>

ከኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ማዕከላዊ ኮሚቴ የተሰጠ ድርጅታዊ መግለጫ

የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት(ኦህዴድ) ማዕከላዊ ኮሚቴ የተጀመረው የለውጥ ጉዞና የወደፊት አቅጣጫ ለ10 ቀናት ዝርዝር ግምገማ በማድረግ ዛሬ ማምሻዉን በስኬት አጠናቋል፡፡ ግንባራችን ኢህአዴግም በጥልቅ ለመታደስ የጀመረውን ንቅናቄ ዳር ለማድረስበቅርቡራሱን ገምግሞ አቅጣጫ ማስቀመጡ የሚታወስ ሲሆን ከግምገማው በመነሳትም ሀገራችን ኢትዮጵያና ክልላችን በፖለቲካዊ፤ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መስኮች ያለችበትን ሁኔታ በዝርዝር በመገምገም ቀጣይ አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡
አስር ቀናት በፈጀው የአሁኑ ውይይታችን፣ የሕዝባችን ሰላምና አብሮነት በምንም መልኩ አደጋ ውስጥ እንዳይገባ የክልላችን ሕዝቦች እና መሪ ድርጅቱ ኦህዴድ በቅንጅት በመስራት የሀገራችንን ሕልውና መታደግና የተጀመረውን የለዉጥ ጉዞ በስኬት እንዲጠናቀቅ የተቀናጀ ጥረት ማድረግ ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር መሆኑን አጽንኦት ሰጥቶ ተወያይቷል፡፡ድርጅታችን ከሚታወቅባቸው መለያ ባህሪያቱ እያንደንዱ ጉድለቶቹን ያለማመንታት መቀበልና ለማረም ጥረት ማድረግ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይህ የዴሞክራሲያዊ ድርጅት ባህሪይ በመሆኑ ከሕዝብ የሚነሱ ቅሬታዎችን ማድመጥ፣ ሕዝቡን ከልብ ይቅርታ የመጠየቅና የእርምት እርምጃ መውሰድ አስፈላጊ መሆኑን በዝርዝር በመምከር አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡
የፌዴራል ስርዓቱን አደጋ ውስጥ ሊጥሉ የሚችሉ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ምክንያቶችን ሳይንሳዊ በሆነ መልኩ ለይቶ አፋጣኝ እርምጃዎችን በመውሰድ የሕዝቡን መሻት ማሳካት ለነገ የማይባል ጉዳይ መሆኑን በዝርዝርተመልክቷል፡፡ ፍትሃዊ የኃብት ክፍፍል፣ አሳታፊ የፖለቲካ ስርዓት፣ ሰላምና ፍትህ እንዲሰፍን በጥብቅ ዲስፒሊን በመስራት የሕዝብ እርካታን ማረጋገጥ ጊዜ የማይሰጠው መሰረታዊ አጀንዳ ስለመሆኑ መክሯል፡፡ የኦሮሞ ሕዝብ ከመላዉ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ጋር በመተባበር የሀገራችንን ቀጣይ ጉዞ የማቅናት ሚናውን ዛሬም እንደትላንቱ መጫወት እንደሚገባውም ተወያይቷል፡፡
