>

የዜጎች የመንቀሳቀስ መብት ይከበር! [ዞን ፱]

ዘጠኝ ጦማሪያንና ጋዜጠኞችየዜጎች ከሀገር ሀገር የመንቀሳቀስ መብት በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥትም ሆነ ኢትዮጵያ አባል ሆና በፈረመቻቸው አህጉር አቀፍ እና ዓለማቀፍ ድንጋጌዎች የተጠበቀ ነው፡፡ በሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 32/1 ላይ “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ . . . ከሀገር የመውጣት ነጻነት አለው” በማለት ተደንግጓል፡፡ ኢትዮጵያ ፈራሚ አባል የሆነችበት ‘ዓለም አቀፉ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች ቃልኪዳን’ በበኩሉ ማንኛውም ግለሰብ ሕጋዊ ማዕቀብ ካልተጣለበት በስተቀር ወደፈለገው ቦታ የመንቀሳቀስ ከሀገር መውጣትን የሚጨምር መብት እንዳለው ይደነግጋል፡፡ በኢትዮጵያ ህግም ብቸኛ ገደብ የሚያስቀምጠው የኢምግሬሽን አዋጅ ቁጥር 354/2003 በአንቀጽ 7 ላይ “ማንኛውም ሰው ከኢትዮጵያ እንዳይወጣ ሊታገድ የሚችለው በሕግ መሠረት በፍርድ ቤት ሲታዘዝ ብቻ ነው” በማለት የመንቀሳቀስ መብት ገደብን በማያሻማ መልኩ ያስቀምጠዋል፡፡

እንደሚታወሰው የዚህ የጡመራ መድረክ አባል የሆነው ዘላለም ክብረት በወንጀል ተጠርጥሮ ታስሮ የነበረ ቢሆንም ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በራሱ ተነሳሽነት ክሱ እንዲቋረጥ በማድረጉ ከማሕሌት ፋንታሁን፣ ከአስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ፣ ከኤዶም ካሳዬና ከተስፋለም ወልደየስ ጋር ሐምሌ 01/2007 ከእስር ተፈትቷል፡፡ ከላይ በተጠቀሰው የሕግ አግባብ መሠረት ከሀገር እንዳይወጣ የሚያደርግ ምንም ዓይነት ሕጋዊ ክልከላም የለበትም፡፡ ይሁንና ሕዳር 05/2008 ዘላለም ለቡድኑ የተበረከተ ሽልማትን ለመቀበል ወደ ፈረንሳይ፣ ፓሪስ ለማቅናት ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ቢገኝም የጉዞ ሰነዱ (ፓስፖርቱ) ተነጥቆ ከሀገር እንዳይወጣ ተከልክሏል፡፡ በተለያዩ የመገናኛ አውታሮች እንደተገለጸው ጦማሪው የጉዞ ሰነዱ እንዲመለስ እና የመንቀሳቀስ መብቱ እንዲከበር ያደረገው ሙከራ ከመጉላላት በቀር ምንም መፍትሔን አላስገኘም፡፡ እንዲያውም በአግባቡ ምላሽ የሚሰጥ መንግሥታዊ አካል መጥፋቱን ለመታዘብ ችለናል፡፡ በዚህም ምክንያት የተለያዩ ዕድሎችን ተጠቅሞ መማርም ሆነ መሥራት እንዳይችል ሁኗል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽንም ይህንን የመብት ጥሰት ‹ጉዳዩ ከአቅሜ በላይ ነው› በሚል ምክንያት ሊያስቆም አልቻለም፡፡

በሌላ በኩል ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ በታኅሣሥ 01/2008 ዓ.ም. ለትምህርት ወደ አሜሪካ ለመሔድ በሞከረችበት ወቅት የጉዞ ሰነዷን ተቀምታ ከሐገር መውጣት እንደማትችል የተነገራት ሲሆን፤ ለምን የጉዞ ሰነዷን እንደተነጠቀች በተደጋጋሚ ለኢሚግሬሽን እና ዜግነት መምሪያ ጥያቄ ብታቀርብም እስከ አሁን ድረስ ምላሽ ማግኘት አልቻለችም፡፡

