>

በሸራተን ጓዳ! (አርአያ ተስፋማሪያም)

ጊዜው 1993 ዓ.ም ጅማሮ ላይ ነው። በኢትዮ – ኤርትራ ጦርነት ዙሪያ በልዩነት የተለኮሰው የውስጥ ቅራኔ ተመርኩዞ አቶ መለስ ተከታዮችን የሚይዙበትና በአንፃሩ በአቋም የተለዩዋቸውን ለመምታት በፅሁፍ ዝግጅት የተጠመዱበት ወቅት ነበር። “ታማኝ” በሚሏቸው ካድሬዎች በኩል “የድርጅቱ የመበስበስ አደጋ፣ በሙስና አመራሩ ሰጥሟል..” በሚል በስም ጭምር እየተጠቀሱ ማስነገር ይዘዋል። በሙስና ዙሪያ ትልቅ ፕሮፖጋንዳ ውስጡን ተቀጣጥሏል። ይህ እየተካሄደ ባለበት የ93 ጅማሮ ላይ ሸራተን ሆቴል አንድ ዝግጅት ሲካሄድ አቶ መለስና ዶ/ር ነጋሶ በክብር እንግድነት ታድመዋል። ጎን ለጎን ተቀምጠው እያለ ዶ/ር ነጋሶ ከአቶ መለስ ጋር በዝግታ ማውራት ይጀምራሉ። ነጋሶ ጀመሩ “ከሰሞኑ የምሰማው ፀረ ሙስና ዘመቻ የጥቂት ባለስልጣናት ስም ብቻ ዘሪያ ነው። ሙስናን እንዋጋለን ብለህ ታጥቀህ ተነስተሃል?..” ..ይላሉ። አቶ መለስም “አዎ..ሙስና የስርአታችን፣ የፓርቲያችንና የአገር አደጋ ሆኗል” በማለት የማያዳግም እርምጃ እንደሚወስዱና ምእራባውያንም ይህን እንዲያደርጉ በማስጠንቀቂያ ጭምር እየነገሯቸው መሆኑን ተናገሩ። ዶ/ር ነጋሶ አያያዙና “በጣም ጥሩ! ..” ብለው በ10 ሚሊዮን በሚገመት ወጪ ቪላ ሰርተው የሚያከራዩትንና ከፍተኛ ሀብት ያካበቱትን 5 የሚሆኑ ባለስልጣናት ስም ጠቅሰው፣ የሰሩትን ቪላ ከነአድራሻው ዘርዝረው ለመለስ ነገሩ። (አንዱ በአሜሪካ አምባሳደር ናቸው..ሌሎቹም በስልጣን ላይ አሉ..በስም ሳልጠቅስ ልለፈው) ..የመለስ መልስ እጅግ አስገራሚና ለነጋሶ አስደንጋጭ ነበር። ..