በኢህአዴግ አባል ድርጅቶች መካከል ያለውን ግንኙነት በዴሞክራሲ አግባብ በማጠናከር የጋራ አላማችንን ለማሳካት ርብርብ ማድረግና የሀገሪቱን ሕልውና ከአደጋ መከላከል እንደሚገባ በዝርዝር በመምከር አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡
የፌዴራላዊ ስርዓታችንን አደጋ ላይ የጣሉ ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን፣ ሕዝቡ በመሪ ድርጅቱ ላይ እንዲያምጽ ያስቻሉ የመልካም አስተዳደር እጦቶችን፤ስልጣን ህዝብን ማገልገያ መሳሪያ መሆኑንበመዘንጋትበርስትነት ይዞ ለግል ምቾትና ጥቅም ቅድሚያ መስጠትን፣ በነጻነት ተዘዋውሮ የመስራት መብትንነፍጎ በመቶ ሺህዎችየሚቆጠሩ ሕዝቦችንእስከማፈናቀል የደረሰ ድርጊትን፤ በኢንቨስትመንት ስም የመንግስትና የህዝብ መሬት መመዝበሩን፤እንዲሁም የሕዝቦች ሰላምና ጸጥታ መደፍረሱን እና የመሳሰሉትንእየተፈጸሙ ያሉ አደገኛ ድርጊቶችን ሕዝቡን ባሳተፈ መልኩ አምርሮ በመታገል የሀገራችንን ሕልውና መታደግ ልዩ ትኩረት የሚሹ አበይት ጉዳዮች መሆናቸውን በዝርዝር ተመክሮባቸዋል፡፡
ባለፉት ጥቂት ዓመታት በተከሰቱ ግጭቶች የበርካታ ዜጎች ሕይወት ጠፍቷል፤ ንብረት ወድሟል፤የሕዝቦች በሰላም ዉሎ ማዳር፣ ወጥቶ መግባት ከፍተኛ ስጋት ላይ ወድቃል፡፡ለእነዚህ ችግሮች መከሰት ኃላፊነቱን ወስዶእርማት ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ አጽንኦት ሰጥቶ በመምከር አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡
የፌዴራል ስርዓቱን አደጋ ላይ በመጣል ግላዊና ቡድናዊ ጥቅሞችን ለማስጠበቅ በንጹሃን ዜጎች ሕይወት ላይ አደጋ ያደረሱና በታሪካችን ታይቶ የማይታወቅ ፀያፍ ድርጊቶችን የፈጸሙ ኃይሎች በሕግ እንዲጠየቁ ለማድረግ፣ እንዲሁም መሰል ስህተት እንዳይደገምና የሕግ የበላይነት በመላ ሀገሪቱ እንዲሰፍን ለማስቻል ሕዝቦችንን በማሳተፍ ትግሉን ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገር የግድ መሆኑን ከግንዛቤ አስገብቶ ማዕከላዊ ኮሚቴው አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡
ቀንደኛ የሕልውናችን ጠላት ድህነት መሆኑ ቢታወቅም ይህንን ጠላት ለመዋጋት በመንግስት፣ ድርጅትና ሕዝብ ትስስር ሊሰራ እንደሚገባውና አዳዲስ ሃሳቦችን አያፈለቀ አመራር የመስጠት ጉዳይ ከድርጅታችን እንደሚጠበቅ ከስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
ኃብት ማመንጨት ብቻ ሳይሆን ፍትሃዊ የኃብት ክፍፍል እንዲኖር ማስቻል፣የኃብት አጠቃቀምንም ከብክነት የጸዳ ማድረግ፣ ግልጸኝነትና ተጠያቂነትን የሚያረጋግጥ አሰራር በማስፈን ሕዝቡ እንዲያለማ ከማስቻል በዘለለ የመቆጣጠር ሚናውንም ከፍ ማድረግ እንደሚገባ አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡
