>

የቴድሮስ አድሃኖም ዋና አማካሪ የሃሰት ፕሮፌሰር መሆናቸው ተረጋገጠ [ኣበበ ገላው]

አዲስ ቮይስ– የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መስሪያ ቤትና የሚኒስትሩ ዋና አማካሪ እንዲሁም የፖሊሲ ጥናትና ትንተና የበላይ ሃላፊ የሆኑት “ፕሮፌሰር” መኮንን ሃዲስ የሃሰት ፕሮፌሰር እደሆኑ አዲስ ቮይስ ባካሄደው እረዘም ያለ ምርመራ ማረጋገጥ ችሏል።። ግለሰቡ ለ15 አመታት በፕሮፌሰርነት አገልግየዋለሁ የሚሉት አንድ የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲ እንደማያውቃቸው የገለጸ ሲሆን የዶክትሬት ዲግሪ ያገኙበት ተቋምም በአሜሪካ ህግ መወሰኛ ምክር ቤት “የዲፕሎማ ወፍጮ” (diploma mill) ተብሎ የተፈረጀ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል።

Mekonnen Haddis- by Abebe Gelaw“ፕሮፌሰር” መኮንን ሃዲስ ከኦክቶበር 2010 ጀምሮ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋና አማካሪ ሆነው በመንግስት የተሾሙ ሲሆን አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በነበሩ ወቅት ዋና አማካሪያቸው ሆነው ያገለገሉት እኚሁ ግለሰብ በአሁኑ ግዜ የዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ዋና አማካሪ እንዲሁም የፖሊሲ ጥናትና ትንተና ክፍል የበላይ ሃላፈ ሆነው በመስራት ላይ ይገኛሉ።

“ፕሮፌሰር” መኮንን ለረጅም አመታት በአሜሪካን አገር ሜሪላንድ ውስጥ የኖሩ ሲሆን በዚሁ ግዛት ውስጥ በሚገኘው ባዊ ስቴት ዩኒቨርሲቲ (Bowie State University) ለ15 አመታት ያህል በፕሮፌሰርነት ማገልገላቸውን በይፋ ሲናገሩ ቆይተዋል። ከዚህም በተጨማሪ በካሊፎርኒያ ፓስፊክ ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ በሚል ስም ይንቀሳቀስ ከነበረ ተቋም የዶክትሬት ዲግሪ ማገኘታቸውን በተለያየ ግዚያት ሲገልጹ የነበረ ቢሆንም ዩኒቨሲቲው ዲግሪ ያለ ምንም ትምህርት እንደሚሸጥ በአሜሪካ ሴነት ትእዛዝ በተካሄደ ስምንት ወራት በፈጀ ምርመራ ከተረጋገጠበትና “የዲፕሎማ ወፍጮ” በሚል ስያሜ ከተፈረጀ በሁዋላ እአአ 2005 መዘጋቱን ለማወቅ ተችሏል። ምርመራው በተጨማሪም ኬኔዲ ዌስተርን ዩኒቨርሲቲ፣ ሃሚልተን ዩኒቨርሲቲ እና ካሊፎርንያ ኮስት ዩኒቨርሲቲዎች ዲግሪ ያለ ትምህርት የሚቸበችቡ ወፍጮ ቤቶች መሆናቸውን ይፋ አድርጎ እንደነበር እጃችን የገቡ መረጃዎች አረጋግጠዋል።

ይሄው በካሊፎኒያ ግዛት ይንቀሳቀስ የነበረውና የተዘጋው ዩኒቨርሲቲ የባችለር ዲግሪ በ $2295፣ የማስተርስ ዲግሪ $2395፣ እንዲሁም የዶክትሬት ዲግሪ 2595 ዶላር ይሸጥ እንደነበር ለህግ መወሰኛው ም/ቤት በልዩ ምርመራ ጽህፈት ቤት ዳይሬክተር በነበሩት ሮበርት ክሬመር የቀረበው ሪፖርት አረጋግጧል።

ለአስራ አምስት አመታት በፕሮፈሰርነት አገለገልኩት የሚሉት ባዊ ስቴት ዩኒቨርሲቲ የግለሰቡን ፕሮፌሰርነትም ይሁን ቅጥር ጉዳይ እንደማያውቅ ለአዲስ ቮይስ ገልጿል። አዲስ ቮይስ በጉዳዩ ላይ መረጃ ከዩኒቨርሲቲው ለማግኝት በጠየቀው መሰረት የዩኒቨርሲቲው የሰው ሃይል አስተዳደር ከፍተኛ ዳይሬክተር የሆኑት ሼይላ ሆብሰን በሰጡት ምላሽ ዩኒቨሲቲው በአሁኑ ወቅትም ይሁን ቀደም ባሉ አመታት መኮንን ሃዲስ የሚባል የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር እንደማያውቅ አስታውቀዋል።