ከሸራተን መልስ
ለዶ/ር ነጋሶ ጥያቄ አቶ መለስ ፊታቸውን ቅጭም አድርገው “እኔ ኮሚሽን አቋቁሜ እነሱን ስከታተል አልውልም” ሲሉ ነጋሶ ቀበል አድርገው “ታዲያ ስለየትኛው ሙስና ነው የምታወራው?.” ይላሉ። መለስ ከላይ የተናገሩትን ደገሙ። “ከዚህ በኋላ ስለሙስና ምንም ማውራት አትችልም!” አሉ ነጋሶ። ..መሻከሩ በዚህ ተጠነሰሰ።..በመጋቢት 93 የህወሀት መሰንጠቅ ይፋ ሆነ። ስብሰባና ግምገማ ሌት ተቀን ነው። መለስ ህገ መንግስቱን ጥሰው ከፍተኛ ጄኔራሎችን ቤተመንግስት ለስብሰባ ጠሩ። ብ/ጄ ታደሰ ጋውና “ህገ ወጥ ነው” ሲሉ መለስን ተቃውመው ወጡ። ኢታማዦር ሹምና የአየር ሃይል አዛዥ በመለስ “አቋማችሁ ከወዴት?” አይነት ተጠየቁ። ..በሌላ በኩል ዶ/ር ነጋሶ ያሉበት የኦህዴድ ስብሰባ ይካሄዳል። በግምገማው በማስጠንቀቂያ ሊታለፍ የነበረ ከፍተኛ አባል በገመድ ራሱን ሰቅሎ ተገኘ። ..ኢትዮጵያ ራዲዮ የሁለት ጄኔራሎች ከስልጣን መነሳት ዜና አወጀ። ከምሳ መልስ ለነጋሶ ከሁለት ከፍተኛ የኦህዴድ ሹሞች ስልክ ተደወለና በራዲዮ የተሰራጨው ዜና ተነገራቸው። ዜናውን ስላልሰሙ ማመን አቃታቸው። ለአቶ መለስ ስልክ ደወሉ..”የምሰማው ዜና ምንድነው?..ምን እየተካሄደ ነው?”..ሲሉ ጠየቁ፤ አቶ መለስም “የአንተ ተላላኪ አይደለሁም.” አሉ። ከፍተኛ መኮንኖችን የመሾምና ከስልጣን የማውረድ ስልጣን የፕሬዚዳንቱ መሆኑን ህገ መንግስቱ ደንግጓል። መለስ ይህን ጥሰው ነው እርምጃ የወሰዱት። ..”ከዚህ በኋላ ከአንተ ጋር አብሬ አልቀጥልም” ብለዋል ነጋሶ። ለመጨረሻ ጊዜ የነጋሶና መለስ የስልክ ግንኙነት በዚህ አበቃ። ..አጠቃላይ የፓርቲው ስብሰባ ተጠራ። መለስ “ይህ ገበታ ..” እያሉ 3 አማራጭ አቀረቡ። ሶስተኛ ያሉት “ነጋሶ ይህን ገብታ አልታደምም ..እወጣለሁ” ብለው መለስ ሳይጨርሱ ነጋሶ “ሶስተኛው ይስማማኛል!” አሉና ብድግ አሉ። “መንግስቱ ሃ/ማርያምን መሰልከኝ” ሲሉ አከሉ። ገነት ዘውዴ “እንዴት መለስን ይህን ትለዋለህ?” ብለው ያለቅሳሉ። ..አሁን በስደት የሚገኙና በወቅቱ ለኦሮሚያ ፕ/ት እንዲሆኑ በመለስ በውስጥ የታጩ እንዲሁም 4 ሌሎች ባለስልጣናት ዶ/ር ነጋሶን ማስጨነቅ፣ ማስፈራራትና ማወከብ ያዙ። ዶ/ር ነጋሶ ከቤተመንግስት እንዲለቁ ተደርገው ሳር ቤት በሚገኝና በጣም በተቦዳደሰ የመንግስት ቤት እንዲገቡ ተደረገ። (በስደት እዚህ የመጡትን የቀድሞ አመራር በስልክ ሰለዚህ ድርጊት ስጠይቃቸው ለማስተባበል ሞከሩ..ግን አድርገውታል)..አንድ ከፍተኛ ጄኔራል “ነጋሶ መታሰር አለበት። ጄ/ል ታደሰ ጋውናም መታሰር አለበት” ሲሉ በስብሰባ ላይ ለመለስ ተናገሩ። ለነጋሶ የተመደበው መኪና በካዛንችስ በትራፊክ ፖሊስ ተያዘና ወደ ቤተመንግስት ተወሰደ። ..የተወሰነላቸው የጡረታ መብት ተገፈፈ። ፍ/ቤት አመለከቱና ዳኞች የዶ/ር ነጋሶ አቤቱታ አግባብ ነው ብለው ፈረዱ። “ይግባኝ” ተብሎ ሰበር ድረስ ሄደው እጅግ አሳፋሪ ውሳኔ አስቀልብሰው አስወሰኑ። ዶ/ር ነጋሶን ጨምሮ ከመለስ ጋር በሃሳብ የተለዩትን አመራሮች ቀን በቀን የሚከታተሉና የሚያስጨንቁ ደህንነቶች ..በወ/ስላሴ (የቀድሞ የደህንነት ሹም..አሁን በሙስና ወንጀል እስር ቤት የሚገኝ) ተመድበው ነበር። አቶ መለስ እስካለፉበት ጊዜ ድረስ ይህ ድርጊት ነበር። ..”ነጋሶና ጋውና መታሰር አለባቸው” ያሉት ከፍተኛ ጄኔራል ..ይህን ካሉ ከ3 አመት በኋላ ለነጋሶና ታደሰ ስልክ ደወሉ።
(ይቀጥላል)
Filed in: Amharic