አዳጊ ኢኮኖሚን የሚያንኮታኩቱ መጥፎ ልማዶችን በተለይም ሙስና፣ ኮንትሮባንድ፣ ሕገወጥ የገንዘብ ዝውውር ፍላጎቱን ማኮላሸት፣የአቅርቦት ሰንሰለቱን ማስተጓጎል፣ ማንኛምውም የገበያ ፍትሃዊነትን የሚያዛቡ አሉታዊ ተግባራትንአጥፍቶ በምትኩ በዘመናዊነት የታገዘ ፍትሃዊ አሰራርን መዘርጋት፣ ያልተገባ የጥቅም ትስስር ያላቸዉን ሰንሰለቶች በጥናት ላይ በመመሰረት የመበጣጠስ ተግባር በተቀናጀና የሪፎረም ሥራውንበሚያሳልጥ መልኩ እንደሚፈፀም አቅጣጫ ተቀምጠዋል፡፡
ሕገመንግስታዊ ድንጋጌዎች ሳይሸራረፉ ተግባር ላይ እንዲውሉ፣ የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲከበሩ ዜጎች ካለምንም ስጋት ከቦታ ቦታ ተዘዋውረው እንዲሰሩ በማስቻል በፍትህ ስርዓቱና በፖሊሲ ስርዓታችን ላይ ተጨባጭ ለውጥ ሊያስገኙ የሚችሉ ሁለንተናዊ ሪፎርም ማከናወን እንደሚገባ ከስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
ከክልሎች ጋር የጀመርነዉን ህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ህግ መንግስታዊነቱን ጠብቆ እንዲቀጥልና ፌዴራላዊ ስርዓታችን ይበልጥ መጠናከር የሚችልበት ሁኔታ አጽንኦት ተሰጥቶት ተመክሮበታል፡፡የኦሮሞ ሕዝብ የመቻቻል፤የመደጋገፍና አብሮ መኖር እሴቶችን ያዳበረ በመሆኑ ከሌሎች ሕዝቦች ጋር በመከባበርና በፍቅር አብሮ በመኖር የሁሉም ዜጎች መብት በእኩል እንዲከበር ከወንድም ሕዝቦች ጋር አብሮ መስራት ይጠበቅበታል፡፡ ጥላቻን በጥላቻ፣ክፉተግባርን በሌላ ያልተገባ ድርጊት መመከትሊቆም ይገባዋል፡፡ በመሆኑም ተከሰቱ ለሚባሉ ችግሮች ሁሉ መፍትሄው ፍትሃዊና ሕጋዊ የትግል ስልትን መከተል መሆኑ ታምኖበት ከጥፋት ተግባራት በመታቀብኦሮሙማን በሚያጎላአቃፊ መሆን እንደሚገባ ከስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ሕዝቦች ጋር የነበረንን መልካም ግንኙነት በመመለስ እንደ ወንድማማች ሕዝቦች የባይተዋርነት ስሜት እንዳይፈጠር በሚያስችል መልኩ በታላቅ የኃላፊነትስሜት እንዲመራግዚያዊ ችግሮችን ፈተን ለዘላቂ የጋራ ጥቅሞቻችን በወንድማማችነት መንፈስ እነድንረባረብ የሶማሌም ይሁን ሌሎች ብህረ ብሄረሰቦች በኦሮሞ ባህልና የገዳ ስርዓተ ባስተማረን መልኩ በፍቅርና በአብሮነት እንዲኖሩ ለማስቻል ሕዝቡ የበኩሉን ሚና እንዲጫወት ማዕከላዊ ኮሚቴው ጥሪ አቅርቧል፡፡
የሐሳብ ልዩነቶችን ማጥፋት አስቸጋሪ እንደሆነ እሙን ነው፡፡ ስለሆነም ሁል ጊዜ ለውይይትና ለክርክር አውድ ማስፋት አስፈላጊ መሆኑ ታምኖበታል፡፡ ፍላጎትን በውይይት እንጂ በኃይል የማስረጽ ዝንባሌ እንዳይታይ በቀጣይነት መስራት እንደሚያስፈልግም መግባባት ላይ ተደርሷል፡፡
