>
5:14 pm - Sunday April 30, 0761

በምርጫው ጉዳይ ላይ ከባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ  የተሰጠ መግለጫ !

በምርጫው ጉዳይ ላይ ከባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ  የተሰጠ መግለጫ !


የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ  በሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ/ም የተደረገውን 6ኛ አገራዊ ምርጫ ድምጽ መስጫ ሂደት በተመለከተ መረጃዎችን በአዲስ አበባ ከተማ ካሉ የምርጫ ክልሎች በሙሉ በማሰባሰብ አጠናክሮ ለህዝብ ይፋ ለማድረግ በሚያስችል ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን ደግሞ፣ በድምጽ አሰጣጡ እና ቆጠራው የነበሩ ችግሮችን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርዱ ፓርቲያችን አቅርቦ ምላሽ በመጠበቅ ላይ ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ ምግባር አ/ቁ. 1162/11 የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጊዜያዊ የምርጫ ውጤትን ይፋ ከማድረጉ በፊት ተወዳዳሪ ፓርቲዎች ውጤቱን ከመግለጽ እንዲቆጠቡ የሚከለክል ሕጋዊ ድንጋጌ በመኖሩ ፓርቲያችን እስካሁን ለሕግ ተገዥ በመሆን በድምጽ መስጫ ቀን የነበሩትን ችግሮች እና ውጤቱን በሚመለከት መግለጫ ከመስጠት ተቆጥቦ ቆይቷል፡፡ ሆኖም ቦርዱ እስካሁን በተወሰኑ የአገራችን ክልሎች ያሉ ውጤቶችን ይፋ ከማድረጉ በስተቀር፣ በተሻለ መረጋጋት ውስጥ የተደረገውን የአዲስ አበባ ከተማን ውጤት አሳማኝ ባልሆነ ምክንያት ለህዝብ ይፋ ሳያደርግ ጊዜ እየወሰደ እንደሆነ ፓርቲያችን ያምናል፡፡
በፓርቲዎች የቀረቡ ቅሬታዎች እንዳሉ ሆነው፣ ቦርዱ ውጤቱን ያፋ ሳያደርግ በተድበሰበሰ ሁኔታ መቆየቱ አላስፈላጊ ለሆኑ እንቅስቃሴዎች በር የሚከፍት እንደሆነ ፓርቲያችን ይረዳል፡፡ አዲስ አበባን በተመለከተ በቦርዱ እጅ የገባው ውጤት የአንድ ፓርቲን የበላይነት እንደከዚህ በፊቱ የሚያረጋግጥ ሆነም አልሆነም፣ ፓርቲያችን እና ህዝቡ እውነቱን የማወቅ መብት አላቸው፡፡ ፓርቲያችን አሁንም የቦርዱን ሰብሳቢ፣ “ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ የአዲስ አበባን ጊዜያዊ የምርጫ ውጤት ለመራጩ ህዝብ ይፋ ያድርጉ” ብሎ ጥሪውን ያቀርባል፡፡
ሆኖም፣ ቦርዱ ውጤቱን ይፋ ለማድረግ ምክንያታዊ ያልሆነ ጊዜ አሁንም መውሰዱን የሚቀጥል ከሆነ፣ ፓርቲያችን በእጁ ያለውን የጥናት ሪፖርት ለህዝብ ይፋ ለማድረግ እና ለቀጣይ ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ ለመግባት የሚገደድ ይሆናል፡፡
ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ።          
   ድል ለእውነተኛ  ለዲሞክራሲ !!!
Filed in: Amharic