>

አክራሪና አሸባሪዉ ኢህአዴግ ወይስ የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት? [ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ]

JOURNALIST REEYOT ALEMUልጆች ሆነን “እከሌ (እከሊት) አክራሪ ነዉ (ናት) ” ሲባል ይሰጠን የነበረዉ ትርጉም እና አሁን አክራሪነት እየሰጠ ያለዉ ትርጉም ለየቅል ይመስለኛል፡፡ ያኔ አንድ ሰዉ በአክራሪነት ሲጠራ ከብዙሃኑ በተለይ ሁኔታ ሃይማኖቱን ወይም የሚያምንበትን አንዳች ነገር አጥብቆ መያዙን እና በሚያምንበት ነገር ላይ የማይደራደር መሆኑን ከማሳየት አልፎ የአሁኑን አይነት አሉታዊ ትርጉም አይሰጥም ነበር፡፡ በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማዕከል የተዘጋጀዉ የአማርኛ መዝገበ ቃላትም ያኔ ቃሉን እረዳበት ከነበረዉ ትርጉም ብዙም የራቀ ፍቺ አያቀርብም፡፡ በ1993 ዓ.ም የካቲት ወር የተዘጋጀዉ ይኸዉ መዝገበ ቃላት አክራሪ ለሚለዉ ቃል የሚሰጠዉ ፍቺ “በሚከተለዉ እምነትና አስተሳሰብ ዉስጥ ፍፁምነት ሊኖር ይገባል ብሎ የሚያምንና የቆየዉን እምነትና አስተሳሰብ ከዘመናዊዉ ሁኔታ ጋር ማስተካከል እና ማጣጣም የማይፈልግ አጥባዊ (ሰዉ)” የሚል ነዉ፡፡ ከቅርብ ግዜ ወዲህ ግን የቃሉ ፍቺ እየተቀየረ መጥቶ አሁን ያለዉን እጅግ አሉታዊ የሆነ ገፅታ ይዟል፡፡ የህግ ባለሙያዉ ተማም አባቡልጉ የካቲት3 2007ዓ. ም በወጣዉ ኢትዮምህዳር ጋዜጣ ላይ “አክራሪ ሰዎች እነማን ናቸው?” በሚል ርዕስ ባስነበቡት ፅሁፋቸዉ “የራሱን ዘር፣ ሃይማኖትና ቡድን ጥቅም ሌሎችን በመጉዳት ጭምር ለማስጠበቅ የሚንቀሳቀስ ወይም ከማስጠበቅ የማይመለስ” ሰዉ እንደሆነ አክራሪ የሚባለዉ ገልፀዋል፡፡

የዚህ ፅሑፍ አላማ አሁን እየተግባባንበት ካለዉ ፍቺ አንፃር ” የአክራሪነትና የአሸባሪነት ባህሪ የሚንፀባረቀዉ በቅርቡ በተፈረደባቸዉ የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ላይ ወይስ በከሳሹ መንግስት?” የሚላዉን ጉዳይ መፈተሽ ይሆናል፡፡

የኢህአዴግ የምናብ ቀበሮዎች

ኢህአዴግ እኔን ጨምሮ በርካታ ከሽብር ጋር ሊገናኝ የማይችል ማንነት ያለንን ዜጎች የአሸባሪነት ስም ሰጥቶናል፡፡ ይሄን በአሰብኩ ቁጥር ሁሌም ወደ አእምሮዬ የሚመጣዉ ብዙዎቻችሁ የምታዉቁት የዉሸታሙ እረኛ ታሪክ ነዉ፡፡ እንደምታስታዉሱት ሌሎችን በማታለል የሚዝናናዉ ዉሸታም እረኛ ቀበሮ መጥቶ በጎቹን እየበላበት እንደሆነ አድርጎ የድረሱልኝ ጥሪ በጩኸት በማቅረብ አላፊ መንገደኞችን ይሰበስባል፡፡ መንገደኞቹ ለእርዳታ ሲመጡ ታዲያ ቀበሮዉ በገሀዱ አለም ያለ ሳይሆን የእረኛዉ የምናብ ዉጤት መሆኑን ይረዱና እየተበሳጩ ወደየመንገዳቸዉ ይመለሳሉ፡፡ ኢህአዴግም “አክራሪ ደረሰብን ፤ አሸባሪ መጣብን” እያለ አደንቋሪ ጩኸቱን ለቁጥር በሚያዳግት መልኩ በተደጋጋሚ አሰምቷል፡፡ ጩኸቱን ሰምተዉ ስለሁኔታዉ ለማወቅ የሞከሩትን ሁሉ ግን የጠበቃቸዉ እንደዉሸታሙ እረኛ የምናብ ቀበሮ ሁሉ የዉሸት አክራሪና አሸባሪ ነዉ፡፡የምናብ ቀበሮ የሚበላዉ በግ እንደሌለ ሁሉ የምናብ አክራሪና አሸባሪም የሚያወድመዉ ንብረትም ሆነ የሚያጠፋዉ የሰዉ ህይወት የለም፡፡ እስክንድር ነጋና ሌሎች በእስር ላይ የሚገኙ ጋዜጠኞችና ጦማሪያን አሸባሪ ሊያሰኝ የሚችል ምን አደረጉ? አንዷለም አራጌ እና ሌሎች የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ምን አጠፉ? ምንም!

የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላትም እንደከዚህ ቀደሞቹ ሁሉ የኢህአዴግ የምናብ ቀበሮዎች ናቸዉ፡፡ ኡስታዝ አቡበከር አህመድ ይሁን ሌሎቹ የኮሚቴ አባላት አክራሪም ሆነ አሸባሪ ለመባል የሚያበቃ ያደረጉት ነገር የለም፡፡ ይልቁንም መንግስት በሃይማኖታቸዉ ጉዳይ ጣልቃ ገብቶ እምነቱን ለመበረዝና ለመከለስ የሚያደርገዉን ጥረት እንዲያቆም እጅግ በሰለጠነና ሰላማዊ በሆነ መንገድ ሲጠይቁ የነበሩ በህዝበ ሙስሊሙ የተመረጡ የአላማ ሰዎች ናቸዉ፡፡ ለመረጣቸዉ ህዝብና ለሃይማኖታቸዉ ታማኝ ሆነዉ መገኘታቸዉ ግን ለኢህአዴግ ስላልተስማማዉ እንዲያስራቸዉ ብሎም ለመስማት የሚከብድ አሰቃቂ በደሎችን እንዲፈፅምባቸዉ ምክንያት ሆነ፡፡ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን በስህተት ያሳየዉ የአንደኛ ተከሳሽ የአቡበከር አህመድ እጆች በካቴና ታስረዉ ሲመረመር የሚያሳየዉ አሳዛኝ ምስል የተመለከተዉን ሁሉ ልብ የሚያደማ ነበር፡፡ በሁኔታዉ ልባቸዉ የተነካ ሙስሊም ወገኖቻችንን አቡኪ ወንድሜ የእስልምና ብርሃን ሁኔታህን አይተን ሁላችን አነባን ብለዉ እንዲያዜሙ ያስገደደ ነበር፡፡