ዛሬ አድገው የሀገራቸውን ህዝብ ኑሮ በከፍተኛ ደረጃ ያሻሻሉ ሀገራት ታሪክ ሲመረመር በአገራዊ ጉዟቸውውስጥ ሕዝባዊ አመጽን ያስተናገዱ፣የወጣቶች ቁጣ የደረሰባቸውና መሰል አጋጣሚዎችን በዴሞክራሲያዊ መንገድ መቀልበስ የቻሉትየዘላቂ ልማት ባለቤት እንደሆኑ ታሪካቸው ያሳያል፡፡ በመሆኑም በወጣቶች ላይ የሚታየውንፍትህ የመሻት ቁጣሀገርን በማያፈርስ መልኩ ከሃይል በፀዳ ሁኔታ ሰላማዊ የትግል ስልት እንዲከተሉ በማስተማር የዴሞክራሲ ባህልን ማዳበር አስፈላጊ መሆኑን ኮሚቴው ያምናል፡፡ ዋነኛ ሚናውም የተሻለች ሀገር ለቀጣዩ ትውልድ ማሸጋገር በመሆኑ የተሻለች ሀገር ብቻ ሳይሆን ብቁ ተረካቢ ወጣቶችንማፍራት እንደሆነም ይገነዘባል፡፡
በአለም አቀፍ ደረጃ እየታየ ያለው ድርቅ፣ ግጭት፣ስደት፣ የሕዝብ መብዛትያልተደራጀ ኢኮኖሚና ያልደበረ የዲሞከራሲ ባህል ባለበት ሀገርነገሮች እንዲባባሱ ከማድረግ አልፎ የሀገር ህልውናን አደጋ ውስጥ እስከመጣል እንደሚደርስ ታውቆየተሻለች ሀገር የመፍጠሩና ብዙ ተረካቢ የማፍራቱ ተግባር በጥንቃቄና በኃላፊነት ስሜት እንዲከወን በዝርዝር ተመክሯል፡፡
ይህንንም ከማሳካት አኳያ ቅድሚያ ከተሰጣቸው ተግባራት መካከል ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የተፈናቀሉ ወገኖችን ከጊዜያዊ መጠለያ ወደ ቋሚ ቦታ ማስፈር፤የወጣቶችን የስራ አጥነትን በመቀነስ የኑሮ ሁኔታቸውን ማሻሻል፤ የመልካም አስተዳደርና ብልሹ አሰራሮችን ማስተካከል፤የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓትን ማዘመን፤ፍርድ ቤት፣አቃቤህግ፣ፖሊስ፣ የወረዳና የቀበሌ መዋቅሮችን መልሶ ማደረጀት፤ሰላምና ፀጥታ በማስከበር የሕግ የበላይነትን ማረጋገጥ ይገኙበታል፡፡
በመላ የሀገራችን ህዝቦች ይሁንታ አፋን ኦሮሞ የፌዴራል የስራ ቋንቋ እንዲሆንድርጅታችን ይሰራል፡፡ በተጨማሪም በሂደት ላይ ያሉና ያልተጠናቀቁ መሰረታዊ የህዝብ ጥያቂዎች በጥብቅ ዲስፕልን እዲፈጸሙ አቅጣጫ አስቀምጠዋል፡፡
በድርጅቱተጠያቅነትን ለማረጋገጥ፤መድረኩ የሚጠይቀውን የትግል ልክ በብቃት ለመፈፀም፣ በቀጣይም ጥንካሬውን አጎልብቶ መጓዝ ይችል ዘንድ 14የኢህአዴግ ምክር ቤት አባላት እንዲተኩ እና4 የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትም እሰከሚቀጥለው ጉባኤ እንዲታገዱና አንድ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል በማስጠንቂያ እንድታለፍ የወሰነ ሲሆን የዉስጠ ድርጅት ዲሞክራሲ የማስፋትና የአመራሩን የሃሳብና የተግባረ አንድነት ይበልጥ ማጠናከር በቀጠይነት እዲሰራበት ተመክሮዋል፡፡

