>

የአማራ ፋኖ ወሎ ዕዝ እስክንድር ክፍለ ጦር የተላለፈ መልዕክት .. !!

የአማራ ፋኖ ወሎ ዕዝ እስክንድር ክፍለ ጦር የተላለፈ መልዕክት ..!! 

 ሚያዝያ 1 ቀን 2016 ዓ.ም ከምዕራብ ወሎ ግንባር የመልዕክቱ ሙሉ ይዘት እንደሚከተለው ቀርቧል። 
 ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለ1445ኛው የኢድ አልፈጥር በዓል አደረሳችሁ፤ኢድ-ሙባረክ!!
ክፍለ ጦራችን የሚንቀሳቀሰው ከደሴ ከተማ በስተምዕራብ በሚገኙ ወረዳዎች በተለይም በወግዲ፣ መካነሰላም፣ ሳይንት፣ ለጋምቦ፣ ከለላ እና ጃማ ሲሆን ቀጠናው በእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ ትልቅ ክብር እና ቦታ ያላቸው የሀበሻው ቁጥብ ተብለው የሚጠሩት የከለላው ደገር መስጊድ መስራች የሆኑት የጌታው ሸህዬ የኖሩበትና ለአንድነት እና ለፍቅር አርአያ የሆኑበት ምድር ስለሆነ ፍቅርን እና መከባበርን ከሀበሻው ቁጥብ የተማረው የእኛ ትውልድም የአባቶቹን አርበኝነት እና ለአንድነት ያላቸውን ከፍተኛ ቦታ በመውረስ የፋሽስቱ ስርአት በሀይማኖት ሰበብ ፋኖን ሊያዳክም ሲራወጥ ቀድመን በመሰባሰብ ሴራውን አክሽፈን የአማራ ህዝብን የአድንነት ገመድ አጥብቀን በድል ታጅበን ዛሬ ደርሰናል። ባሳለፍናቸው የፆም ሳምንታትም አንጀታችንን አስረን አስደናቂ ጀብዱዎችን ፈፅመን የጠላትን ቅስም በመስበር ለወገን ኩራት የሆነ ሀይልንም መገንባት ችለናል።
 ከጌታው ሸህዬ አገር ከለላ ደገር፣ ከአባ ጊዮርጊስ ዘ ጋስጫ ገዳም አጠገብ፣ ከእግዜር ድልድይ አቅራቢያ ሆነን ከአባ ኮስትር በላይ የትውልድ መንደር ጦር መሽገን፣ በእውነተኛው የዘመናችን አርበኛ እና የነፃነት ታጋይ እስክንድር ነጋ ስም አደረጃጀታችንን ሰይመን ለጠላት ረመጥ የሆነውን ክፍለ ጦር የምድር ድሮን በሚባሉ ተወርዋሪ ተዋጊ ጀግኖች አሸብርቀነው እንኳን ለታላቁ የረመዳን ፆም ፍች አደረሳችሁ የሚል መልዕክት ስናስተላልፍላችሁ በታላቅ ኩራትና ልዩ ከሆነ የጀግንነት ስሜት ጋር ነው።
 በፆም ወቅት ቆይታችሁ በነበራችሁ ፈጣሪን የመማፀን ዱአችሁ እኛንም ስታስቡን መቆየታችሁን ክፍለ ጦራችን ባስመዘገባቸው ድሎች እንዲሁም አዛን እና ቅዳሴ እየረበሸው በተሰቃየው በሰይጣኑ እና ከፋፋዩ ስርአት አገልጋዮች ሽንፈት እና መሽመድመድ አረጋግጠናል።
ሸሆቹ በዱአቸው “አላህ ሀቅን ከነፍጥ ጋር ላነገቡ ብርታትና ድልን ያጎናፅፍልን” አገስግስ እያሉ ከጎናችን ቆመው ሳለ እኛን ወደፊት ከመገስገስ የሚያቆመን ምድራዊ ሀይል ሊኖር አይችልም። ግስጋሴያችን ወደ አራት ኪሎ ነው፤ እየመጣን ነው!!
ፆሙን በጋራ ጀምረን ፈጣሪያችንን በመማፀን ለነፃነታችንም በጋራ እየተዋደቅን የፋኖነትን አማራዊ እሴት ጠብቀን ዛሬ ደርሰናል።
በረመዳን ወር ያስመዘገብነው ድል የሰራዊቱን አመራሮች ጭምር በእጃችን ላይ የጣለ ተአምር የታየበት ድል ሲሆን ከወር በሗላ ለሚከበረው ለትንሳኤ በአል ማጀቢያ የሚሆን ደማቅ ድል አስመዝግበን እንደምናስደምማችሁም እርግጠኞች ነን። የአማራ ትንሣኤን በቅርቡ እናያለን።
ቃሉን በተግባር በሚያሳየው የነፃነት ታጋይ እስክንድር ነጋ ስም የተሰየመው ክፍለ ጦራችን ልክ እንደ እስክንድር ቃልን በተግባር የሚለውጥ አቅም ያለው ስብስብን ያቀፈ መሆኑን በሰራነው ስራ አስመስክረናል፤ ወደፊትም እናስመሰክራለን።
 ከፋፋዩ እና ፋሽስታዊው ስርዓት ዳግም ላይመለስ እየተንኮታኮተ ስለሆነ የመጨረሻው ምዕራፍ መጀመሪያ ላይ መሆናችንን በመገንዘብ ሁሉም ነፃነት እና ፍትህን ወዳድ ወገን ከፋኖ ጎን በመቆም በአማራ ህዝብ ላይ የተሰነዘረውን ጥቃት በመቀልበሱ ሂደት የድርሻውን እንዲወጣ እያስታወስን በድጋሜ እንኳን ለ1445ኛው የኢድ አልፈጥር በዓል አደረሳችሁ እንላለን።

 ኢድ ሙባረክ!! 

እየመጣን ነው!

በለጠ ካሳ (ኢትዮ ኒውስ)

https://t.me/beletekassa
Filed in: Amharic