>

ከሴት የፖለቲካ እስረኞች መካከል ጥቂቱ  (የአንድ ደቂቃ ንባብ!)

በፈቃዱ ዘ ሃይሉ

እማዋይሽ ዓለሙ – መንግሥትን በኃይል ለመገልበጥ አሲራችኋል በሚል በሚያዝያ ወር 2001 ነበር የታሰረችው። የዕድሜ ልክ ፍርደኛ ነች። አንዳንድ አባሪዎቿ “በምኅረት” ሲፈቱ እሷ ግን እስካሁንም በቃሊቲ ወኅኒ፣ የጥየቃ ሰዐቷ ተገድቦ አለች።

ጫልቱ ታከለ – ስምንት ዓመታት ያክል ኦነግ ነሽ ተብላ ታስራ ከተፈታች በኋላ፣ በድጋሚ ኦነግን ልትቀላቀል ስትል ተያዘች በሚል ዘንድሮ በሽብር የተከሰሰች ሴት ናት። እሷም የጠያቂዎቿ ቁጥር እና የጥየቃ  ሰዐቷ ተገድቦ ቃሊቲ አለች።

ንግሥት ይርጋ – ጎንደር የነበረውን የሐምሌ 2008 ፍፁም ሠላማዊ ሰልፍ፣ “የአማራ ሕዝብ አሸባሪ አይደለም” የሚል ቲሸርት ለብሳ ስታስተባብር ታይታ በሽብር የታሰረች ወጣት ፖለቲከኛ ናት። እሷም የጠያቂዎቿ ቁጥር እና የጥየቃ ሰዐቷ ተገድቦ ቃሊቲ ወኅኒ አለች።

ሴና ሰለሞን – ስለትግል በምታቀነቅናቸው ዜማዎቿ የምትታወቅ ድምፃዊት ናት። ከጓደኞቿ ጋር ‘ሰገሌ ቄሮ’ በሚል የዩቱብ ገጽ ላይ ወቅታዊ ዜናዎችን በመሥራታቸው በሽብር ተከስሳለች። እሷም፣ በቃሊቲ ወኅኒ የጠያቂዎቿ ቁጥር እና የጠያቂ ሰዐት ተገድቦባት አለች።

እየሩሳሌም ተስፋው – የቀድሞ የሰማያዊ ፓርቲ አባል ነበረች። በሠላማዊ ትግል በተደጋጋሚ በመታሰሯ፣ ግንቦት ሰባትን ለመቀላቀል በመወሰኗ በ2007 ታስራ የተፈረደባት ወጣት ነች። እሷም በቃሊቲ ወኅኒ፣ የጠያቂዎቿ ቁጥርና የጥየቃ ሰዐቷ ተገድቦ አለች።

(እነዚህ ማሳያዎቻችን ብቻ ናቸው)

Filed in: Amharic