ይህ ሁሉ ሆኖ ግን ኮሚቴዎቹ ከታሰሩበት አሰቃቂ ቦታም ሆነዉ ሰላማዊ የሆነዉ ጥያቄ መንግስት በሚወስዳቸዉ ያልተገቡ የአፈና ምላሾች ሳቢያ ሌላ መልክ እንዳይዝ በጎ መልዕክት ከማስተላለፍ ወደኋላ አላሉም፡፡ ኮሚቴዎቹ በዚህ መጠን ከህዝበ ሙስሊሙ አልፈዉ ለሀገር ሰላም ቢጨነቁም ዉሸታሙ እረኛ ግን የተለመዱ የሀሰት ዶክመንተሪዎችን በማቅረብ ስማቸዉን ለማጥፋት ሲታትር ነበር፡፡ ይብስ ብሎ ደግሞ በቅርቡ ከሰባት እስከ ሃያሁለት አመታት የሚደርስ ፍርድ ቀኝ እጁ በሆነዉ ፍርድቤት በኩል አስተላለፈባቸዉ፡፡ ይህ አስገራሚ ፍርድ በሚተላለፍበት ወቅት ግን ኮሚቴዎቹ በጀግንነት ቆመዉ እንባ የሚራጩ ዘመድ ወዳጆቻቸዉን ሲያፅናኑ እንደነበር ችሎቱን የተከታተሉ ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡ አስቀድመዉ በነበሩ ችሎቶች ላይ “እዚህ የቆምነዉ ፍትህ እናገኛለን በሚል እምነት አይደለም፡፡ ለታሪክ ምስክር ለመሆን እንጂ” በማለት እንደገለፁት ከካንጋሮ ፍርድቤት የሚጠብቁት ፍትህ ባለመኖሩ የተሰጣቸዉ ፍርድ እንደማያስደነግጣቸዉ ግልፅ ነዉ፡፡ የኮሚቴዎቹ አባባል ኔልሰን ማንዴላ ያልተገባ ስም ተሰጥቷቸዉ ለፍርድ በቀረቡበት ወቅት የተናገሩትንና የግል የህይወት ታሪካቸዉን ባሳተሙበት መፅሐፍ ዉስጥ የሚገኘዉን የሚከተለዉን ሃሳብ ያስታዉሰኛል፡፡ ይህ የፍትህ ስርዐት ጥፋተኛዉ ንፁሑን በህግ ፊት እንዲያቀርበዉ ጉልበት የሚሰጠዉ በመሆኑ ትልቅ ስጋት ዉስጥ ይከተኛል፡፡ የፍትህ ስርዐቱ ልክ ያልሆነዉ ልክ የሆነዉን እንዲከስና ማስቀጣት እንዲችል የሚያደርግ ነዉ……. በመሆኑም ፍትሃዊና ተገቢ ፍርድ አላገኘም፡፡
ያኔ ኔልሰን ማንዴላ አስቀድመዉ እንደተናገሩት የአፓርታይድ መሪዎቹ የሚያሽከረክሩት ፍርድቤት ያልተገባ ፍርድና የወንጀለኛነት ስም ሰጥቷቸዋል፡፡ ዛሬም ኮሚቴዎቹ ኢህአዴግ በሚያሽከረክረዉ ፍርድቤት አማካኝነት ከማንዴላ ጋር ተቀራራቢ የሆነ ፍርድና ተመሳሳይ የሆነ ስያሜ አግኝተዋል፡፡ “አሸባሪነት” ዛሬም እንደትላንቱ ሁሉ አምባገነኖች የሚቃወሟቸዉን ንፁሃን የሚመቱበት ዱላ መሆኑን ቀጥሏል፡፡

አክራሪዉ ኢህአዴግ ነዉ!

የኢህአዴግ ባላስልጣናት አክራሪነት ከሱ ሌላ የሆነ ቡድን ወይም ማንነት እንዲኖር የማይፈቅድ እንደሆነና “ለልማታችን እና ለዲሞክራሲ ግንባታችን” ዋነኛ ጠር መሆኑን ሁሌም እንደነገሩን ነው፡፡ ከአባባሉ ተነስተን አክራሪ ስንፈልግ ዉለን ብናድር የምናገኘዉ ትልቁ አክራሪ ግን እራሱ ኢህአዴግ ሆኖ ይገኛል፡፡ ከአብዮታዊ ዲሞክራሲ ሌላ ርዕዮተ አለም በሀገራችን እንዳይኖር አይደለም እንዴ የተለየ መስመር የሚከተሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን የሚያፈርሰው? በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ ጋዜጦችና መፅሔቶች የመዘጋታቸዉና ጋዜጠኞቹ የመታሰርና የመሰዳደቸዉ ምክንያትስ እርሱ ከሚቆጣጠራቸዉ ዉጪ የሆኑ ሚዲያዎች እንዳይኖሩ ከመፈለግ የመጣ አይደለምን? የደሃ ሀገራችንን አንጡራ ሃብት እንደ ሃኪንግ ቲም ላሉ የጣልያን ተቋማትን የሚከሰክሰዉ ሁሉን ለመቆጣጠር ባለዉ ክፉ አባዜ ምክንያት መሆኑን መች አጣነዉ? የትምህርትም ሆነ የስራ እድል የኢህአዲግ አባል ካልተሆነ ለማግኘት የጠበበዉ ከኢህአዲግ አክራሪ ባህሪይ የመነጨ መሆኑ ግልፅ ነዉ፡፡ ሌሎች ብዙ የኢህአዲግ አክራሪነት መገለጫዎችን መዘርዘር ይቻላል፡፡

