>

የህወሃት የበላይነት የሚረጋገጠው በፍርሃትና ሽብር ነው! (ስዩም ተሾመ)

የህወሓት የበላይነት የሚረጋገጠው ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች የሚመሩበትን ሕገ-መንግስታዊ ስርዓት በድርጅቱ የፖለቲካ አቋምና አመለካከት የተመሰረተ እስከሆነ ድረስ ነው። የተለየ ወይም አዲስ የፖለቲካ ሃሳብና አመለካከት በብዙሃኑ የሕብረተሰብ ክፍል ዘንድ መስረፅና መስፋፋት ከጀመረ በሕገ-መንግስቱና ፖለቲካዊ ስርዓቱ ላይ ለውጥና መሻሻል ሊያስከትል ይችላል። ይህ ደግሞ የህወሓት የበላይነት የቆመበትን መሰረት ይንደዋል።

በዚህ መሰረት፣ የህወሓትን የበላይነት ለማስቀጠል ሕገ-መንግስታዊ ስርዓቱን በተግባር መለወጥና ማሻሻል ቀርቶ መታሰብ እንኳን የለበትም። ምክንያቱም፣ በህወሓት የፖለቲካ አቋምና አመለካከት ላይ የተመሰረተውን ሕገ-መንግስታዊ ስርዓት በዘላቂነት ለማስቀጠል አንድ ዓይነት የፖለቲካ አቋምና አመለካከት ያለው ልሙጥ ማህብረሰብ መፍጠር ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ አዲስና የተለየ ሃሳብ የሚያፈልቁ ግለሰቦች በማህብረሰቡ ውስጥ በነፃነት መንቀሳቀስ የለባቸውም።

ስለዚህ የሃሳብና አመለካከት ነፃነትን የሚገድቡ የሕግ አዋጆችን በማውጣት የሕግ-የበላይነትን በመናድ፣ የዜጎች ዴሞክራሲያዊ መብትና ነፃነትን በመጣስ፣ ግልፅነትና ተጠያቂነት የጎደለው ሥራና አሰራር በመዘርጋት፣… በሀገሪቱ ፖለቲካ ላይ የፍርሃት ድባብ መፍጠር ያስፈልጋል። የሕግ ዋስትና እንዲያጡ በማድረግ የተለየ የፖለቲካ አቋምና አመለካከት የሚያንፀባርቁ ወገኖችን በሙሉ በአምባገነናዊ ሽብር ማራድ፥ ማሽመድመድና ማስወገድ ያስፈልጋል፡-

“Terror substitutes for the boundaries of law and channels of communication between individual men… It eliminates individuals for the sake of the species; it sacrifices men for the sake of mankind—not only those who eventually become the victims of terror, but in fact all men insofar as this movement, with its own beginning and its own end, can only be hindered by the new beginning and the individual end which the life of each man actually is. With each new birth, a new beginning is born into the world, and a new world has potentially come into being.”  Hanna Arendt, On the Nature of Totalitarianism: An Essay in Understanding: 329-360

በዚህ መሰረት፣ የህወሓት/ኢህአዴግ መንግስት የተለየ የፖለቲካ አቋምና አመለካከት የሚያራምዱ ቡድኖችን፣ አዲስ ሃሳብና የተሻለ ነገር መፍጠር የሚችሉ ጠንካራ ዜጎችን ከመላ ሀገሪቱ ለማጥፋት ያላሳለሰ ጥረት አድርጓል። ባለፉት አስር አመታት ለዚህ ዓላማ ተግባራዊ ከተደረጉ የሕግ አዋጆችና መመሪያዎች ውስጥ የፀረ-ሽብር አዋጅ፣ የመረጃ ነፃነትና ሚዲያ አዋጅ፣ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ሕብረት መመሪያ፣ የኮምፒውተር ነክ ወንጀሎች አዋጅ፣ እንዲሁም በ2009 ዓ.ም የወጣው የአስቸኳይ ግዜ አዋጅ በዋናነት ይጠቀሳሉ። ከዚህ በተጨማሪ፣ የኢንተርኔት አገልግሎትን ማስተጓጎልና መቆጣጠር፣ የአገልግሎቱን ተጠቃሚዎች በመከታተል በፖለቲካ መሪዎች፥ ጋዜጠኞች፣ የመብት ተሟጋቾች፥ ጦማሪያን፣ እንዲሁም በተለያየ የሙያ ዘርፍ የተሰማሩና በሀገሪቱ ፖለቲካ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ የሚያደርጉ ዜጎችን ለእስር፥ ስደት፥ እንግልት፥ የአካል ጉዳትና ሞት ዳርጓል።

ይህ ሁሉ በደልና ጭቆና የሚደርስበት መሰረታዊ ምክንያት ዜጎች መንግስታዊ ስርዓቱ ከተመሰረተበት የፖለቲካ አቋምና አመለካከት ውጪ ሌላ ምንም ዓይነት የተለየ ሃሳብና አስተያየት እንዳይሰሙ፥ እንዳይናገሩ፥ እንዳይፅፉ፥ እንዳያውቁ፥ እንዳያሳውቁ፥ … ለማድረግ ነው። የህወሓት የበላይነትና ቀጣይነት የሚረጋገጠው በዚህ መልኩ ነው።

Filed in: Amharic