>
5:13 pm - Wednesday April 18, 4103

ይህ ሰልፍ፡ ዶ/ር አብይን ለመቃወም ወይም ለመጠየቅ? ኦሮማራን ለማጠናከር ወይስ ለማፍረስ? (ስዩም ተሾመ)

ይህ ሰልፍ፡ ዶ/ር #አብይን ለመቃወም ወይም ለመጠየቅ? #ኦሮማራን ለማጠናከር ወይስ ለማፍረስ?
ስዩም ተሾመ
* ኢትዮጲያ ውስጥ መሬት የህልውና መሠረት ነው፡፡ የመሬት ባለቤትነትና ያለመፈናቀል መብት ከነዋሪዎቹ ባህልና ማንነት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ በየትኛውም አከባቢ ከመሬቱ የተፈናቀለ አርሶ-አደር ከስሩ እንደተነቀለ ዛፍ ነው!!!
 
 በተለያዩ የአማራ ክልል ከተሞች ሰላማዊ ሰልፎች ተካሄደዋል፡፡ በሰልፉ የተላለፉት መልዕክቶች ለብዙዎች ጠብ-አጫሪ፣ ፀረ-አብይ፣ አክራሪነት እና ፀረ-ህገመንግስት፣… በተለይ ደግሞ #ፀረ_ኦሮማራ ሊመስሉ ይችላሉ፡፡ በእርግጥ አንዳንድ መፈክሮች አግባብ ናቸው ለማለት ይከብዳል፡፡
ሆኖም ግን ሰላማዊ ሰልፉ ሆነ መልዕክቶቹ ከሌሎች ህዝቦች ጋር ፀብ ለመጫር፣ የዶ/ር አብይን አመራር ለመቃወም ወይም ህገ-መንግስቱን ለመጣስ አይደለም፡፡
ከሁሉም በላይ ደግሞ የኦሮማራ ጥምረትን የሚፃረር አይደለም፡፡ ከዚያ ይልቅ የአማራ ህዝብ መብትና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ፣ ህገመንግስቱ በአግባቡ እንዲተገበር፣ እንዲሁም የኦሮማራ መሠረት  እንዲጠናከር፣ የዶ/ር አብይ አመራርም በዚህ ረገድ የሚጠበቅበት ድርሻና ሃላፊነት ለመጠየቅ የተደረገ ነው፡፡ ይህን በአግባቡ ለመረዳት ስለ ኦሮማራ ጥምረት በቂ ግንዛቤ ሊኖረን ይገባል፡፡
የኦሮ-ማራ ጥምረት መሬት ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ “መሬት” የሚለው ቃል፤ 
አንደኛ፦ የሁለቱ ህዝቦች ጥምረትና ትብብር በተጨባጭ እውነታ ላይ የተመሠረተ መሆኑን ያሳል፣ ሁለተኛ፦ የኦሮማራ ጥምረት መሠረቱ የሁለቱ ህዝቦች የመሬት ባለቤትነትና ተጠቃሚነት ላይ የቆመ መሆኑ ነው፡፡ እስኪ ወደ 2008 ዓ.ም ተመለሱና የኦሮ-ማራ ጥምረት በተግባር የተጠነሰሰበትን ሁኔታ ለማስታወስ ሞክሩ፡፡ በ2008 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል ለተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመፅና ተቃውሞ መነሻ ምክንያቱ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ነው፡፡ ይህ ማስተር ፕላን በአዲስ አበባ ዙሪያ የሚገኙ የአሮሞ አርሶ አደሮችን በልማት ስም በማፈናቀል የእርሻ መሬታቸዎን ለመቀራመት የተዘጋጀ መሆኑ እርግጥ ነው፡፡
በሐምሌ 2008 ዓ.ም በጎንደር ህዝባዊ አመፅና ተቃውሞ የተቀሰቀሰበት ምክንያት የወልቃይትና ፀገዴ ማንነት ኮሚቴ አባላት አፍኖ ለመውሰድ የተደረገው ሙከራ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ የኮ/ል ደመቀ ዘውዴ #የአልሞት_ባይ_ተጋዳይነት በክልሉ ለተቀሰቀሰው አመፅና ተቃውሞ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል፡፡ የማንነት ጥያቄ የተነሳበት መሠረታዊ ምክንያት የህወሓት አፓርታይድ ስርዓት በወልቃይትና ፀገዴ የሚኖሩ አማራዎችን ከመሬታቸው እያፈናቀለ፣ በምትኩ የራሱን የቀድሞ ታጋዮች በማስፈሩ ነው፡፡