ለማጠቃለል ያህል አንዱን ልጥቀስ በሜታ ሮቢ ወረዳ አስተዳደር የወራቦ ቀበሌ አስተዳደር ነዋሪ የሆኑ አስራ አራት ግለሰቦች “በ2007ዓ.ም በተካሄደዉ ምርጫ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን ሲደግፉ ነበር” በሚል አስገራሚ ምክንያት የተነሳ ማናኛዉንም የህግና የአስተዳደር አገልግሎቾችን ማግኘት እንዳይችሉ በቀበሌ አስተዳደሩ ለሚመለከተዉ ሁሉ ስማቸዉ ተዘርዝሮ ተፅፏል፡፡ ባለፈዉ ረቡዕ ከሰንደቅ ጋዜጣ ጋር ቆይታ ያደረጉት የመድረክ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ጥላሁን እንደሻዉ እንዚህን ግለሰቦች ጨምሮ በርካታ የፓርቲዉ አባላትና ደጋፊዎች ላይ ዘርፈ ብዙ ችግሮች እየደረሱ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የችግሩን ምክንያት ሲያስረዱም “እነዚህ ታጋዮቻችን ህዝቡ መድረክን እንዲመርጥ ምን ሲሰሩ እንደነበር ስለሚያዉቅ አሁን እየወሰደ ያላዉ የበቀል እርምጃ ነዉ” ብላዋል፡፡ በዚህ መጠን ከእርሱ ሌላ እንዳይኖር የሚፈልገዉና ኖሮ ሲገኝ ደግሞ ተሸብሮ ህዝቡን የሚያሸብረዉ ኢህአዲግ የማይገባቸዉን ሰዎች አሸባሪ እና አክራሪ ሲል አፉን ያዝ እንኳን አያደርገዉም፡፡ ገዢዉ ፓርቲ ያልተገባ ስም የሰጣቸዉ ሙስሊም እህቶቻችን ቢቸግራቸዉ እንዲህ በማለት ሊያርሙት ሞክረዉ ነበር
የሂጃቡ ነገር ከላይ ከፈጣሪ
የኒቃቡስ ነገር ከላይ ከፈጣሪ
ልባል አይገባም አክራሪ አሸባሪ
የኮሚቴዎቹ እስርና ፍርድ ምን ሊያስከትል ያችላል?
ገዢዉ ፓርቲ ጥያቄዎችም ሆነ ተቃዉሞዎች ሲነሱበት ራሱን ከመመርመር ይልቅ በድፍረት ድምፃቸዉን ያሰሙ አካላትን ማሰርን ይመርጣል፡፡ በዚህም እፎይታን የሚያገኝ ይመስለዋል፡፡የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላትም ላይ ያደረገዉ ይህንን ነዉ፡፡ ነገር ግን ይሄ አካሄዱ የተመኘዉን እፎይታ ሊያስገኝለት ይቅርና ለሀገር የሚተርፍ ችግር ሊያመጣ እንደሚችል ጉዳዩን በጥልቀት የተከታተሉ ወገኖች ይገልፃሉ፡፡
ከነዚህ ወገኖችአንዱ የሆነው ጋዜጠኛ ሀይለመስቀል በሸዋምየለህ በቅርቡ ገበያ ላይ በዋለዉና “የሀይለማርያም እዳ እና የሙስሊሙ ትግል” በሚል ርዕስ ባዘጋጀዉ መፅሐፉ ዉስጥ በርካታ በጉዳዩ ላይ የተሰሩ ጥናቶችን ዋቢ በማድረግ እንደገለፀዉ ኢህአዲግ የሙስሊሙን ጥያቄ ለማፈን እየተጓዘበት ያለዉ መንገድ እጅግ አፍራሽ ዉጤት ይኖረዋል፡፡ ከአፍራሽ ዉጤቶቹ አንዱ ደግሞ “ኢህአዴግ እየተከላከልኩት ነዉ የሚለዉ ፅንፈኝነት መፈጠር” ሊሆን እንደሚችል መፅሐፉ ያስረዳል፡፡ ዶ/ር አባድር ኢብራሂም ADDIS STANDARD በተሰኘ ወርሃዊ መፅሔት የዚህ ወር እትም The unfair trial of Muslim Leaders ; why it undermines counter terrorism