡ በኋላ ጉዳዩ ለህዝብ ተወካዮች ነበር የቀረበው፡፡  በአዲስ አበባ የኦሮሚያ ልዩ ጥቅም ላይ የተለየ አቋም አልቀረበም ነበር?
በአርቃቂ ኮሚሽኑ በኩል ችግር አልነበረም፤ ሁሉም የተቀበለው ጉዳይ ነበር፡፡ ምክንያቱም ቀድሞ በወጣው አዋጅ ላይ ስለነበርና የኦሮሞ ድርጅቶች ዋነኛ ጥያቄም ስለነበረ መከራከሪያ አልቀረበም ነበር።

በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባላት በጉዳዩ ላይ የቀረቡ መከራከሪያዎች ነበሩ? እኛ ሚያዚያ 19 ቀን 1986 ዓ.ም የተወያየንበትን ለም/ቤቱ አቀረብን፡፡ ተወካዮች ም/ቤት ከሚያዚያ 25 ጀምሮ ለ12 ቀናት ተወያይቶበታል፡፡ በወቅቱ ይህቺ የልዩ ጥቅም ጉዳይ በአብላጫ የድምፅ ውሳኔ ነበር ያለፈችው፡፡ ጉባኤው በ507 ድጋፍ እና በስድስት ሰዎች ድምፀ ተአቅቦ ነው ያፀደቀው፡፡ በወቅቱ አንቀጹን የተቃወመ የለም፡፡ በወቅቱ የተወካዮች ም/ቤት 12 ቀን ከተወያየበት በኋላ 545 ጉባኤዎች ተመረጡ፡፡ 42 የግል ተሳታፊዎች ነበሩ፡፡ የዚህ የህገ መንግስት ጉባኤ መክፈቻ ጥቅምት 18 ቀን 1987 ነበር፡፡ እስከ ህዳር 29 ቀን 1987 ዓ.ም ነበር የተካሄደው፡፡ በመጨረሻም ህዳር 29 ቀን 545 ሰዎች የፈረሙበት ህገ መንግስት ፀደቀ፡፡ ይሄ ሲደረግ በረቂቁ ላይ ህዝበ ውሳኔ አልተደረገበትም፡፡

ይሄ ህገ መንግስት ሲፀድቅ ረቂቁ ከተዘጋጀ በኋላ ህዝቦች በሚፈልጉት መንገድ ስለመዘጋጀቱ ራሳቸው ህዝቦች በድጋሚ እንዲገመግሙት አለመደረጉ፣ በህገ መንግስቱ አፀዳደቅ ላይ እንደ ስህተት የምመለከተው ጉዳይ ነው፡፡ ሌላኛው የህገ መንግሥቱ ድክመት እነ ኢህአፓ፣ መኢሶን፣ ኢሠፓ በሂደቱ ተሳታፊ ያለመሆናቸው ነው፡፡

በጉባኤው መድረኩን የምንመራው እኔ፣ አቶ አዲሱ ለገሰና አቶ አባተ ኪሾ ነበሩ፡፡ በወቅቱ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ያፀደቀውን ረቂቅ ህገ መንግስት ለጉባኤው ያስረከቡት የአቶ መለስ ምክትል የነበሩት የሽግግር መንግስቱ ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ፍቃዱ ገዳሙ ነበሩ።

Filed in: Amharic