የተከበርከው የኦሮሞ ሕዝብ

ለዘመናት ትከሻህ ላይ ተጭኖ የነበረውን የጭቆና ቀንበር ለመስበር ሁልጊዜም ታሪክ እየዘከረው የሚኖር አኩሪመስዋዕትነት ከፍለሃል፡፡ በከፈልከው መስዋዕትነት ከሌሎች ወንድሞችህ ጋር በመሆን አዲሲቷን ኢትዮጵያ ለመፍጠር፤ እኩልነት፣ ፍትህ፣ ዴሞክራሲና ሁሉን አቀፍ መብቶች የተረጋገጡባትን የበለፀገች ሀገር ለመገንባት መሰረት ጥለሃል፡፡ በተጀመረው የግንባታ ሂደት ውስጥ የመጡ ተስፋ ሰጪ ድሎች እንዳሉ ሁሉ የጭቆና መሰረት የሆኑ አስተሳሰቦችና አሰራሮችን የሚፈጥሩ አዝማሚያዎችም ይታያሉ፡፡ በነዚህ አዝማሚያዎች ላይም የጀመርከውን ትግል አጠናክረህ መቀጠል ያንተም ሆነ የወንድም ሕዝቦች የሕልውና ጉዳይ ነው፡፡
የመደብ ጭቆና ምን ያህል አስከፊ እንደሆና አዎንታዊ ለውጥን እንደሚገታ ባለፈው ታሪክህ ካንተ በላይ የሚገነዘብ የለም፡፡ በአሁኑም ሰዓት ተመሳሳይ መደባዊ ጭቆና ዳግም በሀገራችን እንዳያቆጠቁጥ ትግልህን አጠንክረህ መቀጠል ይገባሃል፡፡
በሁሉም የታሪክ ምዕራፎች ኢፍትሃዊነትና ጭቆናን ባለመቀበል ከሌሎች የኢትዮጵያ ህዝቦች ጋር በመሆን መስዋዕትነትእየከፈልክ ወደ ድል ስትራመድ እንደነበረው ሁሉ አሁንም ሀገራችንን የገጠሟትን ፈተናዎች በታጠቅከው የገዳ ስርዓት ቱባ ባሕል መሰረት ብሄር፣ብሔረሰቦችና ሕዝቦችን በማቀፍና ከጎንህ በማሰለፍ ትግሉን ወደ ላቀ ደረጃ በማሸጋገር የአዲሲቷን ኢትዮጵያ ህልውና በማስጠበቅ ለውጧን ሁለንተናዊ በሆነ መልኩ የማስቀጠል ኃላፊነትህን እንዲትወጣ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጥሪውን ያቀርባል፡፡
የተከበራችሁ የኦሮሚያ ክልል ወጣቶች
የክልላችንም ሆነ ሀገራዊ ለውጦች ያለወጣቱ ተሳትፎና መሪነት የሚታሰብ አይደለም፡፡ በዚሁ መሰረት እስካሁን በሀገራችን የመጡ ለውጦች በወጣቱ ተሳትፎና አኩሪ መስዋዕትነት የመጡ መሆናቸውን ኦህዴድ ይገነዘበዋል፡፡ ወጣቶቻችን በሁሉም መስክ የተጀመሩ የለውጥ እንቅስቃሴና መልካም ጅምሮች ወደ ላቀ ድል እንዲሸጋገሩ በባለቤትነት መሳተፍና ኃላፊነትን መወጣት፣ይህንንም በተደራጀ መልኩ መተግበር ይገባዋል፡፡ ወጣቱ በሁሉም መስክ የሚያደርገውን ትግል ምክንያታዊና ሳይንሳዊ በሆኑ ሃሳቦች እየተመራ፤ ዴሞክራሲያዊነትን በጠበቀና ተደማሪ ለውጦችን በተንከባከበ መልኩ የሁሉም መብት ተከብሮ፣ የሀገራችንም ህልውናና የክልላችን ሰላምእንደተጠበቀ የሚቀጥልበት አካሄድ እንዲረጋገጥ ግንባር ቀደም ኃላፊነቱን እንዲወጣ ድርጅታችን ኦህዴድ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

የተከበራችሁ የኦሮሞ ምሁራን 

በሁሉም የታሪክ ምዕራፍ ላይ የኦሮሞ ሕዝብ ባለፈበትየትግል ሂደት ውስጥ እናንተም መስዋዕትነት ከፍላችኋል፡፡ አሁንም በደረስንብት የትግል ምዕራፍ ውስጥ ከሕዝባችሁና ከመሪው ድርጅታችሁ ኦህዴድ ጋር በመሰለፍ ዋንኛው ሥራ የሆነውን ሃሳብን የማፍለቅና የትግሉን አቅጣጫ በጥናትና በምርምር የማሳየት የማይተካ ሚናችሁን እንደሁል ጊዜው መወጣት ይኖርባችኋል፡፡ ድርጅታችን ኦህዴድ፣ ምሁራንን ባላቸው አደረጃጀትም ሆነ በግል ክህሎታቸው፣እውቀትና የአመራር ብቃትም ጭምር አብሮ ለመስራት የጀመረውን ሥራ በተደራጀና በተቀናጀ መልኩ አጠናክሮ ለመቀጠል ወስኗል፡፡ በዚሁ መሰረት የተከበራችሁ የኦሮሞ ምሁራን የጀመራችሁትን ጠንካራና ተኪ የሌለው ሚናችሁን በመወጣት አጠናክራችሁ ትግሉን እንድትቀጥሉ፣ ለስኬትም እንድትረባረቡ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

