>
5:13 pm - Sunday April 20, 9806

‘‘ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች!!’’ (በኒቆዲሞስ -ከሀገረ ኢትዮጵያ)

‘‘ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች!!’’

በኒቆዲሞስ (ከሀገረ ኢትዮጵያ)


ሰቆቃወ ኢትዮጵያ… (ከሰቆቃው ኤርምያስ መጽሐፍ የተወሰደ)

ጤት። የኢትዮጵያ በሮችዋ በመሬት ውስጥ ሰጠሙ፥ መወርወሪያዎችዋን አጠፋ ሰበረም፤ ነቢያቶችዋም ከእግዚአብሔር ዘንድ ራእይ አላገኙም። 

ዮድ። የኢትዮጵያ ሴት ልጅ ሽማግሌዎች ዝም ብለው በመሬት ላይ ተቀምጠዋል፤ ትቢያን በራሳቸው ላይ ነሰነሱ፥ ማቅም ታጠቁ፤ የኢትዮጵያ ደናግል ራሳቸውን ወደ ምድር አዘነበሉ። 

ካፍ። ሕፃኑና ጡት የሚጠባው በከተማይቱ ጐዳና ላይ ሲዝሉ፥ ዓይኔ በእንባ ደከመች፥ አንጀቴም ታወከ፤ ስለ ወገኔ ሴት ልጅ ቅጥቃጤ ጉበቴ በምድር ላይ ተዘረገፈ። 

ላሜድ። በከተማ ጐዳና እንደ ተወጋ ሰው በዛሉ ጊዜ፥ ነፍሳቸውም በእናቶቻቸው ብብት በወጣች ጊዜ፥ እናቶቻቸውን። እህልና የወይን ጠጅ ወዴት አለ? ይሉአቸዋል። 

ሜም። የኢትዮጵያ ሴት ልጅ ሆይ፥ ምን እመሰክርልሻለሁ? በምንስ እመስልሻለሁ? ድንግሊቱ የኢትዮጵያ ልጅ ሆይ፥ አጽናናሽ ዘንድ በምን አስተካክልሻለሁ? ስብራትሽ እንደ ባሕር ታላቅ ነውና፤ የሚፈውስሽ ማን ነው? 

ኖን። ሀገሬ ሆይ፣ ነቢያቶችሽ ከንቱና ሐሰተኛ ራእይ አይተውልሻል፤ ምርኮሽንም ይመልሱ ዘንድ በደልሽን አልገለጡም፤ ከንቱና የማይረባ ነገርንም አይተውልሻል። 

ሳምኬት። መንገድ አላፊዎች ሁሉ እጃቸውን ያጨበጭቡብሻልና። በውኑ የውበት ፍጻሜና የምድር ሁሉ ደስታ የሚሉአት ከተማ ይህች ናትን? እያሉ፥ በኢትዮጵያ ሴት ልጅ ላይ ያፍዋጫሉ፥ ራሳቸውንም ያነቃንቃሉ።

ዔ። ጠላቶችሽ ሁሉ አፋቸውን አላቀቁብሽ፤ እያፍዋጩና ጥርሳቸውን እያፋጩ። ውጠናታል፤ ነገር ግን ተስፋ ያደረግናት ቀን ይህች ናት፤ አግኝተናታል አይተናትማል ይላሉ። 

ፌ። እግዚአብሔር ያሰበውን አደረገ፤ በቀድሞ ዘመን ያዘዘውን ቃል ፈጸመ፤ አፈረሰ አልራራምም፤ ጠላትንም ደስ አሰኘብሽ፥ የሚያስጨንቁሽንም ቀንድ ከፍ ከፍ አደረገ። 

ጻዴ። ልባቸው ወደ ጌታ ጮኸ። የኢትዮጵያ እናት ሆይ፥ እንባሽን እንደ ፈሳሽ ቀንና ሌሊት አፍስሺ፤ ለሰውነትሽ ዕረፍት አትስጪ፤ የዓይንሽ ብሌን አታቋርጥ። 

ቆፍ። ተነሺ፥ በሌሊት በመጀመሪያ ክፍል ጩኺ፥ በጌታም ፊት ልብሽን እንደ ውኃ አፍስሺ፤ በጐዳና ሁሉ ራስ ላይ በራብ ስለ ደከሙ ስለ ሕፃናትሽ ነፍስ እጆችሽን ወደ እርሱ አንሺ። 

ሬስ። አቤቱ፥ እይ፤ በማን ላይ እንደዚህ እንዳደረግህ ተመልከት። በውኑ ሴቶች ፍሬያቸውን፥ ያቀማጠሉአቸውን ሕፃናት፥ ይገፋሉን? በውኑ ካህኑና ነቢዩ በጌታ መቅደስ ውስጥ ይገደላሉን?

አቤቱ፥ የሆነብንን አስብ፤ ተመልከት ስድባችንንም እይ። ርስታችን ለእንግዶች፥ ቤቶቻችን ለሌሎች ሆኑ። 

ድሀ አደጎችና አባት የሌለን ሆነናል፤ እናቶቻችን እንደ መበለቶች ሆነዋል። ውኃችንን በብር ጠጣን እንጨታችንን በዋጋ ገዛን። አሳዳጆቻችን በአንገታችን ላይ ናቸው፤ እኛ ደክመናል ዕረፍትም የለንም። 

ለግብጻውያንና ለአሦራውያን እንጀራ እንጠግብ ዘንድ እጅ ሰጠን። አባቶቻችን ኃጢአትን ሠሩ ዛሬም የሉም፤ እኛም በደላቸውን ተሸከምን። 

ባሪያዎች ሠልጥነውብናል፤ ከእጃቸው የሚታደገን የለም። ከምድረ በዳ ሰይፍ የተነሣ በሕይወታችን እንጀራችንን እናመጣለን። ከሚያቃጥል ከራብ ትኩሳት የተነሣ ቁርበታችን እንደ ምድጃ ጠቈረ።

በጽዮን ሴቶችን፥ በይሁዳም ከተሞች ደናግልን አጐሰቈሉ። አለቆች በእጃቸው ተሰቀሉ፤ የሽማግሌዎች ፊት አልታፈረም። ጕልማሶች ወፍጮን ተሸከሙ፥ ልጆችም ከእንጨት በታች ተሰናከሉ።

ሽማግሌዎች ከአደባባይ፥ ጕልማሶች ከበገናቸው ተሻሩ። የልባችን ደስታ ቀርቶአል፤ ዘፈናችን ወደ ልቅሶ ተለውጦአል። አክሊል ከራሳችን ወድቆአል፤ ኃጢአት ሠርተናልና ወዮልን!

ስለዚህ ልባችን ታምሞአል፤ ስለዚህም ነገር ዓይናችን ፈዝዞአል፤ ስለ ኢትዮጵያ ተራራ፥ ባድማ ሆናለችና፥ ቀበሮችም ተመላልሰውባታልና። አቤቱ፥ አንተ ለዘላለም ትኖራለህ፤ ዙፋንህ ከትውልድ እስከ ትውልድ ነው። 

ስለ ምን ለዘላለም ትረሳናለህ? ስለ ምንስ ለረጅም ዘመን ትተወናለህ? አቤቱ፥ ወደ አንተ መልሰን እኛም እንመለሳለን፤ ዘመናችንን እንደ ቀድሞ አድስ፡፡

Filed in: Amharic