>
5:21 pm - Thursday July 21, 8861

"አሸባሪዎችን ከእነአስተሳሰባቸው ቀብረን ኢትዮዽያን እናስቀጥላለን ...!!!" (ተመስገን ጥሩነህ)

“አሸባሪዎችን ከእነአስተሳሰባቸው ቀብረን ኢትዮዽያን እናስቀጥላለን …!!!”
ተመስገን ጥሩነህ

“ካልደፈረሰ አይጠራም ካልጠራ አይጠጣም” የሚል አባባል አለን:: ጁንታው ከማዕከላዊ ፖለቲካ ራሱን ሲያገል የተማመነበት ጉዳይ የፌደራሊስት ሀይሎች በሚል አደራጅቶ የማዕከላዊ የለውጥ ፖርቲና መንግስቱን መገዳደር ነበር:: አልቻለም:: የመጀመሪያውን የሽንፈት ነጥብ ጣለ:: ያለህግ ምርጫ አደርጋለሁ አለ:: አደረገ::
 ከመስከረም 30 በኃላ ህጋዊ መንግስት የለም አለ:: ማንም አልሰማውም:: እሱ ግን ምርጫ አድርጊያለሁ እናም ህጋዊ መንግስት ነኝ በሚል አዲስ መንግስት አዋቀርኩ አለ:: የፌደሬሽን ምክር ቤት በሀገሪቱ ህግን ተከትሎ ምርጫ የተራዘመ ቢሆንም በህገወጥ ምርጫ ለተቋቋመ ህገወጥ መንግስት በጀት እንዳይሰጥ ፤ ይሁን እንጂ የወረዳና ቀበሌ አስተዳደር አካላት በጀት በቀጥታ ከማዕከላዊ መንግስት እንዲሰጣቸው ወሰነ:: ክልል የሚባል ህገወጥ መንግስት ሆነ::  ጁንታው ሁለተኛውን ነጥብ ጣለ::
ጡረተኛና ዘራፊ ፖለቲከኞች ፤ የጦር መሪዎችና የደህንነት ሹሞችን የሰበሰበው ጁንታ ሶስተኛ ነጥቡን በሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት በመሰንዘር ጣለ:: በሀገራችን አሳፋሪና አስነዋሪ ታሪክ አስመዘገበ::
አሁን ደግሞ የአማራና አፋር ክልሎችን በመውረር ንፁሀንን ጨፈጨፈ ፤ ዘረፈ፤ አጎሳቆለ:: አራተኛውን ነጥብ ጣለ::
ሩብ ክፍለ ዘመን ሀገር በመራበት ጊዜ የፈፀማቸው ጥፋቶች ይበቁት ነበር:: የኢትዮዽያ ህዝብ ምንም እንኳ ቢበደልም ለይቅርታ የሚሆን ልብ እና አንጀት አላጣም ነበር:: ይቅር ብሎትም ነበር:: ነገር ግን ይቅርታ ይሉኝታን ለሚያውቅ በኢትዮዽያዊ ጨዋነትና ስነምግባር ተኮትኩቶና ተገርቶ ላደገ እንጂ ሳያውቅ አውቃለሁ ለሚል ፤ ሳይማር ተማርኩ ለሚል፤ ማታለሉ እየታወቀበት እንደማይታወቅበት ለሚያስብ ብልጣብልጥ፤ እየዘረፈ መዝረፍ ከፈጣሪው የተሰጠ ፀጋ ለሚመስለው ወመኔ፤ ሞቶም አልሞትኩም እኮ ለሚል እርኩስ መንፈስ ለተጠናወተው፤ እርሱ ከሌለ ትውልዱም እንዲጠፋ ለሚፈርድ ፍርደ ገምድል እንደማይሰራ ተረጋግጧል:: ይህ የጁንታ አስተሳሰብ ደግሞ የጥቂት ዘራፊ፣ ቀማኛ፣ ውሸታም፣ ገዳይ ወንበዴና አሸባሪ ጡረተኛ ቡድን ብቻ እንዳልሆነ ተረጋግጧል::
ገራሚው ነገር የዓለም ፖሊስ መሳዮች፣ የዴሞክራሲ አስተማሪዎች ነን ባዮች፣ በጊዜ መዛባት እና ኢ-ፍትሀዊ ዓለማዊ ሁኔታ አድገናል ፊት ነን የሚሉ ሀገራት ይህ አሸባሪ ቡድን ሀገራችንን ለማፍረስ ችግሩን ከመጠንሰስ ጀምሮ የሚያደርገውን ግልፅ የንፁሀን ጭፍጨፋ፣ ዘረፋ፣ ወረራ ወዘተ… ነውረኛ ድርጊቶች እንኳን ሊገስፁ ቀርቶ እንዲያውም ቀለብ ከመስፈር ጀምሮ የህክምና መድሀኒቶችና የመገናኛ መሳሪያዎችን እያመቻቹ መገኘታቸው ሳያንስ መንግስትን ሲተቹ፤ ሲጎነትሉና ሲያስፈራሩ ማየት ልብን ያደማል፤ ጨጏራ ይመልጣል፤ ቆሽትን ያሳርራል::
ጨው ሲበዛ ይመራል እኮ፤ ለመሆኑ እኒህ አካላት እንደትኋን እየመጠመጡን የሚዘልቁ መስሏቸው ከሆነ ተሳስተዋል:: ከእኛው ወልጋዳ ባንዳዎች ጋር ሆነው የሚሰሯትን እያንዳንዷን ሴራም እናውቃለን:: ለአሁኑ ከሳሽም ፈራጅም፣አልቃሽም አንጋሽም፣ አጣሪም መርማሪም፣ ጯሂም ገላጋይም እነሱው በመሆናቸው እውነት ብንይዝም ጆሮ ዳባ ለብሷል:: ፍትህና ርትዕም ተቀብሯል:: አንድ ነገር ግን እንላቸዋለን የትኛውም ቦታ ቢሆን ጁንታው እና ተባባሪዎቹ የእጃቸውን ያገኛሉ::ሞትን ይመርጣሉ እንጅ ኢትዮዽያውያን በነፃነታቸው ላፍታም አይደራደሩም::
ስለሆነም እንደ አበው አባባል “ካልደፈረሰ አይጠራም ካልጠራ አይጠጣም” እንላለን:: ትርጉሙም በችግር ውስጥ ካልታለፉ በስተቀር መልካም ነገር ተመቻችቶ አይገኝም ለማለት ነው:: የእስካሁን ክብራችንንና ነፃነታችንን የተጎናፀፍነውም በጀግኖቻችን መስዋዕትነት ነው::
Filed in: Amharic