የተከበራችሁ የኦሮሚያ ክልል መንግስት ሰራተኞች

የኦሮሞ ሕዝብ ባደረገው ትግል የራሱን ክልል መስርቶ ያሉበትን ችግሮች ለመፍታትና ራዕዮቹን ለማሳካት ትልቅ የመንግስት መዋቅር ዘርግቷል፡፡ በዚህ መዋቅርውስጥ የሕዝባችንን ችግር መፍታት የሚቻለው ከእውቀትና ክህሎት በተጨማሪጠንካራ ዲሲፒሊን ባለው የመንግስት ሰራተኛ ነው፡፡ በመሆኑም፣በመንግስት መዋቅር ውስጥ እየፈጠረበት ያለውንየመብት ጥሰት፣ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ እየተስፋፋ ያለው ሙስናና ኪራይ ሰብሳቢነት፣ ኢ-ፍትሃዊነትና የዴሞክራሲ እጦት ችግሮችን ለመፍታትየክልላችን መንግስት ሰራተኞች ቁልፍ ሚና አላችሁ፡፡ሕዝባችንን አንገት ያስደፋውን ዋነኛ ችግሩንበመቅረፍ ብልጽግናን ለማስፈን፣ የማስፈፀም አቅምን ለማጎልበት፣ቀን ከሌሊት ተግታችሁ የመስራት ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

የተከበራችሁ የኦሮሚያ ክልል የፀጥታ አካላት

በክልላችን ሰላምና ደህንነትን ለማረጋገጥ ከሕዝባችን ጋር በተለይም ከወጣቶች ጋር በመቀናጀት የሕዝባችንን ጥቅምና ሀብት ሲዘርፉ የነበሩ ኮንትሮባንዲስቶች ላይ የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥ፣ እንዲሁም በክልላችን የተጀመረውን ሪፎረም ለማደናቀፍ ዝርፊያ ድርጊታቸውን ማስቀጠል የሚፈልጉ የተደራጁ ኪራይ ሰብሳቢዎች የከፈቱትን ጥቃት ለመመከት በግንባር ቀደምነት ተሰልፋችሁ ከፍተኛ መስዋዕትነት ከፍላችኋል፡፡ በዚሁም የአዲሲቷን ኢትዮጵያ ሕልውና እንዲቀጥል ድርሻችሁን በመወጣት ከአደጋ እየታደጋችሁ ትገኛላችሁ፡፡
የኪራይ ሰብሳቢዎች ቡድን በመንግስት ስልጣን የመክበር አባዜ ከስር ተነቅሎ፣ የሕግ የበላይነት ሰፍኖ እስኪሸነፍ ድረስ የጀመራችሁትን ትግል ሕዝብን በማሳተፍ በከፍተኛ ዲሲፒሊን ሕዝባዊ ኃላፊነታችሁን መወጣት ይገባችኋል፡፡ በክልላችን አስተማማኝ ሰላምና የሕግ የበላይነት የተረጋገጠበት፣ እንዲሁም ፍትህ የሰፈነበት እንዲሆንና ዜጎቻችን መብታቸውተከብሮ ስርዓት አልበኝነት እንዳይኖር የተሰጣችሁን ተቋማዊ ኃላፊነት ከሕዝብ ጋር በመቆም ሕዝባዊ በሆነ መንፈስ እንድትወጡ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

የተከበራችሁ የኦህዴድ አባላት

ተንሰራፍቶ የቆየውን ጭቆና ለማስወገድ ሕዝባችን ሲያካሄድ በነበረውን መራራ ትግል ውስጥ የመርነት ሚናንተቀብለህ መስዋዕትነት በመክፈል የዛሬው ምዕራፍ ላይ እንዲደርስ የበኩልህን አስተዋፅኦ አበርክተሃል፡፡ ጠንካራ ድርጅት ያላ ጠንካራ አባል ሊታሰብ አይችልም፡፡ ኦህዴድ ያለበትን ታሪካዊ ኃላፊነት እንዲወጣ አሁን በደረሰበት የትግል መድረክ የሚመጥን ቁመና እንዲኖረው ለማስቻልና ለማስቀጠል የድርጅታችን አባላት የድርጅታችሁን አላማ በጥብቅ ዲስፒሊን ለማሳካት ቀን ከሌሊት መታገል ይገባችኋል፡፡ ሕዝባችን በተለያየ ደረጃ እያደረገ ባለው ትግል ውስጥ አባሎቻችን በግንባር ቀደምነት በመሳተፍና በመምራት ችግሮችን በኃላፊነትመፍታት ይገባቸዋል፡፡ አሁን የደረስንበት የትግል ምዕራፍ የሚጠይቀውን መስዋዕትነት በቅድሚያ በመክፈል ለሌሎች ምሳሌ በመሆን የድርጅታችሁን ተልዕኮ በተሰማራችሁበት መስክ ሁሉ በማሳካት የሕዝባችንን ጥያቄ በአፋጣኝ እየመለሰ፣ ትግሉን በግንባር ቀደምነት በመምራት አዲሲቷን ኢትዮጵያ እውን የማድረግ ኃላፊነቱን የሚወጣ፣ ጠንካራና ከለውጥ ጋር ራሱን የሚያሳድግ ድርጅት እውን እያደረጉ መጓዝትኩረት የሚሻ በመሆኑ ይህንንም በብቃት መወጣት ይገባችኋል፡፡