እንዲሁም ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በጥር 11/2008 ዓ.ም. ወደ ጀርመን ሃገር ለስድስት ሳምንታት የጋዜጠኝነት ልምድ ለመቅሰም ያገኘውን አጋጣሚ ለመጠቀም ያደረገው ሙከራም በተመሳሳይ የጉዞ ሰነዱን ያለምንም ሕጋዊ ምክንያት በመነጠቁ ምክንያት ሳይሳካ ቀርቷል፡፡

ይባስ ብሎም ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ ለስድስት ሳምንታት ወደ ጀርመን ሃገር በመሔድ በጀርመኑ የመንግስት ቴሌቪዥን ጣቢያ የቀረበለት የልምድ ልውውጥ ላይ ተሳትፎ ወደ ሃገሩ ሲመለስ በየካቲት 26/2008 ዓ.ም. በተመለሰበት ወቅት ‹ከሃገር እንዴት ልትወጣ ቻልክ› ከሚል ከባድ ዛቻና ማስፈራሪያ ጋር የጉዞ ሰነዱን ሊነጠቅ ችሏል፡፡

ይህንን ሕገ ወጥ ድርጊት ለማረም ሁሉንም ሕጋዊ መንገዶች አሟጠን የምንጠቀም ሲሆን፤ ሕግ አስፈጻሚው አካል ግን ይህንን ስህተቱን ማረም የሚጀምርበት ተጨማሪ ዕድል አግኝቷል፡፡ ዘላለም ክብረት የዘንድሮው The Nelson Mandela Fellowship ወይም በቀድሞው አጠራር Young African Leaders initiative (YALI) አሸናፊ ሆኗል፡፡ የኔልሰን ማንዴላ ፌሎውሽፕ የአሜሪካው ፕሬዝዳነት ባራክ ኦባማ ወጣት አፍሪካውያን አህጉራቸውን የሚጠቅሙ መሪዎች እንዲሆኑ የሚያግዛቸውን ክህሎት እንዲጨብጡ በማሰብ እ.ኤ.አ. 2010 ይፋ ያደረጉት መርሐ-ግብር ሲሆን፤ በዚህ ስድስት ሳምንታት በሚፈጀው መርሐ-ግብር በየዓመቱ በርካታ አፍሪካውያን ለራሳቸውም ለአህጉራቸውም ጠቃሚ የሆነ ዕውቀት ገብይተው ተመልሰዋል፡፡ የዘንድሮው ውድድር አሸናፊ የሆኑት ሌሎች ኢትዮጵያውያን እና ዘላለም ክብረት በመጋቢት እና ሚያዝያ ወር ቅድመ ሁኔታዎችን አሟልተው በሰኔ አጋማሽ ወደ አሜሪካ እንደሚያቀኑ የመርሐ-ግብሩ የጊዜ ሰሌዳ ያሳያል፡፡

እኛም ከጊዜ ወደ ጊዜ ጉዳዩ ሕጋዊ መልክ ይይዛልና ይሻሻላል ብለን ተስፋ ብናደርግም ነገሮች ግን እየተባባሱ እና የመብት ጥሰቱም እየጨመረ መጥቷል፡፡ ይሄም ድርጊት ዜጎች በሃገራቸው ሕግን አምነው ለመኖር አለመቻላቸው ማሳያም ነው፡፡ በመሆኑም የሚመለከተው የአስፈጻሚ አካል ያለምንም የሕግ አግባብ የጉዞ ሰነዳቸውን ተቀምተው የሚገኙ ጦማሪዎችና ጋዜጠኞች መብታቸው ተከብሮላቸው የጉዞ ሰነዶቻቸው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲመለሱላቸው እንዲያደርግ እና የመንቀሳቀስ መብታቸውን እንዲያከብር እንጠይቃለን፡፡

ሕገ መንግሥቱ ይከበር!

Filed in: Amharic