>

እንዳንግባባ ተረግመን ይሆን? ወይስ ማህበረሰባዊ ግራ መጋባት? (ያሬድ ሀይል ማርያም)

እንዳንግባባ ተረግመን ይሆን? ወይስ ማህበረሰባዊ ግራ መጋባት?
ያሬድ ሀይል ማርያም
በታሪኮቻችን ላይ አንግባባም፣
በባንዲራችን አንግባባም፣
በቤሔራዊ መዝሙራችን አንግባባም፣
ስለ ሀገር ባለን ትርጉም እና ግንዛቤ ላይም አንግባባም፣
በመብቶቻችን እና ነጻነቶቻችንም ላይ አንግባባም፣
በፖለቲካ አመለካከታችንም አንግባባም፣
አገር እንዴት ይገንባ በሚለውም ላይ አንግባባም፣
በሕገ መንግስቱም ላይ አንግባባም፣
በመንግስት አወቃቀ ላይ አንግባባም፣
በቋንቋ አጠቃቀማችንም ላይ አንግባባም፣
በክልል አጥሮቻችንም ላይ አንግባባም፣
በሃይማኖቶቻችንም ዙሪያ አንግባባም፣
በባህል እሴቶቻችንም ዙሪያ አንግባባም፣
በታሪክ ባለውለተኞቻችን እና በጀግኖቻችንም ማንነት ላይ አንግባባም፣
በብሔር ማንነት ትርክቶቻችንም ላይ አንግባባም፣ 
በኢትዮጵያዊነታችንም ላይ አንግባባም፣
በቅርሶቻችንም ላይ አንግባባም፣
የነገዋ ኢትዮጵያ ምን ትምሰል በሚለው ላይም አንግባባም፣
የእርግማኑን ነገር ወደ ጎን ልተወው እና በማህበረሰባችን ውስጥ የሚታየውን ግራ መጋባት በቅጡ ብንመረምረው መልካም ነው። እነዚህ አለመግባባቶች በቅጡ ካልተያዙ እና በአግባቡ ምላሽ ካላገኙ በመካከላችን ያሉት ክፍተቶች እየሰፉ ገደል ይሆናሉ።
በገደሎች ማዶና ማዶ እየተቧደነ የቆመ ማህበረሰብ ደግሞ አገር ሊገነባ አይችልም። በአገራዊ ጉዳይ በተለያዩ ሚዲያዎች የሚስተዋሉት ውይይቶችም የዕለት ተዕለት ክስተቶች ላይ ነው ጊዜያቸውን የሚያጠፉት እንጂ እነዚህን መሰረታዊ የማህበረሰቡን ችግሮች ለመፍታት በሚያስችሉ ውይይቶች ላይ ሲሰሩ አይስተዋልም።
ጎበዝ ሳይረፍድ ብንነቃ፤ ሳይዘገይ በችግሮቻችን ዙሪያ በቅንነት እና በእውቀት ላይት ተመስርተን ብንወያይ፤ ገደሉም ሳይሰፋ ክፍተቱን ብንገጥመው ይበጃል። የመደመር ዘፈን ብቻውን በቂ አይዸለም።
Filed in: Amharic