የተከበራችሁ በውጭ ሀገራት የምትኖሩ የኦሮሞ ተወላጆች

በኦሮሞ ሕዝብ የለውጥ ጉዞ ውስጥ ባላችሁ እውቀትና ኃብት በተደራጀም ሆነ ባልተደራጀ መልኩ የበኩላችሁን አስተዋጽኦ ለመወጣት ስታደርጉ የነበረውን ርብርብ የሚፈታተኑ ሁኔታዎች እንደነበሩ እና መድረኮችም አስቸጋሪ እንደነበሩ ኦህዴድ ይገነዘባል፡፡ በሕዝባችን አንድነትናሁለንተናዊ የለውጥ እንቅስቃሴ ውስጥ በእውቀት፣ በቴክኖሎጂ፣ባላችሁ ተሞክሮዎና ትስስር፣ በኃብትና በመሳሰሉት ሁሉ እንድትሳተፉና የሕዝባችንን ችግር በጋራ እንድንፈታ፤ የሚያስፈልጉ ሁኔታዎችም እንዲመቻቹ ኦህዴድ ጠንክሮ እንደሚሰራ ሊያረጋግጥ ይወዳል፡፡ በዚሁ መሰረት በውጭ ሀገር የምትኖሩ የኦሮሞ ተወላጆች በሕዝባችን ጥቅም ላይ ያለምንም ድንበርና ልዩነት በጋራ እንድንሰራ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

የተከበራችሁ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች

ድርጅታችን ኢህአዴግ፣በሀገራችን ሕዝቦች ላይ የተጫነውን ጸረ-ዴሞክራሲ፣ ድህነት፣ የመልካም አስተዳደር እጦትና ኋላቀርነትን ለመፍታት ባደረገው እንቅስቃሴ ተስፋ ሰጪ ድሎችን ማስመዘገብ የጀመረው በውስጡ ያለውን ችግር በተከታታይ በመፈተሽና በመፍታት ላይ ነው፡፡ በቅርቡ በኢህአዴግ ደረጃ በተደረገ ግምገማ በእህት ድርጅቶቹ መካከል የተፈጠረው ያልተገባ ግንኙነትበሂደትም ወደ ጥቅም ቡድተኝነት እያደገ በመምጠቱ የነበረው ግንኙነት እያሻከረ እንዲሄድ አድረገዋል፡፡ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴም ጉዳዩን በጥልቀት በመገምገም ማንኛውም ግንኙነቶች መርህና መርህ ላይ ብቻ እንዲመሰረቱና ዴሞክራሲያዊ ትግልን ማዕከል ያደረጉ እንዲሆኑ ለማስቻል ትኩረት ሰጥቶ ተወያይቶበት አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡ በዚሁ መሰረት የእህት ድርጅቶች አሁን በደረስንበት የትግል ምዕራፍ በግንባራችን ኢህአዴግ ተገምግመው አቅጣጫ የተቀመጠባቸውን ጉዳዮች ያለምንም መሸራረፍ እንዲፈፀሙና የሕዝባችንን ጥያቄ ለመመለስ ከመቼውም ጊዜ በላይ በአንድነት ርብርብ እንድናደርግ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

