>

ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ ላልተወሰነ ጊዜ ወደ ቃሊቲ ተዛወረ

Wibishet Tayeበሽብርተኝነት ክስ ጥፋተኛ ነህ ተብሎ የአስራ አራት አመት እስር የተፈረደበት ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ በእስር ከሚገኝበት የዝዋይ እስር ቤት ላልተወሰነ ጊዜ ወደ ቃሊቲ ተዛወረ፡፡

የጋዜጠኛ ውብሸት ባለቤት ወ/ሮ ብርሃኔ ተስፋዬ ለነገረ ኢትዮጵያ እንደገለጸችው ውብሸት ከዝዋይ ወደ ቃሊቲ ከተዛወረ ቀናት ተቆጥረዋል፡፡ ‹‹ሆኖም ግን ብዙ ሰዎች ውብሸት ወደ ቃሊቲ መዛወሩን መረጃው የላቸውም›› ያለችው ወ/ሮ ብርሃኔ፣ ‹‹አሁን ውብሸት ቃሊቲ በፊት ለፊት በር በኩል ዋይታ ቤት በሚባለው በኩል ይገኛል፡፡ ከሰኞ እስከ አርብ ሙሉ ቀን ሊጠይቀው የፈቀደ ሁሉ መጠየቅ ይችላል›› ብላለች፡፡

ውብሸት ወደ ቃሊቲ የተዛወረበት ምክንያት የቤተሰብ ጉዳይ ስላለበት መሆኑን የጠቀሰችው ወ/ሮ ብርሃኔ ባለቤቷ ቃሊቲ የሚቆየው ላልተወሰነ ጊዜ መሆኑን ገልጻለች፡፡ ‹‹እስከ መቼ ቃሊቲ እንደሚቆይ ባላውቅም መስከረም 29 ቀጠሮ ስላለው እስከዚያው በዚሁ እንደሚቆይ እገምታለሁ›› ብላለች፡፡

ጋዜጠኛ ውብሸት የአንድ ልጅ አባት ሲሆን ቀደም ሲል ዝዋይ እስር ቤት እያለ ልጁን ለማየት ፈተና እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ‹‹አሁን ለጊዜውም ቢሆን ልጃችንን ይዠ ስለምጠይቀው ልጁን ቶሎ ቶሎ ማየት ችሏል›› ስትል ወ/ሮ ብርሃኔ ለነገረ ኢትዮጵያ ተናግራለች፡፡

የውብሸት ልጅ ፍትህ ውብሸት ይባላል፡፡ ይህ ህጻን ‹‹እኔም ሳድግ እንደ አባቴ እታሰራለሁ?›› ሲል መጠየቁ ይታወሳል፡፡

በሌላ በኩል ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ በእስር ቤት ሆኖ የጻፈው ‹‹የነጻነት ድምጾች›› መጽሐፍ ለንባብ መብቃቱን ባለቤቱ ወ/ሮ ብርሃኔ ገልጻለች፡፡

ምንጭ:- ነገረ ኢትዮጵያ

 

Filed in: Amharic