ኢትዮጲያ ውስጥ መሬት የህልውና መሠረት ነው፡፡ የመሬት ባለቤትነትና ያለመፈናቀል መብት ከነዋሪዎቹ ባህልና ማንነት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ በየትኛውም አከባቢ ከመሬቱ የተፈናቀለ አርሶ-አደር ከስሩ እንደተነቀለ ዛፍ ነው፡፡ ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ በኦሮሚያ የተነሳው ህዝባዊ አመፅና ተቃውሞ፣ ከወልቃይትና ፀገዴ፣ እንዲሁም ከቅርብ ግዜ ወዲህ በራያ የተነሳው የማንነት ጥያቄ መነሻ ምክንያቱ የመሬት ባለቤትነትና ያለመፈናቀል መብት ጋር በቀጥታ የተቆራኘ ነው፡፡ በ2008 ዓ.ም ጎንደር ላይ “የኦሮሞ ደም የእኛም ደም ነው” ብለው የወጡበት ምክንያት ሁለቱ ህዝቦች የጋራ ጥያቄና ጠላት ስላላቸው ነው፡፡ በአጠቃላይ የኦሮማራ ጥምረት የተመሠረተው መሬት ላይ ነው፡፡ ይህን መሠረት አድርጎ የተፈጠረው ጥምረትና ትብብር የህወሓትን የበላይነት ገርስሶታል፡፡ ነገር ግን ህወሓት የዘረጋው የአፓርታይድ ስርዓት የፖለቲካ ስልጣን ለመቆጣጠር ብቻ አይደለም፡፡
ህወሓት የፖለቲካ ስልጣኑን የተቆጣጠረበት መሠረታዊ ምክንያት የኢኮኖሚ ብዝበዛ፣ በተለይ የህልውና መሠረት የሆነውን መሬት ለመቀራመት ነው፡፡ ህወሓት ወደ ስልጣን እንደመጣ የወልቃይትና ራያን መሬት፣ የአፋር የጨው ማዕድን ተቀራመተ፡፡ በመቀጠል የጋምቤላ እና የአዲስ አበባ መሬትን ዘርፈ፡፡ የአዲስ አበባን መሬት ተቀራምቶ ከጨረሰ በኋላ በማስተር ፕላን ሰበብ የኦሮሞ መሬትን ለመቀራመት ሲመጣ ታላቅ ቁጣ ተቀሰቀሰ፡፡ የተጠራቀመ ብሶት ያለበት የወልቃይትና ፀገዴ ህዝብ አልሞት-ባይ-ተጋዳይነት በአማራ ክልል የለኮሰው አመፅና ተቃውሞ በኦሮሚያ ከነበረው ጋር ሲጣመር የኦሮማራ ጥምረት ተወለደ፡፡
የኦሮማራ ጥምረት የህወሓትን የበላይነት አስወግዷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በኦሮሚያ ለተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመፅና ተቃውሞ መነሻ የሆነውን የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን አስቀርቷል፡፡ በአማራ ክልል ለተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመፅና ተቃውሞ መነሻ የሆነውን የወልቃይትና ፀገዴ፣ እንዲሁም የራያ የማንነት ጥያቄ ግን አልተመለሰም፡፡ ቀደም ሲል ለመግለፅ እንደሞከርኩት፣ በእነዚህ አከባቢዎች የሚነሳው የማንነት ጥያቄ መሠረቱ የመሬት ባለቤትነትና ተጠቃሚነት ነው፡፡ የትኛውም ማህብረሰብ በማንነቱ ላይ የማንም ምስክርነትና ፍቃድ አያስፈልገውም፡፡ የወልቃይት ህዝብ “አማራ ነኝ” ካለ ከራሱ በስተቀር “አማራ ነህ” ወይም “አማራ አይደለህም” የሚለው አካል ሊኖር አይችልም፡፡ በተመሣሣይ የራያ ህዝብ “ራያ ነኝ” ካለ ማንም አይደለህም ሊለው አይችልም፡፡
እስካሁን ድረስ ህወሓት ይህን ጥያቄ በሃይል ሲያፍንና ሲያዳፍን የነበረው ከማንነቱ ጥያቄ በስተጀርባ ያለውን የመሬት ባለቤትነትና ያለመፈናቀል መብት ላለማክበር ነው፡፡ የወልቃይትና ራያ ህዝብ ከሚያነሱት ጥያቄ በስተጀርባ የህልውናቸው መሠረት የሆነውን መሬት እየተዘረፉ በሄዱ ቁጥር እንደ ማህብረሰብ የነበራቸው ባህልና ማንነት እየተሸረሸረ ስለሆነ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ የወልቃይት ህዝብ ከ1983 ዓ.ም በፊትና በኋላ ከመሬት ባለቤትነት፣ ባህልና ቋንቋ አንፀር ያለውን ማንነት ብቻ በቂ ነው፡፡ በኦሮሚያ ክልል ለተቀሰቀሰው አመፅና ተቃውሞ መነሻ የሆነው የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ተቋርጧል፡፡ በተመሣሣይ አማራ ክልል ለተቀሰቀሰው አመፅና ተቃውሞ መነሻ የሆነው የመሬትና የማንነት ምላሽ ሊሰጠው ይገባል! በዛሬው እለት በተለያዩ የአማራ ክልል ከተሞች የተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ መሠረታዊ ጥየቄ ይሄ ነው፡፡ ዶ/ር አብይን ለመቃወም ሳይሆን ለማስታወስ ነው፡፡ ህገመንግስቱን ለመጣስ ሳይሆን እንዲከበር ለመጠየቅ ነው፡፡ ኦሮማራን ለማፍረስ ሳይሆን ይበልጥ ለማጠናከር ነው!
Filed in: Amharic