>

አራት የኦፌኮ አመራሮች ተፈረደባቸው (ጌታቸው ሺፈራው)

“ሞት በእኛ ይብቃ!
ደም ደም ይሸታል ቤቱ፣ የፍርድ ቤቱ! ” 
የእነ በቀለ ገርማ አዲሱ የነፃነት መዝሙር

አራት የኦፌኮ አመራሮች ተፈረደባቸው

~የኦፌኮ አመራሮችን ደግፈው ያጨበጨቡ የግንቦት 7 ተከሳሾች ተፈርዶባቸዋል

(ጌታቸው ሺፈራው)

ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ በተቀሰቀሰው ህዝባዊ ንቅናቄ የተከሰሱት አራት የኦፌኮ አመራሮች ዛሬ ጥር 3/2010 በችሎት መድፈር ቅጣት ተወስኖባቸዋል። በእነ ጉርሜሳ አያኖ ክስ መዝገብ የተከሰሱት ጉርሜሳ አያኖ፣ ደጀኔ ጣፋ፣ አዲሱ ቡላላ እና በቀለ ገርባ በመከላከያ ምስክርነት የጠቀሷቸው እነ ለማ መገርሳ እንዲሁም በእስር ላይ የሚገኘው አንደየዓለም በምስክርነት እንዳይቀርቡ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ብይን በሰጠበት ወቅት ተቃውሞ በማሰማታቸው ችሎት ደፍራችኋል በሚል እያንዳንዳቸው 6 ወር ተፈርዶባቸዋል።

ፍርድ ቤቱ ” በሚረባና በማይረባ ጉዳይ የመንግስት ባለስልጣናት ለምስክርነት መቅረብ የለባቸውም” በሚል ባለስልጣናቱ በምስክርነት እንዳይቀርቡ ውድቅ ያደረገ ሲሆን አቶ በቀለ ገርባ “በሚረባና በማይረባ እያላችሁ የምትጠቀሙት ቃል ከእናንተ የሚጠበቅ አይደለም” ማለታቸውን ችሎቱ የታዘቡ ገልፀዋል። አቶ ደጀኔ ጣፋ በበኩላቸው “አቃቤ ህግ አመራሮችን ጠርቶ አስመስክሮብናል። እኛ አመራሮችን በምስክርነት ስንጠራም መመስከር የለባቸውም ሊባል አይገባውም” ሲሉ በችሎቱ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል።

ተከሳሾቹ “ደም ደም ትሸታላችሁ፣ 26 አመት ሙሉ የኦሮሞን ህዝበ ገድላችኋል፣ 26 አመት ሙሉ በኢትዮጵያ ህዝብ ደም ተጨማልቃችኋል፣ ሞት በእኛ ይብቃ ” ሲሉ እንደተናገሩና እንደዘመሩም ታውቋል። አመራሮቹ በፍርድ ቤቱ ውሳኔ ተቃውሞ በማሰማታቸው በችሎት መድፈር በተፈረደባቸው ወቅት ፍርድ ቤቱ ሲያነብ አንሰማም ብለዋል።

በእነ በለጠ ክስ መዝገብ በግንቦት 7 የተከሰሱት 3 ተከሳሾችም፣ እነ ጉርሜሳ ሲፈረድባቸው አጨብጭባችኋል በሚል በችሎት መድፈር 3 ወር ተፈርዶባቸዋል። 3 ተከሳሾች “ለምን አጨበጨባችሁ?” ተብለው በፍርድ ቤት ሲጠየቁ “ወንድሞቻችን ስለሆኑ ነው” ብለው መልስ መስጠታቸው ታውቋል። ከችሎት ወጥተው የእስረኞች ጊዜያዊ ማቆያ የነበሩ እስረኞችም በኦሮምኛ ሲዘምሩ ተደምጠዋል። በአማርኛም “ሞት በእኛ ይብቃ! ደም ደም ይሸታል ቤቱ፣ የፍርድ ቤቱ! ” እያሉ ሲዘምሩ ተሰምተዋል።

Filed in: Amharic