የተከበራችሁ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች

በብዝሃነት ለተገነባች ሀገራችን ኢትዮጵያ ዴሞክራሲ የህልዉና ጉዳይ መሆኑ እሙን ነው፡፡እንደ ነብር ዥንጉርጉር የሆነው የእርስ በእርስ ግንኙነታችን የሃሳብ ልዩነትን ማስተናገድ የሚያስችል አሰራርና ባህል ማዳበር ያስፈልገዋል፡፡ከሃይል የፀዳ፣ በዉይይትና በምክክር የሚያምን፣ ይበልጥ ለሀገር የሚበጅ ሃሳብ የሚፈልቅበት የውይይት ባህል እንዲዳብር የፖለቲካ ድርጅቶች ሚና ከፍተኛ ነው፡፡በዚህ ወሳኝ ወቅት የሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች አስተዋይነትና አርቆ አሳብነት የሚፈተንበት ጊዜ መሆኑ ግለፅ ነው፡፡ በመቀራርብናበመነጋገር የፖለቲካ ባህላችንን እንድናሻሽል ብሎምየሀገራችንን መፃኢ ዕድል በጋራ ማበጀት እንችል ዘንድ ተቀራርበን እንድንሰራ ድርጅታችን ይፈልጋል፡፡
ዴሞክራሲ ለሀገራችን ሕዝቦች የሕልውና ጉዳይ ነው፡፡ ዴሞክራሲ ለመገንባት የሀሳብ ልዩነቶች የሚስተናገዱበት ማዕቀፍና አሰራር እንዲሁም ባህልና አስተሳሰብ እንዲዳብር የፖለቲካ ፓርቲዎች ወሳኝ ሚና እንዳላቸው ኦህዴድ በሚገባ ይገነዘባል፡፡ የሀገራችን ሕዝቦች አማራጭ ሀሳቦች እየቀረቡለት በዴሞክራሲያዊ ሂደት የሚጠቅመውን ሃሳብ እንዲመርጥ፣ለፖለቲካ ፓርቲዎች በሕገመንግስቱ የተቀመጡ ቃልኪዳኖች ያለመሸራረፍ እንዲተገበሩና ዴሞክራሲ እንዲሰፍን ኦህዴድ ከተቃዋሚ ፖለቲካ ፖርቲዎች ጋር በቅርበት እንደሚሰራ በጥልቅ ተወያይቶበት አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡ በዚሁ መሰረት በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያላችሁ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ልዩነታችን እንደተጠበቀ ሆኖ በሀገራችንና በሕዝባችን የጋራ ጥቅምላይ ከድርጅታችን ኦህዴድ ጋር አብራችሁን እንድትሰሩ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

የተከበራችሁ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች

የኢትዮጵያ ብሔር፤ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በችግርም ሆነ በመልካም ጊዜ በጋራ ተፈትነው ትላንትን መሻገር ችለዋል፡፡ ለገጠማቸው ፈተናዎችምእኩል የታገሉና መሰዋትነት የከፈሉ ህዝቦች ናቸው፡፡ ሀገራችን ህልዉ ሆና እድትቀጥል ከማስቻላቸዉ ባሻገር በዓለም ታሪክ ውስጥ ጉልህ ቀለም እንዲኖራት አድርገውለዛሬ ትውልድ አሰረክበዋል፡፡በአባቶቻችን ተጋድሎ የተገነባችውን ኢትዮጵያ እኛም አስውበንና አንድነቷን አስጠብቀን ለቀጣይ ትዉልድ የማሻገር ታርካዊ ኃላፍነት አለብን፡፡በአንድ እጅ ማጨብጨብ አይቻልምና ይህን ሀላፍነታችን በብቃት እንድንወጣ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትንበማጠናከር፣ የጋራ እሴቶቻችንን በማጎልበት፣ የተጀመረው መልካም ጅማሮ ዳር እንዲደርስ እጅ ለእጅ ተያይዘን ለስኬቱ በጋራ እንድንረባረብ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴየ10 ቀናት የለዉጥ ግምገማ ቆይታ ድርጅቱ ለሃገራችን ሰለም ልማትና ዴሞክራሲ ጉዞ ስኬት እንዲሁም ለህዝቦች እኩል ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ ከመቼዉም ግዜ በላይ በላቀ ቁርጠኝንትና ተነሳሽነት ለማከናዉን ዝግጁነቱን ያረጋገጠበት መድረክ እነደሆነ የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ አረጋግጦዋል

የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ
ጥር 29/05/2010 ዓ.ም

Filed in: Amharic