in Ethiopia በሚል ርዕስ ባቀረቡት ፅሁፋቸዉ ዉስጥም ተመሳሳይ ስጋት እናገኛለን፡፡ ዶ/ር አባድር ኮሚቴዎቹ ላይ የተሰጠዉን የጥፋተኝነት ዉሳኔ መነሻ በማድረግ ባዘጋጁት በዚህ ፅሁፋቸዉ የተላለፈዉ ውሳኔ የፍትህን መክሸፍ ከማሳየቱ በላይ እነዚህ የሲቪል ማህበረሰብ መሪዎች ወደፊት ከሚመጣ የሽብር አደጋ የመስዕዋት ጠቦት ሆነዉ ሊያድኑን አለመቻላቸዉ እንዳሳዘናቸዉ ገልፀዋል፡፡ ዶክተሩ ኮሚቴዎቹ ላይ የተላላፈዉ ውሳኔ እንደዉም የሽብር ስጋቱን እንደሚጨምር አምስት መከራከሪያዎችን በማቅረብ ይሞግታሉ፡፡ እኚሁ የህግ ምሁር ከመከራከሪያዎቹ በአንዱ እንዳብራሩትኮሚቴዎቹ በህዝበ ሙስሊሙ ዘንድ እጅግ ተሰሚነት ያላቸዉ መሪዎች እንደመሆናቸዉና በፀረ ሽብር ትግሉ አገላለፅ “ለዘብተኛ” የሚባሉ ስለሆኑ አክራሪነትን ለመከላከል ግንባር ቀደም አጋር ሊሆኑ የሚችሉ ነበሩ፡፡ ኢህአዲግ እነዚህን ትልቅ አጋር ሊሆኑ የሚችሉ መሪዎችን በመክሰስና በማሰር እዋጋቸዋለሁ የሚለዉን አክራሪ ድርጅቶች የቤት ስራ እንደሰራላቸዉ ዶክተሩ በፅሁፋቸዉ ይገልፃሉ፡፡ ምክንያቱን የሚያብራሩትም እንደነ አቡበከር አይነቶቹ ቅሬታዎችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍረታት የሚታትሩ ሙስሊም መሪዎች ባላቸዉ ተቀባይነት ፅንፈኛ ድርጅቶች ቅቡልነት እንዲያጡ በማድረግና የድርጅቶቹን ትምህርቶች ሊገዳደር በሚችል የሃይማኖቱ ትምህርት በመምታት እስልምናን ሽፋን አድርጎ የሚመጣን የሽበር አደጋ ለመከላከል የነበራቸዉን አቅም በመጥቀስ ነዉ፡፡ ዶክተሩ በሌላኛዉ መከራከሪያቸዉ ደግሞ በሰላማዊ መንገድ ለመወያየት ጥያቄያቸዉን ለማቅረብ በሞከሩ ሙስሊሞች ላይ መንግስት እየፈፀማቸዉ ባሉ በደሎች ሳቢያ አመፅአልባ ትግሉጥያቄ ዉስጥ መግባቱና ሰዎች ወደሌላ አማራጭ ለማየት መገደዳቸዉ እንደማይቀር ያስገነዝባሉ፡፡
ጋዜጠኛ ሀይለመስቀልም ሆነ ዶ/ር አባድር ይሄ ትልቅ ሀገራዊ ችግር የሚያመጣዉ ኪሳራ አሳስቧቸዉ መፍትሄ ፍለጋ ላይ ታች ቢሉም ኢህአዲግ ግን አሁንም ከመጥፎ ድርጊቱ አልታቀበም፡፡ በትላንትናዉ ዕለት እራሱ ኮሚቴዎቹን ለማስፈታት ተንቀሳቅሳችኋል ያላቸዉ ሃያ የዕምነቱ ተከታዮች ላይ ክስ እንደመሰረተ በማህበራዊ ድረገፆች እያነበብን ነዉ፡፡ እስርቤት በነበርኩበት ወቅትም የአዳማ ሙስሊምተማሪዎችን ጨምሮ በተመሳሳይ ክስ በርካታ ሙስሊሞች ይታሰሩ እንደነበር አዉቃለሁ፡፡ ገዢዉ ፓርቲ ስህተቱን በስህተት ለማረም የሚያደርገዉ እንዲህ አይነቱ አሳፋሪ እንቅስቃሴ መገታት ይኖርበታል፡፡ አለበለዚያ በሀሰት ቀበሮ እየተባሉ ፍዳቸዉን የሚያዩ ንፁሃን ወገኖቻችን ጉዳይ አሳስቦን በአንድነት መቆምና ገዢዉን ፓርቲ መታገል ካቃተን ነገ እዉነተኛ ቀበሮዎች ቢመጡ የምንመክትብት ጉልበት አይኖረንም፡፡ ለአሁኑ ግን ለእኔ የታየኝ አደገኛ ቀበሮ ኢህአዴግ ራሱ ነዉ፡፡

Filed in: Amharic