>
5:21 pm - Tuesday July 21, 1457

እየሸሹ ትግል (ዘምሳሌ)

እየሸሹ ትግል

ዘምሳሌ


የጊዜው ፈሊጥ  ድል
የሰው ልጅ   በዘሩ በሀገሩ ሲገደል
በድኑም  በዶዘር  በመረገጥ ሲጣል
አንተ ቤተመንግሥት በግብዣ ስትፎልል

በሚዲያም ደጃፍ ሀሰትን ስትዘራ
በመደመር ስሌት በውሸት ስትሠራ
ካባ ለብሰህ ግደል ስምህም ይጠራ
ቀኑ እስኪመጣብህ ዋናው ያንተ ተራ

መግደል መሸነፍ ነው  ብለህ እያወራህ
ቤተስኪያን መስጊዱን ሲፈርስ ዝምብለህ
ህፃን ሽማግሌ ባልቴትን ጨምረህ
ገደል  ሲከቷቸው  በየቀኑ እያየህ

ስንቱ እየተራበ ስትጨፍር ዳንኪራ
በእርዳታ እየኖርክ መዝናኛ ስትሰራ
ፖርክ ልማት ብለህ  እድገት ሲወራ
ህዝቡ ሲፈናቀል በየሁሉ ስፍራ

ፍላጎትህ ሞልቶ ህልምህም  ተሳክቶ
ጭንቀት ሆኖ እያለ  ወንጀል  ተበራክቶ
ሀገር  በየቀኑ ጩኸቷ በርክቶ
አንተን ያደነዘህ አዕምሮ አሳጥቶ
የቱ አዚም  ይሆን ውስጥህ  ያለው ገብቶ

ያፈዘዘህ እንደዚህ  የደረብከው ካባ
በድግስ   ተጠምደህ ህዝብ ግን  ሲያነባ
በኑሮ ውድነት  ግራ እየተጋባ
የሀገር ባንክ ሲዘረፍ በታቀደ ሌባ

ካባ ለብሰህ ግደል  ህዝቡን አጎሳቁል
በቋንቋው ገድበህ ሀገርንም  አሰጥል
የሚፈሰውም ደም ሆኖ በሜዳው ጠል
ትንሽ የማይገድህ ይሄ ሁላ በደል

የእምነት በር ጨብጠህ ለጊዜው ቢመስልህ
ስዩመ እግዚአብሔር  እስከመባል ደርሰህ
ላሻግራችሁ ስትል  ሙሴያችን ተብለህ
ለምራት ያልሆነልህ በስልጣንህ ሆነህ

የስመኘሁ ነፍስ የእነምባቸው ልጅ እምባ
የአሳምነው  ፅጌ የሰዐረ ደባ
የወለጋው ወንጀል ጨምሮ  አዲስ አባ
ደቡብ ምስራቅ ሰሜን በየሁሉ አምባ

ውሸት ስታሰብክ ብልፅግና ብለህ
የሰው ነፍስ ከሆነ የስልጣን መቆያህ
የተነበዩልህ የእምነት ፖስተሮችህ
ደጋግመህ ስትምል ላሻግራችሁ ብለህ

የተሰጠህ አደራ  ቃል ኪዳን ስትገባ
በአድናቂዎችህ ዙሪያ ተብሎልህ ወሸባ
በስመኝ ቀድሰህ ሀገር ቤት ስትገባ
ሰው በዘር ሲገደል ስታፈስ የአዞ  እምባ

በመለስ ድርጅት በስለላው ተቋም
ወንጀልን ስትሰራ ንፁሀን ስታስለቅም
የታጠብክበት ደም ቢሆን የሚያሰጥም
የግፉአኑ ነፍስ  መች እንዲህ ልተክርም

እየሸሸህ ታገል  ህዝብ አላልቅ ብሎሀል
የኛ ኢትዮጵያዊነት መቼስ  ይገባሀል
አይቀር የህዝብ እምባ በቁምህ ያንቅሀል
እመነኝ  አትዘልቅም   ቀን ተቆጥሮብሀል!
ልክ እንደ ጋዳፊ ሜዳ ይጎትቱሀል

Filed in: Amharic