>
5:13 pm - Friday April 19, 4593

ዶ/ር አብይ ሳያውቁት የደርግን ስህተት እንዳይደግሙት!!! (አብርሀ በላይ)

ዶ/ር አብይ ሳያውቁት የደርግን ስህተት እንዳይደግሙት!!!
አብርሀ በላይ
ዶ/ር ደብረጽዮን ባለፉት ጥቂት ቀናት በልዩ ልዩ የትግራይ ከተሞች እየተዘዋወሩ የሚፈልጉትን መልእክት አስተላልፈዋል። አንዳንድ ተራ የልማት ቦታዎችን ቢጎበኙም፣ ዋናው ተልእኳቸው ግን ህዝቡን ለአይቀሬው ጦርነት ማዘጋጀት መሆኑ ግልጽ ሆኗል። በዶ/ር ደብረጽዮን እና በህዝቡ መካከል ሽር ጉድ ሲሉ የትም የሚታዩት ሆድ እንጂ ጭንቅላት ያልፈጠረላቸው የህወሃት ካድሬዎቹ ናቸው። የዶ/ር አብይን አካሄድ በግልጽ እየኮነኑ የከረሙት ዶ/ር ደብረጽዮን፣ “ፌዴራል ሥርአቱ እየፈራረሰ እና ህገ-መንግስቱን እየተጣሰ ነው” ካሉ በኋላ፤ በትግራይ ህዝብ እና በህወሃት ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶችም ተካሂደው “ስናከሽፋቸው ቆይተናል” ብለዋል።  “እንኳን ለኛ ለሌላም እንተርፋለን” ካሉ በኋላ፣ ደብረጽዮን “በቀኝ እና በግራ የሚመጣውን መክተን፣ ብዙ ዋጋ የከፈልንበት እና አሁን አደጋ ላይ የወደቀው የፌዴራል ሥርአት ማዳን ነው” ብለዋል።
ማስጠንቀቂያ:-
የህወሃት ባለስልጣናት የትግራይ ህዝብን አንቀው ያላንዳች የመሃል አገር ጣልቃ-ገብነት ከተቆጣጠሩት እነሆ ከ40 አመት በላይ ሆኗል። ከአቅም ማጣት ይሁን ወይም አያደርጉትም ከሚል ንቀት፣ እነ ዶ/ር አብይ የትግራይ ህዝብን ከህወሃት ለመነጠል ያደረጉት የተለየ ዝግጅት የለም። ህወሃት የሚፈልገው ደግሞ እስኑ ነው። 90% የሚሆነው የትግራይ ገበሬ፣ ከእለት ጉርሱ ከማሰብ አልፎ የሚያውቀው “ቦለቲካ” የለም። ቢኖር እነ ደብረጽዮን የሚግቱት ፕሮፓጋንዳ እንጂ፣ የነ ዶ/ር አብይ ለውጥ ለሰላም፣ ለዴሞክራሲ፣ ለፍትህ ብሎም ለብሄራዊ ክብራችን መሆኑን አይደለም።
(Warning: TPLF has always the habit of projecting itself as the underdog to its perceived enemies. This helps the rival not to prepare adequately because of the wrong perception that the enemy is too weak and can be dealt with easily.)
ደርግ እድሜውን ያጠረው እስኪ ትግራይን ለቀን እንውጣና የት እንደሚደርሱ እናያለን ካለ በኋላ ነው። ከአመት አመት ከሰውነቱ ጋር የተጣበቀች ብጫቂ ነገር ለብሶ፣ ስራ አጥቶ፣ አፉን ከፍቶ ቀኑ ረዝሞት እያፋሸገ የሚኖረው ድሃው የትግራይ ገበሬ፣ እነ ደብረጽዮን ድንገት ደርሰው ዩኒፎርም እና ጠመንጃ አድለው፣ በሬ አርደው “ውፈር ተበገስ” ቢያስጨፍሩት ከሰማይ እንደወረደ መና ነው ያሚያስደስተው። ለሱ አዲስ የሥራ ዕድል ነው! ኑሮን ማሸነፍ መጀመሩ እንጂ፣ አገር እንደሚያሳጣው አያውቀውም። ስለዚህ በዚች በቀረችው እጅግ አጭር ጊዜ የኢትዮጵያ ህልውና ከአደጋ ለመታደግ አሁንም ጠ/ሚ አብይ አህመድ አስቸኳይ አገር-አቀፍ እርምጃዎች ቢወስዱ ይመረጣል። ጦርነቱ ዱብ ዕዳ እንዳይሆንበትም፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ሊያውቀው ይገባል።
Filed in: Amharic