>

የጋዜጠኛ ወርቁ ዓለማየሁ 19ኛ ሙት ዓመት መታሰቢያ! (ቅዱስ ሃብት በላቸው)

የጋዜጠኛ ወርቁ ዓለማየሁ 19ኛ ሙት ዓመት መታሰቢያ! 

ቅዱስ ሃብት በላቸው

ዛሬ (ነሃሴ9 ቀን) በኢትዮጵያ የነፃ ፕሬስ ታሪክ ፋና-ወጊ ተብለው በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱት ጋዜጠኞች መካከል አንዱ የሆነው የመብሩክ/መብረቅ ጋዜጣ አሳታሚና አዘጋጅ የነበረው ጋዜጠኛ ወርቁ ዓለማየሁ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየበት ዕለት ነው። “ትንሿ ትግራይ!” በሚል ርዕስ በአንድ መንግስታዊ ተቋም ውስጥ ከላይ እስከታች የተሰገሰጉትን የአንድ ብሔር ሰዎች በማስረጃ ማጋለጡን ተከትሎ ድንገት ታፍኖ እስር ቤት ተጥሎ የነበረው ጋዜጠኛ ወርቁ፣ ከእስር ቤት እንደወጣ ነበር እስከወዲያኛው ከዚህ ዓለም በሞት የተለየን። ጋዜጠኛ ወርቁ ከዚያም በፊት ቢሆን በአምባገነኑና ዘረኛው ሕወሃት አገዛዝ ያለአግባብ እየታፈነ በተደጋጋሚ ለእስርና እንግልት ሲዳረግ ነበር።

በአንድ ወቅት የከፍተኛው ፍ/ቤት ሁለተኛ ወንጀል ችሎት ተከሶ ይቀርባል። የተከሰሰው ወያኔ የመጀመሪያዎቹን “ጄነራሎች” ከብዙኀኑ ህዝብ ደብቆ ሾሞ ወሬውን አፍኖት ስለነበር፤ “በረኸኞቹ ያለወታደራዊ ሣይንስ በከፍተኛ ማዕረግ ተንበሸበሹ” በሚል ርዕስ ባወጣው ዜና ነው። በዜናው የተሿሚዎቹን ዝርዝርና ያላቅማቸው የተጫነላቸውን “ማዕረግ” ዘርዝሮ ለህዝብ አቀረበ። የቀረበው የነፃ ፕሬስ ጋዜጠኞችን፣ የተቃዋሚ ፖለቲካ መሪዎችንና አባላትን እንዲሁም ሥርዓቱ ያሰጉኛል ያላቸውን በመቅጣት ከሚታወቁት “ዳኛ” ተብዬዎች ዋነኛ ከሆነው ልዑል ገ/ማርያም ያለበት ችሎት ነበር።

ጋዜጠኛው ዜናው እውነት መሆኑን ወንጀል አለመፈጸሙን ገለጸ። በዚሁ ዜና በምርመራ ስም በፓሊስ ጣቢያ ለረጅም ጊዜ ታስሮ መንገላታቱም አግባብ አለመሆኑን አስረዳ። በጊዜው መከላከያ ማስረጃ እንዳለው ይገልፃል። በዚህ ጊዜ በቁጣ ይህ ዳኛ ተብዬ “ምንድነው መከላከያ ማስረጃህ?” ብሎ ይጮኻል። ተከሳሹ “መከላከያ ማስረጃዎቼ የተሾሙት ጄነራሎች ከየትኛው ወታደራዊ ሣይንስ ተመርቀው እንደወጡ ቀርበው ያስረዱልኛል …” በማለት፤ “… ሜ/ጄነራል ፃድቃን ገ/ተንሳይ፣ …” እያለ መዘርዘር ሲጀምር ይህ ፍትህ ገዳይ አላስችል ብሎት “ዝምበል አንተ እነሱ እንዳንተ ሥራ ፈት አይደሉም። እዚህ ሊመጡልህ አይችሉም” ይልና በቁጣ ያቋርጠዋል።

የቀኝ ዳኛ የነበረችው ወጣት ጣልቃ ገብታ “መከላከያ ምስክር መጥራት መብቱ ነው። እነሱም ለምስክርነት ከተጠሩ ይቀርባሉ። ማንም ሰው ከሕግ በላይ አይደለም” ትላለች። ችሎቱ ፍጥጫ ነገሰበት። ልዑል የሚችለውን ተሳድቦ ሌላ ቀጠሮ ሰጠ። ዳኛዋ ከዚያ በኋላ በዚያ ችሎት አልታየችም። ወያኔ ዘግይቶ ሓየሎም ሲገደል ወያኔ ሹመቱን ሳይወድ ይፋ አድርጎ አወጣ። ጋዜጠኛው ቢቸግረው “ጄነራሎቹ” አይቀርቡም ከተባለ ወያኔ እራሱ ያወጣው ዝርዝር በማስረጃ ይቅረብ ሲልም ሊቀበለው አልፈቀደም። ለወያኔ “ፍትህ” ማለት ይህ ሲሆን፤ ለዳኛ ተብየው ልዑል ገ/ማርያም ደግሞ “ሕግ” የወያኔ ጠላቶች የተባሉትን ሁሉ ያለምህረት መቅጫ የበቀል መሣሪያ ነው።” 

ጋዜጠኛ ወርቁ ባለትዳርና የአንድ ልጅ አባት ነበር። እግዚአብሔር አምላክ የወንድማችንን ነፍስ ማደሪያዋን ከቅዱሳን ጋር ያድርግልን፤ አሜን!

Filed in: Amharic