አዲስ ቮይስ በጉዳዩ ላይ መረጃ ከዩኒቨርሲቲው ለማግኝት በጽሁፍና በስልክ ባቀረበው ጥያቄ መሰረት የዩኒቨርሲቲው የሰው ሃይል አስተዳደር ከፍተኛ ዳይሬክተር የሆኑት ሼይላ ሆብሰን በሰጡት ምላሽ ዩኒቨሲቲው አሁንም ይሁን ባለፉ አመታት በፕሮፌሰርነት ይሁን በሌላ ደረጃ መቀጠራቸውን የሚያሳይ ምንም መረጃ መግኘት አለመቻሉን በኢሜይል በላኩት ምላሽ አሳውቀዋል። ዳይረክተሯ የዩኒቨርሲቲው የሰው ሃይል አስተዳደር ክፍል ከኮምፒውተር ሰነዶች በተጨማሪ በወረቀት የያዛቸውን የመረጃ ክምችቶች ፈትሸው መኮንን ሃዲስ የሚባል ሰው የፕሮፌሰርነት ሹመትም ይሁን የቅጥር ማስረጃ ማግኘት አለመቻላቸውን አስረድተዋል።

አዲስ ቮይስ ባቀረበረበው ተጨማሪ የስልክ ጥያቄ መሰረት ፕሮፌሰሩ የተለያዩ ኮርሶችን አስተምርበት ነበር ያሉትን የታሪክና የስነ መንግስት የትምህርት ክፍል ሊቀመንበር የሆኑትን ፕሮፌሰር ሳሚ ሚለርን ዳይሬክተሯ ጠይቀው የተሩዱት መኮንን ሃዲስ አንድ ወይንም ሁለት ሴሜስተር ለሚሆን ግዜ ከረጅም አመታት በፊት በረዳትነት ማስተማራቸውን ብቻ እንደሚያውቁ አረጋግጠውላቸዋል። ዳይሬክተሯ ዩኒቨርሲቲው ውስጥ በተለያዩ ግዚያት ለአጭር ግዚያት በረዳትነት የሚያስተምር ማንኛውንም ግለሰብ እንደ ዩኒቨርሲቲው ተቀጣሪ እንደማይቆጥር ገልጸዋል። በትምህርት ክፍሉ እንደ ፕሮፌሰር ሚለር ከሰላሳ አመታት በላይ ያገለገሉት ፕሮፌሰር ዊሊያም ሌውስ በበኩላቸው መኮንን በዩኒቨርሲቲው የማስተርስ ዲግሪ ተማሪ እንደነበር አስታውሰው ትምህርቱን ካጠናቀቀ በሁዋላ ለጥቂት ግዚያት ብቻ የተወሰኑ ኮርሶችን በረዳትነት ማስተማሩን አስታውሳለሁ በማለት የመኮንን ሃዲስን ለአስራ አምስት አመታት የዘለቀ የፕሮፌሰርነት አገልግሎት ትክክል አለመሆኑን አረጋግጠዋል።
ፕሮፈሰሩ ለጉዳዩ ምላሽ እንዲሰጡ ያደረግነው ሙከራ ሳይሳካ የቀረ ሲሆን በስራ ላይ መጠመዳቸውን ካስረዱ በሁዋላ “Leave me alone!” በማለት ስልኩን ዘግተዋል። ወደ ኢትዮጵያ በኤክስፐርት ደረጃ ግብረገብ፣ ዴሞክራሲ፣ የግጭት ማስወደድና ተዛማጅ ጉዳዮችን በተመለከተ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና፣ መንግስታዊ ድርጅቶች እየተዘዋወሩ እውቀት ለማካፈል በ2007 ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት መኮንንን ሃዲስ አለም አቀፍ የገጣሚያን ማህበር በአለፉት መቶ አመታት ውስጥ በአለማችን ከተገኘኑ ምርጥ አንድ መቶ ገጣሚዎች አንዱ ነህ ብሎ አክብሮኛል በማለት በይፋ ተናግረው እንደነበር በጋዜጦች ተዘግቦ ነበር። በ ኦክቶበር 2007 የወጣው “ዴይሊ ሞኒተር” ጋዜጣ ፕሮፌሰሩ በበርካታ መቶዎች በሚቆጠሩ ግጥሞቻቸው እንደሚታወቁ መናገራቸውን ከመጥቀስ አልፎ በአለፉት መቶ አመታት ውስጥ ከተከሰቱ ”100 ምርጥ የአለማችን ገጣሚያን አንዱ” በማለት የአለም አቀፍ የገጣሚያን ማህበር የሚባል ድርጅት እንደሰየማቸው ዘግቧል።

ይሁንና ጉዳዩን ለማጣራት ባደረግነው ጥረት በአሁኑ ግዜ የተዘጋው ይህ ድርጅት ሃሰተኛ የሆኑ የግጥም ውድድሮችን በማኪያሄድ አብዛኛውን ተወዳዳሪ በማጭበርበር በርካታ አቤቱታ ቀርቦበት የነበረ ሲሆነ ድርጅቱም ሌላ የንግድ ተቋም መሸጡ ታውቋል።
—-
ጥቆማና ጠቃሚ መረጃ ለመላክ ይህን ኢሜይል ይጠቀሙ editor@addisvoice.com

Filed in: Amharic